ሕዝቅኤል
19 “ስለ እስራኤል አለቆች ሙሾ አውጣ፤* 2 እንዲህም በል፦
‘እናትህ ምን ነበረች? በአንበሶች መካከል ያለች እንስት አንበሳ ነበረች።
በብርቱ ደቦል አንበሶች መሃል ተኛች፤ ግልገሎቿንም በዚያ አሳደገች።
3 ከግልገሎቿ መካከል አንዱን ተንከባክባ አሳደገችው፤ እሱም ብርቱ ደቦል አንበሳ ሆነ።+
አድኖ መብላት ተማረ፤
ሰዎችንም እንኳ ሳይቀር በላ።
4 ብሔራት ስለ እሱ ሰሙ፤ ጉድጓዳቸው ውስጥ ገብቶም ያዙት፤
በስናግም እየጎተቱ ወደ ግብፅ ምድር አመጡት።+
5 እሷም በትዕግሥት ስትጠባበቅ ከቆየች በኋላ የመመለስ ተስፋ እንደሌለው ተገነዘበች።
በመሆኑም ከግልገሎቿ መካከል ሌላውን ወስዳ እንደ ብርቱ ደቦል አንበሳ አድርጋ ላከችው።
6 እሱም በአንበሶች መካከል ይጎማለል ጀመር፤ ብርቱ ደቦል አንበሳም ሆነ።
አድኖ መብላት ተማረ፤ ሰዎችንም እንኳ ሳይቀር በላ።+
7 በማይደፈሩት ማማዎቻቸው መካከል አደባ፤ ከተሞቻቸውንም አወደመ፤
ከዚህም የተነሳ ግሳቱ ወና በሆነችው ምድር ላይ አስተጋባ።+
8 በዙሪያው ባሉ ግዛቶች ያሉ ብሔራት መረባቸውን በእሱ ላይ ለመዘርጋት ተነሱበት፤
እሱም ጉድጓዳቸው ውስጥ ገብቶ ተያዘ።
9 በስናግ ጎትተው በእንስሳት ጎጆ ውስጥ በመክተት ወደ ባቢሎን ንጉሥ አመጡት።
ከዚያ በኋላ ድምፁ በእስራኤል ተራሮች ላይ እንዳይሰማ በዚያ አሰሩት።
10 እናትህ በውኃዎች አጠገብ እንደተተከለ፣ በደምህ ውስጥ ያለ የወይን ተክል* ነበረች።+
ከውኃው ብዛት የተነሳ ፍሬ አፈራች፤ ብዙ ቅርንጫፎችም ነበሯት።
11 ለገዢዎች በትረ መንግሥት የሚሆኑ ጠንካራ ቅርንጫፎች* አወጣች።
አድጋ ከሌሎች ዛፎች ይበልጥ ረጅም ሆነች፤
ደግሞም ከርዝመቷና ከቅጠሎቿ ብዛት የተነሳ ጎልታ ታየች።
12 ሆኖም በቁጣ ተነቀለች፤+ ወደ ምድርም ተጣለች፤
የምሥራቅም ነፋስ ፍሬዋን አደረቀው።
ጠንካራ ቅርንጫፎቿ ተሰብረው ደረቁ፤+ እሳትም በላቸው።+
13 በዚህ ጊዜ በምድረ በዳ፣
ውኃ በሌለበት ደረቅ ምድር ተተከለች።+
“‘ይህ ሙሾ ነው፤ ሙሾ ሆኖም ያገለግላል።’”