ወደ መኖሪያቸው እንደሚበሩ እርግቦች
የሰው ልጅ ለማዳ ካደረጋቸው አእዋፍ መካከል የመጀመሪያዎቹ እርግቦች ሳይሆኑ አይቀሩም። ግብፃውያን ከብዙ ሺህ ዓመታት በፊት ዓመቱን በሙሉ ሊገኝ የሚችል ቀለብ ለማዘጋጀት በመፈለጋቸው በቤታቸው አቅራቢያ የእርግብ ቤት ይሠሩ ነበር። የእርግቦች ስጋ በጣም ተወዳጅ ነበር። ፍጋቸውም ለመሬት ማዳበሪያ ያገለግል ነበር። በመካከለኛው ዘመን በአንዳንድ አገሮች የእርግብ ቤት ሊኖራቸው የሚችሉት ታላላቅ ሰዎችና ሃይማኖታዊ ባለሥልጣኖች ብቻ ስለነበሩ ብዙ ሰዎች የሚመኙት ንብረት ሆኖ ነበር።
በአሁኑ ጊዜ እርግቦች በመብልነታቸው በአብዛኛው በዶሮዎች የተተኩ ቢሆንም የጥንቶቹን የእርግብ ቤቶች አሁንም ማግኘት ይቻላል። እዚህ ፎቶግራፍ ላይ የሚታዩት በግብፅ የሚገኙ የእርግብ ቤቶች ናቸው።
በምሽት ላይ አንድ ላይ ሆነው ወደ ቤታቸው ሲመለሱ ዳመና ይመስላሉ። ዕብራዊው ነቢይ ኢሳይያስ “እርግቦች ወደ ቤታቸው እንደሚበርሩ፣ እነዚህ እንደ ደመና የሚበርሩ እነማን ናቸው?” ብሎ ሲጠይቅ ይህን ማመልከቱ ነበር። ሌላ የመጽሐፍ ቅዱስ ትርጉም ደግሞ “እነዚህ እንደ ደመና የሚያንዣብቡትና ወደ ወፍ ቤት ቀዳዳዎች እንደሚበሩ እርግቦች የሚበርሩት እነማን ናቸው?” ይላል።—ኢሳይያስ 60:8፤ ዘ ኒው ኢንግሊሽ ባይብል
መልሱ በአሁኑ ጊዜ ወደ ይሖዋ ድርጅት እየጎረፉ ያሉት በመቶ ሺህ የሚቆጠሩ ፈሪሃ አምላክ ያላቸው ሕዝቦች ናቸው። በይሖዋ ምሥክሮች የመንግሥት አዳራሽ ውስጥ በአምላክ ላይ ተስፋ ማድረግን ይማራሉ። (ኢሳይያስ 60:9) በአምላክ ሕዝቦች መካከል አንዲት እርግብ በእርግብ ቤት ውስጥ የምታገኘውን የመሰለ ሰላምና ፀጥታ፣ እንዲሁም ሕያው የሆነ እምነት፣ ጤናማ ባልንጀሮችና ለመንፈሳዊ ነገሮች ቅድሚያ የመስጠት ባሕርይ አግኝተዋል።
[በገጽ 32 ላይ የሚገኝ ሥዕል]
Pictorial Archive (Near Eastern History) Est.