በፍቅር ተነሳስተው አደረጉት
በካናዳ የምትኖር ታማኝና እንግዳ ተቀባይ የሆነች አንዲት ባሏ የሞተባት ሴት አራት ወጣት ሴቶች ልጆችዋን በእውነተኛ ክርስትና በማሰልጠን ታሳድግ ነበር። የጉባኤው ሽማግሌዎች ቤቷ ከፍተኛ እድሳት እንደሚያስፈልገው አስተዋሉ። ይህች ሴት ይህን እድሳት ለማከናወን የሚያስችል ገንዘብም ሆነ ችሎታ የላትም። ስለዚህ ሽማግሌዎች በ1 ጢሞቴዎስ 5:9, 10 ላይ ከተገለጸው መሠረታዊ ሥርዓት ጋር በመስማማት ቤቷን ለማደስ በዘዴ ዝግጅት አደረጉ። እንዴት?
ይህች ሴትና ልጆችዋ ለአምስት ቀናት ወደ ሌላ ቦታ እንዲሄዱ አመቻቹ። ከ80 የሚበልጡ የጉባኤው አባላት ቁሳቁስ፣ ገንዘብና ጊዜያቸውን በመለገስ የሙሉ ልብ ድጋፍ አበረከቱ። ብዙም ሳይቆይ ቤተሰቡ ወደ ሌላ ቦታ ሄደ፤ ዝግጁ የሆኑት ሠራተኞች ቤቱን እንደ ንብ ወረሩት። የቤቱ ውጪያዊ ክፍል ሙሉ በሙሉ ተጠገነ። ግድግዳዎች ተለስነው ቀለም ተቀቡ። ወለሉ ሊሾ ተደርጎ አዲስ ንጣፍ ከገባለት በኋላ በላዩ ላይ አዲስ ምንጣፍ ተነጠፈ። አስፈላጊው ኤሌክትሪክና መብራት በሙሉ ገባለት። ያረጁ የቤት ዕቃዎች እንኳ በሌላ ተተኩ። ጠቅላላው እድሳት በአምስት ቀን ውስጥ ተጠናቀቀ!
የነበረው ደስታና የሥራ እንቅስቃሴ የአካባቢው ሰዎቸ መነጋገሪያ ርዕስ ሆኖ ነበር። 80 ዓመት ዕድሜ ያላቸው አንድ ጎረቤት የምሥክሮቹ ሥራ ስለነካቸው የቀለም ብሩሽ ይዘው መጡና አብሬያችሁ ካልሠራሁ አሉ። ከፈቃደኛ ሠራተኞቹ መካከል የአንዱ አሠሪ የሆነ ሰው ለኩሽናው ምድጃ አየር ማስገቢያ የሚያገለግል እቃ ሰጠ። ሌላኛው አሠሪ ደግሞ አዳዲስ የኩሽና መደርደሪያዎች አበረከተ። አንድ ሰው በጣም ስለተነካ ስለ ይሖዋ ምሥክሮች ይበልጥ ለማወቅ ፈለገ። በምድር ላይ በገነት ለዘላለም መኖር ትችላለህ የተባለውን መጽሐፍ በደስታ ወሰደ።
እናትና ልጆቹ ወደ ቤታቸው ሲመለሱ በፊታቸው ላይ ፍጹም ደስታ ይነበብ ነበር። ከደስታ የተነሳ መላቀስ፣ መሳቅና መተቃቀፉ ሌላ ነበር። ክርስቲያናዊ ፍቅርና ስሜት የታየበት የማይረሳ ጊዜ ነበር። ጳውሎስ “እንግዲያስ ጊዜ ካገኘን ዘንድ ለሰው ሁሉ ይልቁንም ለሃይማኖት ቤተ ሰዎች መልካም እናድርግ” በማለት ስለጻፈ በእርግጥም ችግር ላለባቸው የጉባኤ አባላት ልባዊ ፍቅርና አሳቢነት ማሳየት የእውነተኛ ክርስትና መለያ ምልክት ነው።—ገላትያ 6:10