የወንጌል እውነተኝነት
ፓፒረስ ስልሳ አራት (P64) በመባል የሚታወቁ ሦስት በእጅ የተጻፉ የማቴዎስ ወንጌል ቁርጥራጮች ከ1901 ጀምሮ እንግሊዝ ኦክስፎርድ ውስጥ በሚገኘው በማግደለን ኮሌጅ እጅ ይገኛሉ። ምሁራን እነዚህ ቁርጥራጮች የተጻፉት በሁለተኛው መቶ ዘመን እዘአ ማብቂያ ላይ እንደሆነ ያምኑ ነበር።
በቅርቡ በጀርመን ፓደርቦርን የፓፒሮሎጂ ምሁር የሆኑት ካርስተን ፒ ቲዴ በማቴዎስ ወንጌል ምዕራፍ 26 ውስጥ የሚገኙ 10 ቁጥሮችን በያዘው P64 ላይ ጥልቅ ምርምር አድርገው ነበር። ምን ውጤት ተገኘ? ሳይትሽሪፍት ፊዩር ፓፒዮሮሎጊ ኡንድ ኢፒግራፊክ በተባለ መጽሔት (የፓፒሮሎጂ እና የኢፒግራፊክስ መጽሔት) ላይ የኦክስፎርዱ ቁርጥራጭ “የመጀመሪያው መቶ ዘመን የክርስቲያን ኮዴክስ ቁራጭ፣ ምናልባትም (እርግጠኛ ባይሆንም) ቀድሞ ሲታሰብ ከነበረው ቀደም ብሎ በ70 እዘአ የተጻፈ” እንደሆነ ቲዴ ገልጸዋል።
ቲዴ ያቀረቧቸው ሐሳቦች የጋዜጠኞችና የምሁራን ቡድኖች መነጋገሪያ ሆነዋል። ይህ የሆነው ለምንድን ነው? ምክንያቱም በአሁኑ ጊዜ ከሁሉ ይበልጥ ረዥም ዕድሜ አለው ተብሎ ተቀባይነት ያገኘው የወንጌል ክፍል P52 ነው። ይህም በ125 እዘአ ወይም ከሁለተኛው መቶ ዘመን ወዲህ የተጻፈው የዮሐንስ ወንጌል ቁርጥራጭ ነው።
P64 የተባለው የፓፒረስ ቁርጥራጭ መቼ እንደተጻፈ የተሰጠው አዲሱ ቀን ሰፊ ተቀባይነት ማግኘቱና አለማግኘቱ ወደ ፊት ይታያል። ያም ሆነ ይህ ረዥም ዕድሜ እንዳለው መታወቁ P64 ከሁሉ ይልቅ ጥንታዊ መሆኑን የሚያሳይ ብቻ ሳይሆን የማቴዎስ ወንጌል በመጀመሪያው መቶ ዘመን እንደተጻፈ ተጨማሪ ማረጋገጫ ይሰጣል። የተጻፈው የወንጌሉን ትክክለኛነት የሚመሰክሩ በኢየሱስ ምድራዊ ሕይወት የተፈጸሙትን ነገሮች የተመለከቱ አያሌ የዓይን ምሥክሮች በሕይወት በነበሩበት እንዲያውም ከ70 እዘአ ቀደም ብሎ ሊሆን ይችላል።
[ምንጭ]
By permission of the President and Fellows of Magdalen College, Oxford.