የተስፋይቱን ምድር መጎብኘት
አንድ ጓደኛህ በስጦታ መልክ ሊያበረክትልህ ፈልጎ ውብ በሆነና ጸጥ ባለ አካባቢ የሚገኝ አዲስ ቤት እንደገዛልህ ነገረህ እንበል። ‘ቤቱ ምን ይመስል ይሆን?’ ብለህ መጠየቅህ አይቀርም። ራስህ ሄደህ ቤቱን ለማየትና እያንዳንዱን ክፍል ተዘዋውረህ በደንብ ለመመልከት እንደምትጓጓ ምንም ጥርጥር የለውም። ምክንያቱም አዲስ ያገኘኸው ቤትህ ነው!
ይሖዋ በ1473 ከዘአበ ለጥንቱ የእስራኤል ብሔር አዲስ መኖሪያ አወረሳቸው። የተስፋይቱ ምድር የሚል መጠሪያ ያለው ይህ መኖሪያ ከሰሜን እስከ ደቡብ 500 ኪሎ ሜትር ርዝመትና በአማካይ 55 ኪሎ ሜትር ስፋት ያለው ቀጭን ረጅም ቦታ ነው።a እጅግ ለም የሆኑ አካባቢዎችን የሚያካልለው የተስፋይቱ ምድር ብዛት ያላቸው የራሱ የሆኑ ልዩ ገጽታዎች ያሉት አስደሳች የመኖሪያ ሥፍራ ነበር።
ሆኖም ለሌላ ሰው በተለይም ከረጅም ጊዜ በፊት ይኖር ለነበረ ሰው ስለተሰጠ አንድ “ቤት” ማንሳት ለምን አስፈለገ? ምክንያቱም ስለዚህ ታሪካዊ ቦታ የምታገኘው እውቀት ለመጽሐፍ ቅዱስ ታሪኮች ያለህን አድናቆት ስለሚያጎለብትልህ ነው። ፕሮፌሰር ዮሃናን አሃሮኒ “በመጽሐፍ ቅዱስ ላይ በተመዘገቡት አገሮች ውስጥ መልከዓ ድርና ታሪክ በጣም የተሳሰሩ ከመሆናቸው የተነሳ አንዱን ከአንዱ ነጥሎ መረዳት አይቻልም” በማለት ጽፈዋል። በተጨማሪም የተስፋይቱ ምድር በቅርቡ በአምላክ መንግሥት ሥር በመላው ዓለም የሚኖረው ገነት ለሰው ልጆች ምን ማለት እንደሚሆን በትንሹ ያሳየናል።—ኢሳይያስ 11:9
ኢየሱስ ክርስቶስ በምድራዊ አገልግሎቱ ወቅት ተግባራዊ ትምህርት ለማስተላለፍ በተስፋይቱ ምድር ውስጥ በብዛት ይታዩ በነበሩ ነገሮች ተጠቅሟል። (ማቴዎስ 13:24-32፤ 25:31-46፤ ሉቃስ 13:6-9) በጥንቱ የጳለስጢና ምድር የነበሩትን ሁኔታዎች በመመርመር ብዙ ነገሮችን ተግባራዊ በሆነ መንገድ መማር እንችላለን። እስቲ የቤቱን አንዳንድ ክፍሎች በሌላ አባባል ለብዙ መቶ ዓመታት ለአምላክ ህዝቦች መኖሪያነት ያገለገለውን የዚህን ምድር ጉልህ ገጽታዎች እንመርምር። ቀጥለን እንደምንመለከተው ከተስፋይቱ ምድር ብዙ የምንማረው ነገር አለ።
[የግርጌ ማስታወሻ]
a በእነዚህ ርዕሶች ውስጥ “የተስፋይቱ ምድር” የተገለጸችው በመጽሐፍ ቅዱስ ላይ የሰፈረውን የጥንቱን ሁኔታ ለማመልከት ነው። በጊዜያችን በክልሉ ካለው ፖለቲካዊ/ሃይማኖታዊ ሁኔታዎች ጋር ግንኙነት የለውም።
[ምንጭ]
Cover: Pictorial Archive (Near Eastern History) Est.
[ምንጭ]
Garo Nalbandian