“የእውነት ዕንቁዎች”
“የእውነት ዕንቁዎች።” በናይጄርያ ወደሚገኘው የይሖዋ ምሥክሮች ቅርንጫፍ ቢሮ የተላከ አንድ ደብዳቤ ሁለት ልዩ መጽሔቶችን እንዲያ በማለት ገልጿቸዋል። ይህን ደብዳቤ የጻፈው ወጣት እንዲህ ሲል ያብራራል:-
“ይህን ደብዳቤ የጻፍኩላችሁ በመጠበቂያ ግንብ እና ንቁ! መጽሔቶች አማካኝነት ማንኛውንም የዕለት ተዕለት የኑሮ ዘርፍ የሚዳስስ ሐሳብ ለማውጣት ስለምታደርጉት ጥረት ልባዊ የሆነ ምስጋናዬን ለመግለጽ ነው።
“አሥራ ሰባት ዓመቴ ነው። ባለፈው ዓመት በከተማው የሚገኝ አንድ የሬዲዮ ጣቢያ ‘ፍቅር ሲባል የጾታ ግንኙነት ማለት ብቻ አይደለም—ኤድስ የፈጠራ ወሬ አይደለም’ በሚል ጭብጥ አንድ የድርሰት ውድድር አዘጋጅቶ ነበር። እያንዳንዱ ድርሰት ከአራት መቶ ያላነሱ ቃላት ሊኖሩት ይገባ ነበር። አሸናፊ የሆነው ድርሰት 1,000 ናይራ [12.50 የአሜሪካ ዶላር] ሽልማት ያስገኝ ነበር። የሬዲዮ ፕሮግራሙ አዘጋጆች በእርግጥ ሰዎች ሽልማት ለማግኘት ብቻ ሳይሆን ከዚህ ይልቅ አንድ ነገር ለመማር ሲሉ ሊጽፉ ይገባል ብለው ነበር። . . .
“በሁለቱም መጽሔቶች ስለ ኤድስ የሚገልጽ ሐሳብ አግኝቻለሁ። ስለ ፍቅር የተጻፉ ለቁጥር የሚያታክቱ ብዛት ያላቸው ርዕሰ ትምህርቶች አሉ። በነሐሴ 8, 1978 ንቁ! መጽሔት ላይ ያገኘኋቸውን ነጥቦች ተጠቀምሁ።
“ድርሰቴን ከላክሁ ከሁለት ወራት ገደማ በኋላ ውጤቱ ታወቀ። በክሮስ ሪቨር እና በአክዋ ኢበም ግዛቶች ውስጥ አንደኛ መውጣቴን ሳውቅ ተገረምኩ!
“የጻፍኩት ሐሳብ በሙሉ ከመጽሔቶቹ ያገኘሁት ነበር። ይሖዋ በዚህ አስጨናቂና በመንፈሳዊ ብልሹ በሆነ ዓለም ውስጥ ወቅታዊ ማብራሪያ ስለሚያቀርብልን በጣም እናደንቀዋለን። እውነተኛ ክርስቲያኖች እንደመሆናችን መጠን ፍቅር ሲባል የጾታ ግንኙነት ማለት ብቻ እንዳልሆነ እናውቃለን። እንዲሁም አኗኗራችን ንጹህና ሥነ ምግባራዊ ከሆነ እንደ ኤድስ ከመሳሰሉ በሽታዎች እንደሚጠብቀን የተረጋገጠ ነው።
“ያላንዳች መታከት ለምታወጧቸው ለእነዚህ የእውነት ዕንቁዎች ሳላመሰግናችሁ አላልፍም። እነዚህን ብርቅ መጽሔቶች ያለማቋረጥ ለማቅረብ ለምታደርጉት ጥረት ይሖዋ መባረኩን ይቀጥል።”