“ያላችሁን አጥብቃችሁ ያዙ”
አንድ የይሖዋ ምሥክሮች ቡድን በግሪክ አገር ሲክለዲዝ ተብለው ከሚጠሩት 30 የሚሆኑ ደሴቶች መካከል በአንዱ የስብከት ሥራ እያከናወነ ነበር። ከእነርሱ መካከል ሁለቱ በአንድ መንገድ ዳር ከቤት ወደ ቤት እያገለገሉ ሳለ አንድ ፖሊስ ያገኛቸውና ወደ ፖሊስ ጣቢያ ይዟቸው ይሄዳል። ፖሊስ ጣቢያ ደርሰው ብዙም ሳይቆዩ ስልክ ይደወላል። የመንደሩ ቄስ ነበር። “የይሖዋ ምሥክሮች ወደ መንደራችን እንደመጡ ሰምቻለሁ” በማለት ተናገረ። “አዎን፣ ሁለቱ ከእኔ ጋር ናቸው” በማለት ፖሊሱ መለሰ። “አሁኑኑ እመጣለሁ።” ፖሊሱና ቄሱ ሲነጋገሩ ይሰሙ ስለነበር ወንድሞች ትንሽ ስጋት አደረባቸው።
ይሁን እንጂ ቄሱ እንደ ደረሰ በፈገግታ ጨበጣቸው። ከዚያም ከፖሊሱ አጠገብ በነበረው ወንበር ላይ ተቀመጠ። ውይይቱ ሞቅ እያለ ሲሄድ ቄሱ ያሳይ የነበረው የተግባቢነትና የትህትና መንፈስ ፖሊሱን አበሳጨው። ምሥክሮቹን እንዳያመናጭቃቸው ለፖሊሱ ከነገረው በኋላ “በቲኦክራሲያዊ የአገልግሎት ትምህርት ቤት ጥሩ ሥልጠና ስለሚያገኙ ማንኛውም ዓይነት ጥያቄ ቢቀርብላቸው መመለስ ይችላሉ። አንድ የይሖዋ ምሥክር እምነቱን እንዲለውጥ ለማድረግ ከመሞከር ይልቅ ዓለምን ከመሠረቱ ማናጋት ይቀላል” በማለት አክሎ ተናገረ።
ወንድሞች በቀጣዩ ቀን ጠዋት እየሰበኩ ሳለ ቄሱን አገኙትና “ፖሊስ ጣቢያ በነበርንበት ጊዜ በጥሩ ወዳጃዊ መንፈስ ልታነጋግረን የቻልከው ለምንድን ነው?” ብለው ጠየቁት። ቄሱም ሲሮስ ውስጥ በነበረበት ጊዜ በርካታ የይሖዋ ምሥክሮችን ያውቅ እንደነበረና ለብዙ ዓመታት መጠበቂያ ግንብ እና ንቁ! መጽሔቶች ያነብ እንደነበረ ገለጸላቸው። እንዲያውም በተደጋጋሚ ጊዜያት የመጠበቂያ ግንብ መጽሔት በማኅደሩ ውስጥ ደብቆ ወደ ቤተ ክርስቲያን ይወስድና ከመጽሔቱ እያነበበ ይሰብክ ነበር። “የእናንተን ጽሑፍ ባላገኝ ኖሮ ሕይወት ትርጉም የለሽ ይሆንብኝ ነበር። ተስፋዬን የሚያለመልመው የእናንተ ጽሑፍ ነው” በማለት አስተያየቱን ሰጥቷል።
ከዚያም ቄሱ ለምሥክሮቹ እንዲህ አላቸው:- “አንድ ነገር ልነግራችሁ እፈልጋለሁ። ያላችሁን አጥብቃችሁ ያዙ። እምነታችሁን ለመተው ፈጽሞ አታስቡ። አሁን እየነገርኳችሁ ያለሁት ነገር እስካሁን ከሰጠሁት የስብከት ንግግር ሁሉ የሚበልጥ ነው። ይህን የምነግራችሁ ከልቤ ነው።”