“ሰላማዊ መንፈስ መኖሩን ማየት ችያለሁ”
ጀርመንኛ ተናጋሪ የሆነ አንድ ሰው የይሖዋ ምሥክሮችን “ለመሰለል” ሲል እነሱ ወዳዘጋጁት አንድ የአውራጃ ስብሰባ ሄደ። ለምን? ዓላማው “ይህን ኑፋቄ ለማጋለጥና ጓደኞቹን ከተሳሳተ ጎዳና ለመመለስ” ነበር። በስብሰባው ላይ ከተገኘ በኋላ ለጓደኞቹ የሚከተለውን ደብዳቤ ጻፈላቸው:-
“ወደ ስብሰባው ቦታ ስቀርብ ቦታውን ተሳስቼ ይሆን እንዴ ብዬ አሰብኩ። ከስታዲዮሙ ውጭ የቆመ አንድም ሰው አልነበረም፤ እንዲሁም መሬት ላይ የተጣለ ቆሻሻም ሆነ የቢራ ቆርቆሮ አልነበረም። ይበልጥ እየቀረብኩ ስመጣ ስታዲዮሙ መግቢያ ላይ የቆሙ ሁለት ሰዎች ተመለከትሁ። ሰላምታ ከሰጡኝ በኋላ እንድገባ ጋበዙኝ።
“በስብሰባው ላይ ለመገኘት የመጡት በሺዎች የሚቆጠሩ ሰዎች የሚፈጥሩትን ውካታና ጫጫታ ለመስማት ጠብቄ ነበር፤ ሆኖም ፍጹም ጸጥታ ሰፍኖ ነበር። ‘ምናልባት እዚያም እዚህም በተን ብለው የተቀመጡ ጥቂት ሰዎች ኖረው ይሆናል’ ብዬ አሰብኩ።
“ልክ እንደገባሁ ትኩረቴ መድረኩ ላይ እየታየ በነበረው ድራማ ተሳበ። ከዚህ በኋላ ነበር ስታዲዮሙ በትኩረት በሚያዳምጡ በሺዎች በሚቆጠሩ ሰዎች ጢም ብሎ መሞላቱን የተገነዘብኩት። ሰላማዊ መንፈስ መኖሩን ማየት ችያለሁ። በተቀረው የስብሰባው ጊዜ የሰማሁት፣ ያየሁትና ያስተዋልኩት ሁሉ የማይረሳ ትዝታ ጥሎብኝ አልፏል።
“ከምሥክሮቹ ጋር ተደባልቄ በተቀመጥኩበት ደስተኛ ፊታቸውንና ፍቅራዊ መግለጫቸውን ማየት ችያለሁ። ወዲያው ወደ አእምሮዬ የመጣውን ‘በእርግጥ እነዚህ የአምላክ ሕዝቦች ናቸው!’ የሚለውን ሐሳብ ማስወገድ አልቻልኩም።”
ይህ ወጣት ‘ጓደኞቹን ከመመለስ’ ይልቅ እነርሱ መጽሐፍ ቅዱስን እንዲያስጠኑት ጠየቃቸው። ውጤቱ ምን ሆነ? ዛሬ ክርስቲያን ሽማግሌ ሆኗል። እርሱና ቤተሰቡ በስዊዘርላንድ፣ ዙግ ከሚገኙት ጉባኤዎች በአንዱ ንቁ ተሳትፎ ያደርጋሉ።