መልካም ስማችን እንዳይጎድፍ መጠንቀቅ
አንድን የሚያምር ሥዕል በጥሞና መመልከት አስደሳች ሊሆን ይችላል። አንድ ሰው ሥዕሉን ቀረብ ብሎ በጥሞና ሲመለከት ሠዓሊው በብሩሹ አማካኝነት የተለያዩ ቀለማትን ለብዙ ጊዜ በሸራው ላይ በማሳረፍ እንዴት በሚያስገርም ሁኔታ እንደሳለው ያስተውላል።
በተመሳሳይም መልካም ስም የሚገኘው በምሳሌያዊ አነጋገር እንዲያው በአንድ የብሩሽ ቅብ ሳይሆን ረዘም ባለ ጊዜ ውስጥ በሚፈጸሙ ብዙ ጥቃቅን ድርጊቶች ነው። አዎን፣ በምንፈጽማቸው ድርጊቶች አማካኝነት ቀስ በቀስ አንድ ዓይነት ስም እናተርፋለን።
በአንጻሩ ደግሞ አለቦታው የገባ አንድ የብሩሽ ቅብ የአንድን ሥዕል ውበት ሊቀንስ ይችላል። ስማችንን በተመለከተም ጉዳዩ ተመሳሳይ ነው። ጠቢቡ ንጉሥ ሰሎሞን እንዲህ ሲል ተናግሯል:- “የሰው ስንፍና መንገዱን ታጣምምበታለች።” (ምሳሌ 19:3) በጥቂት ስንፍና የተነሣ የአንድ ሰው መልካም ስም ሊጠፋ ይችላል። ይህ ጥቂት ስንፍና ደግሞ አንዲት ቀን ተሳስቶ በቁጣ መገንፈል ወይም ከልክ በላይ ጠጥቶ መታየት ወይም ወሲባዊ ቅሌት መፈጸም ሊሆን ይችላል። (ምሳሌ 6:32፤ 14:17፤ 20:1) ስለዚህ መልካም ስም ለማትረፍ መጣራችንና ስማችን እንዳይጎድፍ ከፍተኛ ጥንቃቄ ማድረጋችን ምንኛ የተገባ ነው!—ከራእይ 3:5 ጋር አወዳድር።