የአንባብያን ጥያቄዎች
ዕብራውያን 12:4 ላይ የተገለጸው “ደምን እስከ ማፍሰስ ድረስ አልተቃወማችሁም” የሚለው ሐረግ ትርጉም ምንድን ነው?
“ደምን እስከ ማፍሰስ ድረስ አልተቃወማችሁም” የሚለው ሐረግ ቃል በቃል ደምን በማፍሰስ እስከ ሞት ድረስ መጽናትን ያመለክታል።
ሐዋርያው ጳውሎስ አንዳንድ ዕብራውያን ክርስቲያኖች በእምነታቸው ምክንያት የደረሰባቸውን ‘መከራ በትልቅ ተጋድሎ’ እንደተቋቋሙ ያውቅ ነበር። (ዕብራውያን 10:32, 33) ይህንንም ሲጠቁም ሩጫን፣ ነፃ ትግልን፣ ቦክስን እንዲሁም የዲስክና የጦር ውርወራን ጨምሮ በግሪክ የአትሌቲክስ ውድድር ወቅት የሚደረጉትን ውድድሮች የሚያመለክቱ ምሳሌያዊ ቃላት የተጠቀመ ይመስላል። በዚህም መሠረት በዕብራውያን 12:1 (አ.መ.ት ) ላይ ክርስቲያን ባልንጀሮቹን “ሸክም የሚሆንብንን ሁሉ፣ በቀላሉም ተብትቦ የሚይዘንን ኃጢአት አስወግደን በፊታችን ያለውን ሩጫ በጽናት እንሩጥ” በማለት አሳስቧቸዋል።—በሰያፍ የጻፍነው እኛ ነን።
ከዚያም ሦስት ቁጥሮች ወረድ ብሎ በዕብራውያን 12:4 ላይ ከሩጫ ውድድር ወደ ቦክስ ውድድር ዘወር ያለ ይመስላል። (ሁለቱም ምሳሌዎች በ1 ቆሮንቶስ 9:26 ላይ ይገኛሉ።) የጥንት ቦክሰኞች እጃቸውን በቆዳ ይጠቀልሉ ነበር። ቆዳዎቹ በተጋጣሚዎቹ ላይ ከፍተኛ ጉዳት እንዲያደርሱ ለማድረግ “በእርሳስ፣ በብረት ወይም እንደ ብረት ባሉ ማዕድናት” ይለበጡ ነበር። እንዲህ ዓይነቱ ጭካኔ የሞላበት ውድድር ከፍተኛ የደም መፋሰስን አንዳንዴም ሞትን እንኳ ሳይቀር ያስከትል ነበር።
ያም ሆነ ይህ የዕብራውያን ክርስቲያኖች የደረሰባቸውን ስደትና የጭካኔ ድርጊት እስከ ሞት ድረስ ማለትም ‘ደምን እስከ ማፍሰስ የተቃወሙ’ በርካታ ታማኝ የአምላክ አገልጋዮች ምሳሌ አለላቸው። ጳውሎስ የጥንቶቹ ታማኞች የደረሰባቸውን መከራ በተመለከተ በጥቅሱ ዙሪያ ያጎላውን ሐሳብ ተመልከት:-
“በድንጋይ ተወግረው ሞቱ፣ ተፈተኑ፣ በመጋዝ ተሰነጠቁ፣ በሰይፍ ተገድለው ሞቱ፣ ሁሉን እያጡ መከራን እየተቀበሉ እየተጨነቁ የበግና የፍየል ሌጦ ለብሰው ዞሩ።” ከዚያም የእምነታችንን ፈጻሚ ኢየሱስን በማጉላት “እርሱ ነውርን ንቆ . . . በመስቀል ታግሦ በእግዚአብሔር ዙፋን ቀኝ ተቀምጦአልና” ሲል ጻፈ።—ዕብራውያን 11:37፤ 12:2
አዎን፣ ‘ደምን እስከ ማፍሰስ የተቃወሙ’ ማለትም እስከ ሞት ድረስ የጸኑ በርካታ የአምላክ አገልጋዮች ነበሩ። ትግል ያደረጉት ውስጣዊ ከሆነው ከእምነት የማጣት ኃጢአት ጋር አልነበረም። ጭካኔ የተሞላበት ውጪያዊ ፈተና ቢደርስባቸውም እስከ ሞት ድረስ በመጽናት ለአምላክ ያላቸውን ታማኝነት ጠብቀዋል።
ምናልባትም የስደቱ ማዕበል ጋብ ካለ በኋላ የመጡት አዳዲሶቹ የኢየሩሳሌም ጉባኤ አባላት ይህን የመሰለ ከባድ ስደት አልደረሰባቸው ይሆናል። (ሥራ 7:54-60፤ 12:1, 2፤ ዕብራውያን 13:7) ሆኖም ቀለል ያሉ የእምነት ፈተናዎች አንዳንዶች ተስፋ በመቁረጥ ውድድሩን አቋርጠው እንዲወጡ አድርጓቸዋል፤ ‘በነፍሳቸው ዝለውና ደክመው’ ነበር። (ዕብራውያን 12:3) ወደ ጉልምስና ማደግ ነበረባቸው። ይህም አካላዊ ጥቃትን ጨምሮ ደምን እስከ ማፍሰስ ድረስ በመጽናት የሚደርስባቸውን ማንኛውንም ዓይነት ፈተና እንዲቋቋሙ ያስችላቸዋል።—ዕብራውያን 6:1፤ 12:7-11
በዘመናችንም በርካታ የአምላክ አገልጋዮች ለሞት የሚዳርጋቸው ቢሆንም ክርስቲያናዊ አቋማቸውን ለማላላት ባለመፍቀድ ‘ደምን እስከ ማፍሰስ ተቃውመዋል።’ በዕብራውያን 12:4 ላይ በሚገኙት የጳውሎስ ቃላት በፍርሃት ከመራድ ይልቅ ለአምላክ ታማኝ በመሆን ረገድ እስከ ምን ድረስ ለመሄድ እንደቆረጥን የሚጠቁሙ እንደሆኑ አድርገን ልንመለከታቸው ይገባል። ጳውሎስ ቆየት ብሎ ለዕብራውያን ክርስቲያኖች በጻፈው ተመሳሳይ ደብዳቤ ላይ የሚከተለውን ብሏል:- “በማክበርና በፍርሃት እግዚአብሔርን ደስ እያሰኘን የምናመልክበትን ጸጋ እንያዝ።”—ዕብራውያን 12:28