የአንባቢያን ጥያቄዎች
ኢየሱስ ክርስቶስ 12ቱን ሐዋርያት ለስብከት በላካቸው ወቅት በትር እንዲይዙና ጫማ እንዲያደርጉ ነግሯቸው ነበር?
አንዳንድ ሰዎች፣ ኢየሱስ ሐዋርያቱን ለስብከት እንደላካቸው የሚገልጹት ሦስቱ የወንጌል ዘገባዎች እርስ በርስ እንደሚጋጩ ይናገራሉ። ይሁንና እነዚህን ዘገባዎች ብናነጻጽራቸው ትኩረት የሚስብ መደምደሚያ ላይ እንደርሳለን። እስቲ መጀመሪያ ማርቆስና ሉቃስ የጻፉትን ዘገባ እናወዳድር። የማርቆስ ዘገባ እንዲህ ይላል፦ “[ኢየሱስ] ከበትር በስተቀር ለጉዟቸው ዳቦም ሆነ የምግብ ከረጢት እንዲሁም በኮሮጇቸው ገንዘብ እንዳይዙ አዘዛቸው። በተጨማሪም ጫማ እንዲያደርጉ ሆኖም ሁለት ልብስ እንዳይለብሱ ነገራቸው።” (ማር. 6:7-9) ሉቃስ ደግሞ “ለጉዟችሁ ምንም ነገር አትያዙ፤ በትርም ሆነ የምግብ ከረጢት፣ ዳቦም ሆነ የብር ገንዘብ እንዲሁም ሁለት እጀ ጠባብ አትያዙ” ሲል ጽፏል። (ሉቃስ 9:1-3) እነዚህ ጥቅሶች እንዲሁ ሲታዩ እርስ በርስ የሚጋጩ ይመስላሉ። ማርቆስ፣ ሐዋርያቱ በትር እንዲይዙና ጫማ እንዲያደርጉ እንደተነገራቸው የገለጸ ሲሆን ሉቃስ ግን ለጉዟቸው ምንም ነገር ሌላው ቀርቶ በትር እንኳ እንዳይዙ መመሪያ እንደተሰጣቸው ጽፏል። ከማርቆስ በተቃራኒ ሉቃስ ስለ ጫማ ምንም የተናገረው ነገር የለም።
ኢየሱስ በዚያ ወቅት ሊያስተላልፍ የፈለገው መልእክት ምን እንደነበር ለመረዳት በሦስቱም የወንጌል ዘገባዎች ላይ የሚገኘውን ተመሳሳይ አገላለጽ እንመልከት። ከላይ በተገለጹት ዘገባዎችም ሆነ በማቴዎስ 10:5-10 ላይ ሐዋርያቱ “ሁለት ልብስ” እንዳይለብሱ ወይም እንዳይዙ ተነግሯቸው ነበር። ሁሉም ሐዋርያት አንድ አንድ ልብስ ለብሰው መሆን አለበት። በመሆኑም ለጉዟቸው ሌላ ልብስ እንዳይዙ ተነግሯቸዋል። በተመሳሳይም ቀድሞውንም ቢሆን ጫማ አድርገው ነበር። ለጉዟቸው የሚሆን ሌላ ጫማ መያዝ አልነበረባቸውም። ተጨማሪ በትር መያዝን በተመለከተስ ምን ማለት ይቻላል? ዘ ጂዊሽ ኢንሳይክሎፒዲያ እንዲህ ይላል፦ “የጥንቶቹ ዕብራውያን በአብዛኛው በትር የመያዝ ልማድ የነበራቸው ይመስላል።” (ዘፍ. 32:10) ሐዋርያቱ፣ ኢየሱስ መመሪያውን በሰጣቸው ወቅት ይዘውት ከነበረው በትር “በስተቀር ለጉዟቸው” ምንም ተጨማሪ ነገር መያዝ እንደሌለባቸው ማርቆስ ገልጿል። የወንጌል ጸሐፊዎች፣ ሐዋርያቱ ለጉዟቸው የሚሆኑ ተጨማሪ ነገሮች ለመያዝ ሲሉ እንዳይዘገዩ ኢየሱስ የሰጠውን ትእዛዝ ማጉላታቸው ነበር።
ኢየሱስ ይህን ትእዛዝ በሰጠበት ወቅት በቦታው የነበረው ማቴዎስ የጻፈው ዘገባ ይህንን ነጥብ ይበልጥ ያጎላል። ኢየሱስ እንዲህ ብሏል፦ “በመቀነታችሁ ወርቅ ወይም ብር ወይም መዳብ አትያዙ፤ ወይም ለጉዞ የምግብ ከረጢት ወይም ሁለት ልብስ ወይም ትርፍ ጫማ ወይም በትር አትያዙ፤ ምክንያቱም ለሠራተኛ ምግቡ ይገባዋል።” (ማቴ. 10:9, 10) ሐዋርያቱ አድርገውት የነበረውን ጫማ እንዲሁም በእጃቸው የያዙትን በትር በተመለከተስ ምን ማለት ይቻላል? ኢየሱስ ያዘዛቸው ተጨማሪ ነገር እንዳይዙ እንጂ የያዙትን እንዲተዉ አልነበረም። እንዲህ ያለ መመሪያ የሰጣቸው ለምን ነበር? “ምክንያቱም ለሠራተኛ ምግቡ ይገባዋል።” ኢየሱስ የሰጣቸው ትእዛዝ ፍሬ ነገር ይህ ሲሆን በተራራው ስብከቱ ላይ ከሰጠው ምክር ጋር የሚስማማ ነው፤ በዚያ ወቅትም ስለሚበሉት፣ ስለሚጠጡት ወይም ስለሚለብሱት ነገር እንዳይጨነቁ ነግሯቸው ነበር።—ማቴ. 6:25-32
የወንጌል ዘገባዎቹ መጀመሪያ ላይ እርስ በርስ የሚጋጩ ቢመስሉም ሁሉም የሚያስተላልፉት ተመሳሳይ ሐሳብ ነው። ሐዋርያቱ የያዙትን ይዘው መሄድ እንጂ ተጨማሪ ነገር ለማግኘት ሲሉ ትኩረታቸው እንዲከፋፈል መፍቀድ አልነበረባቸውም። ለምን? ምክንያቱም የሚያስፈልጋቸውን ይሖዋ ይሰጣቸዋል።
ሰለሞን የጠቀሳቸው “እጅግ የበዙ ሴቶች” እነማን ናቸው?—መክ. 2:8 የ1954 ትርጉም
በእርግጠኝነት መናገር ባይቻልም ሰለሞን በቤተ መንግሥቱ ውስጥ የተቀበላቸው ትልቅ ቦታ የነበራቸው ሴቶች ሊሆኑ ይችላሉ።
በመክብብ ምዕራፍ 2 ላይ ሰለሞን ሰፋፊ የግንባታ ፕሮጀክቶቹን ጨምሮ ያከናወናቸውን በርካታ ነገሮች ጠቅሷል። አክሎም እንዲህ ብሏል፦ “ለራሴም ብርንና ወርቅን፣ የነገሥታትና የአውራጃዎችን ሀብት አካበትሁ፤ ወንድና ሴት አዝማሪዎች፣ የሰው መደሰቻ የሆኑ ቅምጦች [“እጅግ የበዙ ሴቶች፣” የ1954 ትርጉም] ነበሩኝ።”—መክ. 2:8
በርካታ ተንታኞች፣ ሰለሞን የጠቀሳቸው “እጅግ የበዙ ሴቶች” ከጊዜ በኋላ የሰበሰባቸውንና የሐሰት አምልኮ እንዲከተል ያደረጉትን በርካታ የባዕድ አገር ሚስቶችና ቁባቶች እንደሚያመለክቱ ይናገራሉ። (1 ነገ. 11:1-4) ይሁንና እንዲህ ያለው ማብራሪያ አያስኬድም። ሰለሞን ከላይ ያለውን ሐሳብ ሲጽፍ “እጅግ የበዙ ሴቶች” ብሎ የጠራቸውን ሴቶች ያውቃቸው ነበር። እንዲሁም በዚያ ወቅት የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍል የሆኑትን መጻሕፍት እንዲጽፍ አምላክ በመንፈሱ ይመራው ስለነበር የይሖዋን ሞገስ አላጣም ነበር። በመቶዎች የሚቆጠሩ የባዕድ አገር ሚስቶችና ቁባቶች በነበሩትና የሐሰት አምልኮን በተከተለበት ወቅት ግን የይሖዋን ሞገስ አጥቶ ነበር።
በመክብብ መጽሐፍ ላይ ሰለሞን ‘ትክክለኛውን ቃል ለማግኘት እንደተመራመረና የጻፈውም ቅንና እውነት እንደነበር’ ገልጿል። (መክ. 12:10) “ሚስት፣” ‘ንግሥት’ እና ‘ቁባት’ የሚሉትን ቃላት በመንፈስ መሪነት በጻፋቸው መጻሕፍት ውስጥ ስለተጠቀመባቸው እንዲህ ዓይነት ቦታ ያላቸውን ሴቶች ለማመልከት የሚያገለግሉትን ቃላት ያውቅ እንደነበር ግልጽ ነው። (ምሳሌ 5:18፤ 12:4፤ 18:22፤ መክ. 9:9፤ ማሕ. 6:8, 9) ይሁንና በመክብብ 2:8 ላይ እነዚህን የታወቁ ቃላት አልተጠቀመም።
በመክብብ 2:8 ላይ “እጅግ የበዙ ሴቶች” ተብሎ የተተረጎመው የዕብራይስጥ ቃል በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ የሚገኘው አንድ ጊዜ ብቻ ነው። ምሑራን የዚህ ቃል ትርጉም በእርግጠኝነት እንደማይታወቅ ይስማማሉ። ብዙ የመጽሐፍ ቅዱስ ተርጓሚዎች በመክብብ 2:8 ላይ የሚገኘው ሐረግ በርካታ ሴቶችን እንደሚያመለክት ይናገራሉ።
ሰለሞን ዝናው በጣም ከመግነኑ የተነሳ፣ ባለጸጋ የሆነው የሳባ መንግሥት ንግሥት ስለ እሱ ሰምታ ልትጎበኘው ሄዳ ነበር፤ እሷም ባየችው ነገር በጣም ተደንቃ ነበር። (1 ነገ. 10:1, 2) ይህ ሁኔታ ሰለሞን “እጅግ የበዙ ሴቶች” ያለው ማንን ሊሆን እንደሚችል ፍንጭ ይሰጠናል። የአምላክን ሞገስ ከማጣቱ በፊት በነበሩት በርካታ ዓመታት በቤተ መንግሥቱ ውስጥ የተቀበላቸውን ትልቅ ቦታ ያላቸው ሴቶች መጥቀሱ ሊሆን ይችላል።