የይሖዋ መንፈስ ይደግፈናል
1 የይሖዋ ምሥክሮች እንደመሆናችን መጠን ተወዳዳሪ የማይገኝለት ታላቅ ሥራ ተሰጥቶናል። ኢየሱስ “አስቀድሞም ወንጌል ለአሕዛብ ሁሉ ይሰበክ ዘንድ ይገባል” ብሏል። (ማር. 13:10) በሰብዓዊ አመለካከት ሲታይ ይህ የሚቻል አይመስልም። ሆኖም ይቻላል። በአጽናፈ ዓለም ውስጥ ተወዳዳሪ የማይገኝለት እጅግ ከፍተኛ የሆነ ኃይል ማለትም የአምላክ መንፈስ ድጋፍ ይሰጠናል።—ማቴ. 19:26
2 የመጀመሪያው መቶ ዘመን ማስረጃ፦ ኢየሱስ የኢሳይያስ ትንቢት በእርሱ ላይ ተፈጻሚነቱን እንደሚያገኝ በመግለጽ ‘ወንጌልን እሰብክ ዘንድ የጌታ መንፈስ በእኔ ላይ ነው’ በማለት ተናግሯል። (ሉቃስ 4:17, 18) “እስከ ምድር ዳርም ድረስ” ለመመሥከር የሚያስችላቸውን የመንፈስ ቅዱስን ኃይል እንደሚቀበሉ ኢየሱስ ወደ ሰማይ ከማረጉ በፊት ለደቀ መዛሙርቱ ነግሯቸው ነበር። በዚህም መሠረት ፊልጶስ በመንፈስ ቅዱስ ተመርቶ ለኢትዮጵያዊው ባለ ሥልጣን ሰብኳል፤ ጴጥሮስ ወደ ሮማዊው መኮንን እንዲሄድ መንፈስ ቅዱስ ልኮታል፤ እንዲሁም ጳውሎስና በርናባስ ለአሕዛብ እንዲሰብኩ መንፈስ ቅዱስ ልኳቸዋል። እነዚህ የተለያየ አስተዳደግና ሁኔታ የነበራቸው ሰዎች እውነትን ይቀበላሉ ብሎ የገመተ ማን ነበር? ይሁን እንጂ እውነትን ተቀብለዋል።—ሥራ 1:8፤ 8:29-38፤ 10:19, 20, 44-48፤ 13:2-4, 46-48
3 በዘመናችን የሚገኝ ማስረጃ፦ መንፈስ ቅዱስ በጊዜያችን እየተከናወነ ባለው የስብከት ሥራ ውስጥ ያለውን ድርሻ አስመልክቶ የራእይ መጽሐፍ “መንፈሱና ሙሽራይቱም:- ና ይላሉ። . . . የወደደም የሕይወትን ውኃ እንዲያው ይውሰድ” በማለት ይገልጻል። (ራእይ 22:17) መንፈሱ የክርስቶስ የሙሽራ ክፍልና ባልደረቦቻቸው የሆኑት “ሌሎች በጎች” ለሁሉም ሰዎች ምሥራቹን እንዲሰብኩ ያነሳሳቸዋል። (ዮሐ. 10:16) በምንሰብክበት ጊዜ ደፋሮች መሆን ይኖርብናል፤ የአምላክ መንፈስ እንደሚደግፈን በመተማመን ምንም ሳናመነታ ሁሉንም ዓይነት ሰዎች ቀርበን ማነጋገር ይኖርብናል። የአምላክ መንፈስ ለአገልጋዮቹ ድጋፍ መስጠቱን እንዳላቆመ የ1998 የዓመት መጽሐፍ አሳማኝ የሆኑ ማስረጃዎችን ያቀርባል። የተገኘውን ውጤት ተመልከቱ! ባለፉት ሁለት የአገልግሎት ዓመታት ወቅት በየቀኑ በአማካይ ከ1,000 የሚበልጡ ሰዎች ተጠምቀዋል።
4 ይሖዋ እስከ ፈቀደ ድረስ የመንግሥቱን መልእክት በምንሰብክበት ጊዜ የአምላክ መንፈስ ድጋፍ መስጠቱን እንደሚቀጥል እርግጠኞች ሁኑ። ይህን ማወቃችን እጅግ አስፈላጊ በሆነው የመንግሥቱ ሥራ በሙሉ ኃይላችን መሳተፋችንን እንድንቀጥል ሊያበረታታንና ሊያነሳሳን ይገባል።—1 ጢሞ. 4:10