የይሖዋን ስም በምድር ዙሪያ ማሳወቅ
1 ኢየሱስ ለደቀ መዛሙርቱ ‘እስከ ምድር ዳር ድረስ’ ምስክሮቹ የመሆንን ተልዕኮ የሰጠው ራሱ አስቀድሞ ምሳሌ በመሆን ነው። (ሥራ 1:8) በማንኛውም ጊዜና ቦታ ሰዎችን ሲያገኝ አምላክ ለሰው ዘር ያለውን ዓላማ ይነግራቸው ነበር። የኢየሱስን ምሳሌ በመከተል የታማኙ ባሪያ ክፍል የይሖዋ ስም “በምድር ሁሉ ላይ” እንዲታወቅ ለማድረግ የተለያዩ መንገዶችን በመጠቀም ላይ ይገኛል።—ኢሳ. 12:4, 5
2 በቀደሙት ዓመታት የተከናወኑት ነገሮች፦ በቀደሙት ዓመታት ለሕዝብ የቀረቡት ንግግሮች በጋዜጦች ላይ ታትመው ይወጡ ነበር። “የፍጥረት ፎቶ ድራማ” የተባለ ፊልም ተዘጋጅቶ በሚልዮን የሚቆጠሩ ሰዎች እንዲያዩት ተደርጓል። የድምፅ መሣሪያ የተገጠመላቸው መኪናዎች እንዲሁም የሸክላ ማጫወቻ መሣሪያዎችና ለተወሰነ ጊዜ ደግሞ ራዲዮ በሰፊው ጥቅም ላይ ውለዋል። ይህ ሁሉ የምሥራቹን ለመስበክ ሲባል የተደረገ ነው። እርግጥ ፍላጎት ያሳዩ ሰዎችን ተከታትሎ መርዳት እንዲቻል ፊት ለፊት አግኝቶ ማነጋገሩ አጽንኦት ሲሰጠው የኖረ ጉዳይ ነው። በመሆኑም ከቤት ወደ ቤት የሚደረገው አገልግሎት የይሖዋ ስም በሁሉም ስፍራ እንዲታወቅ ለማድረግ የሚያስችል ውጤታማ መንገድ መሆኑ ተረጋግጧል።—ሥራ 5:42
3 በዛሬው ጊዜ በመከናወን ላይ ያለው ሥራ፦ ዘመኑ እየተለወጠ በመምጣቱ ዓለም ሩጫ የበዛበት ሆኗል። በመሆኑም በብዙ ቦታዎች ሰዎችን ቤታቸው ማግኘት አስቸጋሪ ሆኗል። መንፈሳዊ ነገሮችን ለማንበብና ለማሰላሰል ጊዜ የሚመድቡ ጥቂቶች ናቸው። ይህ በመሆኑ እኛም አገልግሎታችንን እንደ ሁኔታው መለዋወጥ ይገባናል። የአገልግሎት ክልላችንን ከቤት ወደ ቤት በመሄድ በተደጋጋሚ ከመሸፈን በተጨማሪ ሰዎች ወደሚገኙበት ቦታ እንድንሄድና በእኛ ስላለው ተስፋ መልስ ለመስጠት “ዘወትር የተዘጋጀን” እንድንሆን ማበረታቻ ተሰጥቶናል። (1 ጴጥ. 3:15) ይህ ማለት ለሥራ ባልደረቦቻችን፣ አብረውን ለሚማሩ፣ በመንገድ ላይ በመናፈሻ ቦታዎች እንዲሁም በመኪና ማቆሚያ ቦታዎች ለምናገኛቸው ከሱቅ ወደ ሱቅ እንዲሁም በማንኛውም ቦታ ሰዎችን ስናገኝ ለመስበክ ጥረት ማድረግ አለብን ማለት ነው። ይሖዋ ስለሚረዳን ጥረታችን መልካም ውጤት ይኖረዋል። አንተስ ሰዎች በሚገኙበት ቦታ ሁሉ ምስክርነት ለመስጠት በሚደረገው ሥራ የበኩልህን እያደረግህ ነውን?
4 በአገልግሎት ክልላችን ውስጥ የሚገኙ ሰዎች የይሖዋን ስም እንዲያውቁ ለመርዳት ስንል በግለሰብ ደረጃ የቻልነውን ሁሉ እናድርግ። ይሖዋ ልበ ቅን ሰዎችን ወደ እርሱ እንደሚስባቸው በመተማመን አገልግሎታችንን ሙሉ በሙሉ የምንፈጽም ከሆነ ከፍተኛ እርካታ እናገኛለን።—ዮሐ. 6:44