ብርታት ለማግኘት በይሖዋ ታመኑ
1 በይሖዋ መታመን አስፈላጊ የሆነባቸው በርካታ ምክንያቶች አሉ። ምሥራቹን ‘በዓለም ዙሪያ’ መስበክ ፈታኝ ሥራ ነው። (ማቴ. 24:14) ፍጽምና ከጎደለው ሥጋችን ጋር የማያቋርጥ ውጊያ አለብን። (ሮሜ 7:21-23) በተጨማሪም ከሰብዓዊ ፍጡር በላይ ከሆኑ ‘ከዚህ የጨለማ ዓለም ገዢዎች’ ጋር እንታገላለን። (ኤፌሶን 6:11, 12) በግልጽ ለማየት እንደሚቻለው እርዳታ ያስፈልገናል። ታዲያ ከይሖዋ ብርታት ማግኘት የምንችለው እንዴት ነው?
2 በጸሎት:- ይሖዋ ለሚጠይቁት ሁሉ ከፍተኛ ኃይል ያለውን ቅዱስ መንፈሱን አትረፍርፎ ይሰጣቸዋል። (ሉቃስ 11:13) ከቤት ወደ ቤት፣ በመንገድ ላይ ወይም በስልክ በመመሥከር ችሎታህ የመተማመን ስሜት ይጐድልሃል? መደበኛ ባልሆነ መንገድ ለመመሥከር ፍርሃት ይሰማሃል? በክልሉ ውስጥ ያሉት ሰዎች ግዴለሽነት ቅንዓትህን ቀንሶታል? እምነትህን ወይም የጸና አቋምህን እንድታላላ ተጽዕኖ ቢያጋጥምህስ? በይሖዋ ተማመን። ብርታት እንዲሰጥህ ጸልይ።—ፊልጵ. 4:13
3 በግል ጥናት:- ሰብዓዊ ምግብ በመመገብ ጥንካሬ እንደምናገኝ ሁሉ የአምላክን ቃልና “ታማኝና ልባም ባሪያ” የሚያዘጋጃቸውን ጽሑፎች አዘውትረን በመመገብ በመንፈሳዊ ጠንካሮች እንሆናለን። (ማቴ. 4:4፤ 24:45) ስታንሊ ጆንስ በቻይና ያለምንም መጽሐፍ ቅዱስ ለዓመታት ብቻውን ታስሮ በነበረበት ወቅት ለመጽናት የሚያስችል ብርታት የሰጠው ምን እንደሆነ ተጠይቆ ሲመልስ እንዲህ ብሏል:- “በእምነት ጸንተን መቆም እንችላለን። እርግጥ ነው ቀደም ብለን ያጠናነው ነገር መኖር አለበት። ያለዚያ ምንም ውስጣዊ ጥንካሬ ሊኖረን አይችልም።”
4 በስብሰባ በመገኘት:- በመጀመሪያው መቶ ዘመን በተደረገ አንድ ክርስቲያናዊ ስብሰባ ላይ ይሁዳና ሲላስ “ወንድሞችን በብዙ ቃል መክረው አጸኑአቸው [“አበረቷቸው፣” NW ]።” (ሥራ 15:32) ዛሬም በተመሳሳይ በስብሰባዎች ላይ የምናዳምጠው ትምህርት ለይሖዋ ጥልቅ አድናቆት እንዲኖረን ያደርጋል፣ እምነታችንን ይገነባል እንዲሁም ለአገልግሎት ያነቃቃናል። ስብሰባዎች ‘ሊያጽናኑን [‘ሊያበረቱን፣’ NW ]’ ከሚችሉት ‘በእግዚአብሔር መንግሥት አብረውን ከሚሠሩት’ ጋር አዘውትረን እንድንገናኝ ያደርጉናል።—ቆላ. 4:11
5 በዚህ “የሚያስጨንቅ ዘመን” ውስጥ ስንኖር እርዳታ ያስፈልገናል። (2 ጢሞ. 3:1) ከይሖዋ ብርታት የሚያገኙትን በተመለከተ “እንደ ንስር በክንፍ ይወጣሉ፤ ይሮጣሉ፣ አይታክቱም፤ ይሄዳሉ፣ አይደክሙም” የሚል ማረጋገጫ ተሰጥቶናል።—ኢሳ. 40:31