ሁሉም ዓይነት ሰዎች ይድናሉ
1. በአምላክ ዘንድ መልካም ስም ማትረፋችን የተመካው በምን ላይ ነው?
1 የአምላክ ይገባናል የማንለው ደግነት የመዳንን መንገድ ከፍቶልናል። የይሖዋ ፈቃድ “ሰዎች ሁሉ እንዲድኑና እውነትን ወደ ማወቅ እንዲደርሱ” ነው። (1 ጢሞ. 2:3, 4) በአምላክ ዘንድ መልካም ስም ማትረፋችን የተመካው በዘራችን፣ በማኀበረሰቡ ውስጥ ባለን ቦታ፣ በችሎታችን ወይም በውጫዊ ቁመናችን ሳይሆን በኢየሱስ ቤዛዊ መሥዋዕት ላይ እምነት በማሳደራችን ነው። (ዮሐ. 3:16, 36) ከአምላክ ጋር የምንሠራ እንደመሆናችን መጠን ይሖዋ ሊቀበላቸው የፈቀደውን ሰዎች ላለመቀበል በልባችን ላይ ተጽዕኖ ሊያሳድርብን የሚችል ማንኛውንም የአድሏዊነት ስሜት ማስወገድ ይገባናል።
2, 3. ውጫዊ ገጽታቸውን ተመልክተን በሰዎች ላይ እንዳንፈርድ ምን ሊረዳን ይችላል?
2 ከመፍረድ ተቆጠቡ:- ይሖዋ ያለ ምንም ጥላቻ እና አድልዎ የሰዎችን ልብ ያያል። (1 ሳሙ. 16:7) እርሱ አቅማቸውንም ከግምት ያስገባል። በመሆኑም እርሱን ለማስደሰት የሚፈልጉትን ሰዎች የተመረጡ አድርጎ ይመለከታቸዋል። (ሐጌ 2:7) ለሌሎች የአምላክ ዓይነት አመለካከት አለን?
3 በአገልግሎት ላይ የሚያጋጥሙን የአንዳንድ ሰዎች ውጫዊ ገጽታ የሚያስፈራ ሊሆን ይችላል። አለባበሳቸው የተዝረከረከ ወይም ጨዋነት የጎደለው አሊያም ጸጉራቸው የተንጨፈረረ ይሆናል። አንዳንዶች ጎዳና ተዳዳሪ ሊሆኑ ይችላሉ። ሌሎች ደግሞ ያመናጭቁን ይሆናል። እንደነዚህ ያሉት ሰዎች በፍጹም የይሖዋ አምላኪዎች አይሆኑም ብሎ ከመፍረድ ይልቅ “ቀደም ሲል እኛ ራሳችን ማስተዋል የጐደለን፣ የማንታዘዝ፣ የተታለልን” እንደነበርን በማስታወስ አዎንታዊ አመለካከት መያዝ ይገባናል። (ቲቶ 3:3) ይህን መገንዘባችን ውጫዊ ሁኔታቸው የማይስብ የሆኑትን ጨምሮ ለማንኛውም ሰው ለመስበክ ጉጉት ያሳድርብናል።
4, 5. ኢየሱስ እና ጳውሎስ ከተዉልን ምሳሌ ምን እንማራለን?
4 የመጀመሪያው መቶ ዘመን ምሳሌዎች:- ኢየሱስ ክርስቶስ በሌሎች ዘንድ ተስፋ የላቸውም ተብለው የተተዉትን ግለሰቦች ለመርዳት ጊዜውን ይሠዋ ነበር። (ሉቃስ 8:26-39) ኢየሱስ መጥፎ ድርጊቶችን ችላ ብሎ የማያልፍ ቢሆንም ሰዎች በመጥፎ የአኗኗር ዘይቤ ሊጠመዱ እንደሚችሉ ያውቃል። (ሉቃስ 7:37, 38, 44-48) ስለዚህ ያሉበትን ሁኔታ በመረዳት ‘እረኛ እንደሌላቸው በጎች ስለ ነበሩ አዘነላቸው።’ (ማር. 6:34) የእርሱን ምሳሌ በተሟላ ሁኔታ መኮረጅ እንችላለን?
5 ሐዋርያው ጳውሎስ በድንጋይ ተወግሯል፣ ተደብድቧል እንዲሁም ወህኒ ተጥሏል። (ሥራ 14:19፤ 16:22, 23) እንዲህ ዓይነት አስከፊ ሁኔታ የገጠመው መሆኑ እንዲማረርና ለአንዳንድ ብሔራትና ጎሣዎች መስበክ ከንቱ ልፋት ነው ብሎ እንዲደመድም አድርጎታል? በፍጹም። ቅን ልብ ያላቸው ሰዎች በሁሉም ጎሣዎች ውስጥ እንደሚገኙ ስለሚያውቅ እነርሱን ለማግኘት ቆርጦ ተነስቶ ነበር። እኛስ በአገልግሎት ክልላችን ለምናገኛቸው የተለያየ አስተዳደግና ባሕል ላላቸው ሰዎች ተመሳሳይ አመለካከት አለን?
6. በጉባኤ ስብሰባዎች ላይ ለምናገኛቸው አዲስ ሰዎች ያለን አቀራረብ ምን ውጤት ሊያስገኝ ይችላል?
6 በዘመናችን ለሌሎች ጥሩ አቀባበል ማድረግ:- አብዛኞቹ የአምላክ ሕዝቦች ቀደም ሲል ወደ ጉባኤ ሲመጡ የሚጋብዝ ዓይነት አለባበስና አቋም ያልነበራቸው ቢሆንም ወንድሞችና እህቶች ወዳጃዊ አቀባበል ስላደረጉላቸው ደስተኞች ናቸው። ጀርመን ውስጥ፣ የተንጨባረረ ጺምና ረጅም ጸጉር ያለው እንዲሁም ቆሻሻ ልብስ የለበሰ አንድ ሰው ወደ አንድ የመንግሥት አዳራሽ መጣ። ግለሰቡ መጥፎ ስም ያተረፈ ሰው ነበር። የሆነ ሆኖ በስብሰባው ቦታ ላይ ጥሩ አቀባበል ተደረገለት። በሁኔታው በጣም ስለተደነቀ ከሳምንት በኋላ ተመልሶ መጣ። ከዚያም በጥቂት ጊዜ ውስጥ አለባበሱንና አበጣጠሩን አስተካከለ፣ ሲጋራ ማጨስ አቆመ እንዲሁም ከሴት ጓደኛው ጋር የነበረውን ግንኙነት ሕጋዊ አደረገ። ብዙም ሳይቆይ ባልና ሚስቱ ከሁለት ልጆቻቸው ጋር ሆነው ይሖዋን ማምለክ ጀመሩ።
7. የማያዳላውን አምላካችንን መምሰል የምንችለው እንዴት ነው?
7 የማያዳላውን አምላካችንን በመምሰል ሁሉም ሰው ይገባናል ከማንለው የአምላክ ደግነት ተጠቃሚ እንዲሆን ግብዣውን ማቅረባችንን እንቀጥል።
[ከገጽ 5 የተቀነጨበ ሐሳብ ]
“እግዚአብሔር ለማንም [አያዳላም] . . . ነገር ግን እርሱን የሚፈሩትንና ጽድቅን የሚያደርጉትን ሁሉ ከየትኛውም ወገን ቢሆኑ ይቀበላቸዋል።”—ሥራ 10:34, 35