ይህን ያውቁ ኖሯል?
በመጀመሪያው መቶ ዘመን የቤተ መቅደሱ ካህናት መሥዋዕት ሆነው የሚቀርቡትን እንስሳት ደም የሚያስወግዱት እንዴት ነበር?
በጥንቷ እስራኤል የነበሩ ካህናት በየዓመቱ በሺዎች የሚቆጠሩ እንስሳትን በቤተ መቅደሱ መሠዊያ ላይ መሥዋዕት አድርገው ያቀርቡ ነበር። በመጀመሪያው መቶ ዘመን የኖረው አይሁዳዊው የታሪክ ጸሐፊ ጆሴፈስ እንደገለጸው በፋሲካ በዓል ወቅት ከ250,000 የሚበልጡ በጎች መሥዋዕት ሆነው ይቀርቡ ነበር፤ በዚህም የተነሳ በጣም ብዙ ደም ይፈስ ነበር። (ዘሌ. 1:10, 11፤ ዘኁ. 28:16, 19) ታዲያ ይህ ሁሉ ደም ምን ይሆናል?
የአርኪኦሎጂ ባለሙያዎች የሄሮድስ ቤተ መቅደስ የተደራጀ የፍሳሽ ማስወገጃ ሥርዓት እንደነበረው ደርሰውበታል፤ የፍሳሽ ማስወገጃው ቤተ መቅደሱ በ70 ዓ.ም. እስከጠፋበት ጊዜ ድረስ ጥቅም ላይ ውሏል። ይህ የፍሳሽ ማስወገጃ በቤተ መቅደሱ የሚፈሰውን ደም ለማስወገድ ይውል እንደነበር ከሁኔታዎች መረዳት ይቻላል።
የመሠዊያው ንጽሕና እንዲጠበቅ አስተዋጽኦ ያበረከቱ ሁለት ነገሮችን እስቲ እንመልከት፦
መሠዊያው ሥር ያሉ ቀዳዶች፦ የአይሁዳውያንን የቃል ሕጎች አሰባስቦ የያዘውና በሦስተኛው መቶ ዘመን ዓ.ም. መጀመሪያ አካባቢ የተጻፈው ሚሽና የመሠዊያውን የፍሳሽ ማስወገጃ አስመልክቶ ይናገራል። እንዲህ የሚል ሐሳብ ይዟል፦ “በስተ ደቡብ ምዕራብ ባለው ጥግ ላይ ሁለት ቀዳዶች ነበሩ፤ ከምዕራብና ከደቡብ አቅጣጫ የሚፈሰው ደም በቀዳዶቹ በኩል ይወርድና በውኃ መውረጃ ቦዩ አማካኝነት ወደ ቄድሮን ወንዝ ይገባል።”
በዘመናችን ያሉ የአርኪኦሎጂ ባለሙያዎችም በመሠዊያው ጥግ “ቀዳዶች” እንደነበሩ ይስማማሉ። ዘ ካምብሪጅ ሂስትሪ ኦቭ ጁዳይዝም የተባለው መጽሐፍ በቤተ መቅደሱ አቅራቢያ “የተደራጀ የፍሳሽ ማስወገጃ ሥርዓት” መገኘቱን ያረጋግጣል። መጽሐፉ ስለ ፍሳሽ ማስወገጃ ሥርዓቱ ሲናገር እንዲህ ይላል፦ “ከቤተ መቅደሱ የሚወጣውን ውኃና የተሠዉ እንስሳት ደም ለማስወገድ ይውል የነበረ ይመስላል።”
በቂ የውኃ አቅርቦት፦ ካህናቱ የመሠዊያውንና የፍሳሽ መተላለፊያ ቦዩን ንጽሕና ለመጠበቅ ብዙ ውኃ ያስፈልጋቸው ነበር። ካህናቱ ይህን ወሳኝ ሥራ ለማከናወን ከከተማው በቂ ንጹሕ ውኃ በቋሚነት ያገኙ ነበር። የውኃ አቅርቦቱን ለማሳለጥ የሚያገለግሉ ቦዮች፣ የውኃ ማጠራቀሚያዎች፣ ጉድጓዶችና ገንዳዎች ነበሩ። ጆሴፍ ፓትሪክ የተባሉት የአርኪኦሎጂ ባለሙያ እንዲህ ብለዋል፦ “እንዲህ ያለ የተደራጀ የውኃ አቅርቦት፣ የጽዳትና የፍሳሽ ማስወገጃ ሥርዓት ያለው ቤተ መቅደስ ለዘመኑ እጅግ አስደናቂ ነው።”