“ዓይናችሁን ግለጡና እዩ”
ልጆቻችሁ የሚያዩት ምንድን ነው? ጦርነት? ወንጀል? ብክለት? ድህነት? ሕመም? በእርግጥ እነዚህ ምንጊዜም ያሉ ነገሮች ናቸው። ይሁን እንጂ ልጆቻችሁ መጽሐፍ ቅዱስ ላይ የተጠቀሰውን አስደናቂ የወደፊት ተስፋ አሻግረው እንዲመለከቱ ተምረዋል? የዘጠኝ ዓመት ልጅ የሆነው የጆኤል ፒርሰን ወላጆች ይህን አድርገዋል። ውጤቱ ምን ነበር?
ጆኤል “ዓይናችሁን ግለጡና እዩ” በሚል ርዕስ የጻፈውን ተመልከቱ። ይህ ርዕስ በዩ ኤስ ኤ በቨርጂኒያ አውራጃ በሚገኝ አንድ ትምህርት ቤት ውስጥ ለሚማሩ ወጣቶች የቀረበ የጽሑፍ ውድድር ነበር። በነሐሴ 22, 1996 ዘ ሴንትራል ቨርጂኒያ በተባለ ጋዜጣ ላይ ታትሞ የወጣው የጆኤል ድርሰት ከአምላክ ቃል በተማረው ተስፋ ላይ የተመሠረተ መሆኑን እንዴት እንደሚያሳይ ተመልከት። እንዲህ ሲል ጽፏል:-
“ዓይናችሁን ግለጡና ምን ዓይነት ውበት እንደሚኖር እዩ።
“አንድ ቀን ጠዋት ከእንቅልፋችሁ ስትነሱ አካባቢን የሚበክል ነገር መወገዱን ስታውቁ ደስ አይላችሁም? ስለ ግድያና ወንጀል በሚነገሩ የዜና ዘገባዎች ምትክ የሰው ልጆች ሕይወት ሰላምና ደስታ የሰፈነበት ይሆናል።
“ጎረቤቶች የአንድ ጓደኛቸውን ቤት በሕብረት እየሠሩ ናቸው። በአቅራቢያው የሚገኙ ሌሎች ሰዎች የአትክልት ቦታቸውን ሲያለሙ ይታያሉ። እነዚህ ጎረቤታሞች እንዲህ አንድ ላይ ተባብረው የሚሠሩት በትክክለኛ የልብ ግፊት ተነሳስተው ነው። አንዱ ሌላውን ለመርዳት ይተባበራል። ድህነት የሚባል ነገር አይኖርም፤ ለሁሉም የሚዳረስ በቂ ምግብ ይኖራል። በዓለም ዙሪያ አንድነትና ሰላም ይሰፍናል። ወደፊት ማንም ሰው እንደገና አይራብም ወይም አይታመምም። ሁሉም ሰው ለእይታ ማራኪ የሆነ አካባቢ ይኖረዋል፤ እንዲሁም ተመልከቱ፣ አንድ ልጅ በነብር ጀርባ ላይ ተቀምጦ ይጋልባል! ነብሩ ብቻ ሳይሆን ሁሉም እንስሳት ከሰዎች ጋር በሰላም ይኖራሉ።
“እኔ መኖር የምፈልገው ይህን በመሰለው አካባቢ ነው። ከእኔ ጋር በዚያ ለመኖር ትፈልጋላችሁ?”
ወጣቱ ጆኤል እዚህ ላይ የገለጻቸውን ዓይነት በረከቶች ለማምጣት በእርግጥ አምላክ ተስፋ ሰጥቷልን? በእርግጥ ሰጥቷል! እባክህ መጽሐፍ ቅዱስህን ግለጥና ቀጥሎ በሚገኙት ጥቅሶች ላይ እነዚህን በረከቶች አስመልክቶ የተገለጹትን ሐሳቦች አንብብ:- መዝሙር 46:8, 9፤ 67:6፤ 72:16፤ ኢሳይያስ 2:3, 4፤ 11:6-9፤ 33:24፤ 65:17-25፤ ማቴዎስ 6:9, 10፤ 2 ጴጥሮስ 3:13፤ ራእይ 21:3, 4