ከሐዲዎች እንዳያስቷችሁ ተጠንቀቁ
ከይሁዳ የተገኙ ዋና ዋና ነጥቦች
የይሖዋ አገልጋዮች ‘ክፉ የሆነውን መጥላትና ጥሩ የሆነውን ነገር አጥብቀው መያዝ’ አለባቸው። (ሮሜ 12:9) ከመጽሐፍ ቅዱስ ጸሐፊዎች አንዱ የሆነው ይሁዳ በ65 እዘአ ገደማ ከጳለስቲና ምድር በጻፈው ደብዳቤ ላይ ሌሎች ይህን ምክር እንዲሠሩበት ረድቷል።
ይሁዳ ራሱን “የኢየሱስ ክርስቶስ ባሪያ፣ የያዕቆብም ወንድም” ብሎ ጠርቷል። ይኸኛው ያዕቆብ በጣም ታዋቂ የነበረው የኢየሱስ ክርስቶስ ግማሽ ወንድም የነበረው ያዕቆብ ሳይሆን አይቀርም። (ማርቆስ 6:3፤ ሥራ 15:13-21፤ ገላትያ 1:19) ስለዚህ ይሁዳ ራሱም ቢሆን የኢየሱስ ግማሽ ወንድም ነበር፤ ይሁን እንጂ ኢየሱስ ክርስቶስ በዚያን ጊዜ በሰማይ የሚኖር ታላቅ መንፈሣዊ አካል ስለነበረ ይሁዳ ይህን ምድራዊ ዝምድና መጥቀሱ ልክ አይሆንም ብሎ አስቦ ሊሆን ይችላል። የይሁዳ ደብዳቤ ‘መልካም የሆነውን አጥብቀን እንድንይዝና’ ከከሐዲዎች ራሳችንን እንድንጠብቅ የሚረዳ በጣም ቀጥተኛ የሆነ ምክር ሰጥቷል።
‘ተጋደሉ’
ይሁዳ ክርስቲያኖች ስላላቸው የጋራ መዳን ለመጻፍ አስቦ ነበር፤ ይሁን እንጂ የደብዳቤው አንባብያን ‘ለእምነት ከፍተኛ ትግል እንዲያደርጉ’ ማሳሰቡ አስፈላጊ ሆኖ አገኘው። (ቁጥር 1-4) ለምን ይሆን? ምክንያቱም ለአምላክ አክብሮት የማያሳዩ ሰዎች ወደ ጉባኤው ሾልከው በመግባት ‘የማይገባንን የአምላክን ደግነት ብልግና ለመፈጸም ማመካኛ አድርገው ይጠቀሙበት ነበር።’ የአምላክን ሕጎች እያፈረሱ በሕዝቡ መካከል መኖር እንደሚችሉ አድርገው በስሕተት ያስቡ ነበር። እንደዚህ ላለው ክፉ አስተሳሰብ ፈጽሞ ፊት አንስጥ። ከዚህ ይልቅ አምላክ በኢየሱስ ደም አማካኝነት ኃጢአቶቻችን በምሕረቱ ስላጠበልን በማመስገን ሁልጊዜ ጽድቅን እንከታተል።—1 ቆሮንቶስ 6:9-11፤ 1 ዮሐንስ 1:7
ማስጠንቀቂያ እንዲሆኑን በፊታችን የቀረቡልን ምሳሌዎች
ከአንዳንድ ዓይነት ዝንባሌ፣ ጠባይና ሰዎች ራስን መጠበቅ አስፈላጊ ነው። (ቁጥር 5-16) አምላክ ከግብጽ አድኖ ያወጣቸው አንዳንድ እሥራኤላውያን እምነት የሌላቸው በመሆናቸው ተደምስሰዋል። ተገቢ ቦታቸውን የለቀቁ መላእክት “በዘላለም እስራት ከጨለማ (ከመንፈሣዊ ጨለማ) በታች እስከ ታላቁ ቀን ድረስ” ተጠብቀዋል። የሚዘገንን የብልግና ድርጊት በሰዶምና በጎሞራ ላይ የፍርድ ‘ቅጣት’ መጣባቸው። ስለዚህ ሁልጊዜ አምላክን እናስደስት እንጂ “የሕይወትን ጐዳና አንተው።”—መዝሙር 16:11
የመላእክት አለቃ ሚካኤል በዲያብሎስ የስድብ ፍርድ ሊያመጣ አልፈለገም፤ እነዚህ ለአምላክ ደንታ የሌላቸው ሰዎች ግን “ጌትነትን” ማለትም አምላክና ክርስቶስ ቅቡዓን ሽማግሌዎች አድርገው በመሾም ክብር የሰጧቸውን ሰዎች ይንቃሉ። እንግዲህ ከአምላክ ለተሰጠ ሥልጣን አክብሮት እናሳይ!
እነዚህ ለአምላክ ደንታ የሌላቸው ሰዎች የቃየንን፣ የበለዓምንና የቆሬን መጥፎ ምሳሌ ተከትለዋል። ከውኃ በታች እንዳለ ዐለት በመሆን ለሌሎች መንፈሣዊነት አደገኛ ነበሩ። በተጨማሪም ውኃ እንደሌላቸው ዳመናዎችና በድን ነበሩ። እንደ ደረቀ ዛፍ ጥቅም ያለው ምንም ነገር የማያፈሩ ነበሩ። እነዚያ ከሃዲዎች ከዚህ በተጨማሪ የሚያጉረመርሙና የሚያማርሩ፣ ለገዛ ጥቅማቸው ሲሉ ሰውን የሚያሞካሹ ነበሩ።
መቃወማችሁን ቀጥሉ
ይሁዳ ቀጥሎ ወደ መጥፎ የሚገፋፉ ኃይሎችን ስለመቃወም ምክር ሰጠ። (ቁጥር 17-25) “በመጨረሻው ዘመን” ዘባቾች ይመጣሉ፤ እውነተኛ ክርስቲያኖችም እነርሱንና የማሾፍ ቃላቸውን ታግሰው መጽናት አለባቸው። እንደነዚህ ያሉትን ወደ መጥፎ የሚገፋፉ ኃይሎች ለመቋቋም የኢየሱስ ምሕረት የሚገለጥበትን ጊዜ እየተጠባበቅን “ቅዱስ የሆነውን እምነታችንን” መገንባት፣ በመንፈስ ቅዱስ መጸለይና በአምላክ ፍቅር ውስጥ ራሳችንን ማቆየት ይኖርብናል።
እነዚህ ለአምላክ ግድ የሌላቸው ሰዎች ሐሰተኛ አስተማሪዎች በመሆን አንዳንዶችን ጥርጥር ላይ ጥለዋል። (ከ2 ጴጥሮስ 2:1-3 ጋር አወዳድር) ታዲያ ተጠራጣሪዎቹ ምን ያስፈልጋቸው ነበር? “ከእሳት” ማለትም ከዘላለማዊ ጥፋት እንዲያመልጡ መንፈሣዊ እርዳታ ያስፈልጋቸው ነበር። (ማቴዎስ 18:8, 9) ለአምላክ አክብሮት ያላቸው ሰዎች ግን እንደዚህ ያለ ፍርድ ይደርስብናል ብለው መፍራት አያስፈልጋቸውም ምክንያቱም ወደ ኃጢአትና ከሐዲዎችን ወደሚጠብቃቸው ጥፋት እንዳይወድቁ ይሖዋ ይጠብቃቸዋል።
[በገጽ 31 ላይ የሚገኝ ሣጥን]
ድብቅ ዐለቶች፦ ይሁዳን ክርስቲያን ወንድሞቹን ‘በፍቅር ግብዣቸው ላይ እንደ ድብቅ ዓለቶች’ ከሆኑት ሰዎች ራሳቸውን እንዲጠብቁ አስጠንቅቋቸዋል። (ይሁዳ 12) እንደነዚህ ያሉት ከሃዲዎች ለአማኞች ፍቅር እንዳላቸው የሚያስመስሉ ስለነበሩ ከውኃ በታች መርከብን ለመስበር ዋናተኞችንም ሆዳቸውን ለመተርተር እንደሚችል የሾለ ዐለት ነበሩ። የፍቅር ግብዣዎቹ ሀብታም ክርስቲያኖች ድሀ የሆኑትን የእምነት ወንድሞቻቸው የሚጋብዙባቸው ትልልቅ ግብዣዎች ኖረው ሊሆን ይችላል። ክሪሶቶም የተባለው የቤተክርስቲያን አባት (347?–407 እዘአ የነበረ) እንዲህ ብሏል፦ “ሁሉም በጋራ የሚካፈሉባቸው ግብዣዎች ነበሯቸው። ሀብታሞቹ ግብዣውን ያሰናዳሉ፤ ድሆችና ምንም ነገር የሌላቸው ሌሎች ሰዎች ደግሞ ተጋባዥ ሆነው ይመጣሉ። ሁሉም አንድ ላይ በግብዣው ይበላሉ።” በጥንት ጊዜ የነበሩት ግብዣዎች ምንም ዓይነት ይሁኑ ይሁዳ የሰጠው ማስጠንቀቂያ መንፈሣዊ ሞትን ማምጣት ከሚችሉት ድብቅ ዐለት የመሰሉ ከሐዲዎች ራሳቸውን እንዲጠብቁ ታማኞቹን ረድቷቸዋል። ክርስቲያኖች ድሮም ሆነ ዛሬ የፍቅር ግብዣ እንዲያደርጉ ትእዛዝ ባይሰጣቸውም የይሖዋ ሕዝቦች በችግር ጊዜ እርስ በርሳቸው ይረዳዳሉ፤ አብረውም የሚያስደስት ጊዜ ያሳልፋሉ።