የይሖዋ ምሥክሮች በዓለም ዙሪያ—ፖርቶሪኮ
በካሪቢያን ባሕርና በአትላንቲክ ውቅያኖስ መካከል ለምለሟና ሞቃታማዋ የፖርቶሪኮ ደሴት ትገኛለች። በ1493 ክርስቶፈር ኮሎምቦስ የስፔይን ክልል ናት ብሎ ሳን ጁአን ባውቲስታ ሲል በአጥማቂው ዮሐንስ ስም ሰየማት። ዋና ከተማዋ ከረዥም ጊዜ ጀምሮ ፖርቶሪኮ ወይም “የበለጸገች ወደብ” ተብላ ነበር። ከጊዜ በኋላ ይህ ስም መላዋ ደሴት የምትጠራበት ሆነና ከተማዋ ደግሞ ሳን ጁአን ተባለች።
ፖርቶሪኮ በብዙ መንገዶች የበለጸገች ወደብ ለመሆን በቅታለች። በስፔይን ትገዛ በነበረችባቸው የመጀመሪያዎቹ ዓመታት ከእሷ ብዙ ወርቅ ይጋዝ ነበር። ዛሬ ያለው አብዛኛው የደሴቲቱ ኢኮኖሚ በኢንዱስትሪ ውጤቶችና ግልጋሎቶች ላይ የተመሠረተ ቢሆንም ደሴቲቱ በአሁኑ ወቅት ሸንኮራ አገዳ፣ ቡና፣ ሙዝ እንዲሁም እንደ ብርቱካንና ሎሚ ያሉትን ፍራፍሬዎች ወደ ውጭ ትልካለች። ይሁንና ፖርቶሪኮ ከዚህ የበለጠ ትርጉም ባለው መንገድ የበለጸገች ወደብ ሆናለች።
ፖርቶሪኮ ውስጥ ስለ አምላክ መንግሥት ምሥራች መሰበክ የተጀመረው በ1930ዎቹ ዓመታት ውስጥ ነበር። ዛሬ በፖርቶሪኮ ከ25,000 በላይ የሆኑ ምሥራቹ አስፋፊዎች ይገኛሉ። በ1993 በዚህ የመጠበቂያ ግንብ ማኅበር ቅርንጫፍ ውስጥ የሚሠሩት ሰዎች ቁጥር ከ23 ተነሥቶ ከ100 በላይ ወደ መሆን ደረጃ ደርሷል። ቅርንጫፉ መጽሐፍ ቅዱሳዊ ጽሑፎችን ወደ ስፓኒሽ ቋንቋ ተርጉሞ በጠቅላላው ዓለም ለሚገኙ ወደ 350,000,000 የሚጠጉ የስፓኒሽ ቋንቋ ተናጋሪዎች እነዚህን ጽሑፎች ማዳረስ እንዲቻል ይህ ጭማሪ አስፈላጊ ነበር።
አዲስ መስከ
በተጨማሪም ቅርንጫፍ ቢሮው የሚከተለውን ሪፖርት አድርጓል፦ “የመንግሥቱን መልእክት መስማት ለተሳናቸው ሰዎች ለማዳረስ እየጣርን ስለሆነ በፖርቶሪኮ አዲስ መስክ ተከፍቶልናል። አንዲት እህት የሚከተለውን ተሞክሮ ተናግራለች፦ ‘መስማት የተሳናቸው ሰዎች በሚኖሩበት አካባቢ ስሠራ ሁለት ትንንሽ ልጆች ያላትን አንዲት ሴት አነጋግሬ ነበር። የይሖዋ ምሥክር እንደሆንኩ ስትገነዘብ እንደሷው መስማት የተሳነው ባሏ የይሖዋ ምሥክሮችን የማይወድ ስለነበር ወዲያውኑ አልፈልግም አለች።
“‘ከጥቂት ወራት በኋላ ይህችው ሴት ከይሖዋ ምሥክሮች ጋር መጽሐፍ ቅዱስ እያጠናች ያለች ጓደኛዋን ልትጠይቅ ሄደች። በጥናቱ ላይ ተገኘችና በጣም ተደሰተችበት። ሴቲቱን እንደገና ሄጄ ሳነጋግራት ባሏ ምሥክሮቹን እንደማይወድ በድጋሚ ነገረችኝ። ይሁን እንጂ ስለ መጽሐፍ ቅዱስ ማወቅ ፈለገች፤ ቤተ ክርስቲያኗ ምንም ስለማያስተምር ሰልችቷት ነበር። በአንድ ትራክት ተጠቅመን ጥናት ጀመርን። አንድ ቀን ባለቤቴ ቤት ስለሚኖር ቅዳሜ ተመልሰሽ ነይ ስትል ነገረችኝ። “ግን እኮ አይወደንም፤ አይደለም እንዴ?” ስል ጠየቅኋት። “የይሖዋ ምሥክሮች ምን እንደሚያስተምሩ በትክክል ማወቅ ይፈልጋል” ስትል መለሰች።
“‘በሚቀጥለው ቀን ሁለቱም ወደ ቤቴ መጥተው በሬን አንኳኩ። ባልዬው ብዙ ጥያቄዎች ስለነበሩት መስማት ለተሳናቸው በተዘጋጀው ስብሰባችን ላይ እንዲገኙ ጋበዝኳቸው። በስብሰባው ላይ ቀድሞኝ ተግኝቶ ነበር፤ ከዚያ ወዲያም አንድም ስብሰባ አላመለጠውም። መስማት ለተሳናቸው ሌሎች ሰዎች እየሰበከ ነው፤ በአንድ ትልቅ ስብሰባ ላይ ተገኝቷል፤ የሚጠመቅበትን ጊዜም በጉጉት እየተጠባበቀ ነው።’”
የቅርንጫፉ ሪፖርት እንዲህ በማለት ይቀጥላል፦ “በዚህ ዓመት ባደረግነው የወረዳ ስብሰባ ላይ ሙሉው ፕሮግራም በምልክት ቋንቋ ቀርቦ ነበር፤ ብዙ መስማት የተሳናቸው ሰዎችና ቤተሰቦቻቸው ተገኝተዋል። በመጨረሻው ንግግር ላይ ተናጋሪው መስማት የተሳናቸው ሰዎች በሚገኙበት መስክ ላይ ሥራው እየተካሄደ እንዳለና 70 የሚያህሉት በስብሰባው ላይ እንደተገኙ ሲናገር የሁሉም ስሜት በጣም ተነክቶ ነበር። ከፍተኛ ጭብጨባ የነበረ ቢሆንም መስማት የተሳናቸው ሰዎች ጭብጨባውን እንዳልሰሙት ተናጋሪው ተረድቶ ነበር። ስለዚህ ተናጋሪው መስማት የተሳናቸው ሰዎች አድማጮችን እንዲመለከቱ በመጋበዝ ‘መስማት የተሳናቸው ወንድሞቻችሁ በመካከላችሁ በመገኘታችው ተደስታችኋልን?’ ሲል በድጋሚ ጠየቀና አድማጮቹን መስማት የተሳናቸው ሰዎች እንደሚያደርጉት ሁለቱንም እጆቻቸውን በማወዛወዝ አድናቆታቸውን እንዲገልጹ ጠየቀ። 11,000 ወንድሞችና እህቶች እጃችውን በማወዛወዝ አድናቆታቸውን ሲገልጹ ማየት በጣም ያስደስት ነበር። መስማት የተሳናቸው ወንድሞቻችንና እህቶቻችን በጣም ተደስተውና የአንድ ታላቅ የወንድማማቾች ማኅበር ክፍል እንደሆኑ ተሰምቷቸው ነበር። ብዙዎች የደስታ እንባ አነቡ።”
በፖርቶሪኮ የሚገኙት የይሖዋ ምሥክሮች በመከሩ ሥራ በተሳተፉ መጠን ደሴቲቱ የበለጸገች ወደብ መሆኗ እንደሚቀጥል አያጠራጥርም። የይሖዋ ቤት በክብር እንዲሞላ እሱ ‘ከአሕዛብ የተመረጡ ዕቃዎች’ ብሎ የጠራቸው የአምላክ “በጎች” መምጣታቸውን ይቀጥላሉ።—ዮሐንስ 10:16፤ ሐጌ 2:7
[በገጽ 9 ላይ የሚገኝ ሣጥን]
የአገሪቱ ሪፖርት መግለጫ
የ1993 የአገልግሎት ዓመት
የምሥክሮቹ ከፍተኛ ቁጥር፦ 25,428
ከሕዝቡ ብዛት ጋር ሲነጻጸር፦ 1 ምሥክር ለ139 ሰዎች
የመታሰቢያው በዓል ተሰብሳቢዎች፦ 60,252
የአቅኚዎች ብዛት በአማካይ፦ 2,329
የመጽሐፍ ቅዱስ ጥናቶች በአማካይ፦ 19,012
የተጠማቂዎች ብዛት፦ 919
የጉባኤዎች ብዛት፦ 312
ቅርንጫፍ ቢሮው የሚገኝበት ቦታ፦ ጉያንአቦ