የሚሰበሰቡት ለምንድን ነው?
በዓለም ዙሪያ የሚገኙ የይሖዋ ምሥክሮች በየዓመቱ ትላልቅ ስብሰባዎችን ያደርጋሉ። በእነዚህ ስብሰባዎች ላይ በብዙ ሺህ የሚቆጠሩ ተሰብሳቢዎች ይገኛሉ። በስብሰባዎቹም ላይ ከብዙ የእምነት ወንድሞቻቸው ጋር የመገናኘት አጋጣሚ ከማግኘታቸውም በላይ ግሩም የሆኑ የመጽሐፍ ቅዱስ ትምህርቶችን ያዳምጣሉ። አንዳንዶች በእነዚህ ትላልቅ ስብሰባዎች ላይ ለመገኘት የሚከፍሉት መሥዋዕትነት ቀላል አይደለም። ለምሳሌ ባለፈው ዓመት በማላዊ የሚኖሩ በስልሳዎቹ ዕድሜ አጋማሽ ላይ የሚገኙ ባልና ሚስት ከወንድ ልጃቸውና ሕፃን ልጅ ከያዘችው ሚስቱ ጋር በመሆን በአንድ ትልቅ ስብሰባ ላይ ለመገኘት 80 ኪሎ ሜትር በብስክሌት ተጉዘዋል። ከንጋቱ አሥራ ሁለት ሰዓት ከመንደራቸው ተነስትው ከ15 ሰዓታት ጉዞ በኋላ ስብሰባው ቦታ ደርሰዋል።
በሞዛምቢክ አንድ ቡድን በአንድ ትልቅ ስብሰባ ላይ ለመገኘት ሦስት ቀን በብስክሌት ተጉዟል። አንድ ቀን ሌሊት ሜዳ ላይ ሰፍረው እያሉ አጠገባቸው አንበሳ ሲያገሳ ሰሙ። አንበሶቹን ለማባረር የሚነድ እንጨት ቢወረውሩም እንኳ ጎህ እስኪቀድ ድረስ ከአካባቢያቸው አልሄዱም። በዚሁ ስብሰባ ላይ ለመገኘት ይጓዝ የነበረ አንድ ሌላ ወንድም በመንገድ ላይ ከአንበሳ ጋር ፊት ለፊት ተገናኘ። አንበሳው ካጠገቡ እስኪሄድ ድረስ ምንም ሳይንቀሳቀስ ጸጥ ብሎ ቆመ። እነዚህ የይሖዋ ምሥክሮች “ከአንበሳ አፍ” እንዴት እንደዳኑ በደስታ ተሞክሯቸውን በስብሰባው ላይ ተናግረዋል።—2 ጢሞቴዎስ 4:17
በትላልቅ ስብሰባዎችም ሆነ በሳምንታዊ የጉባኤ ስብሰባዎች ላይ ለመገኘት ብዙ የይሖዋ ምሥክሮች ከፍተኛ ጥረት ያደርጋሉ። ለምን? አንድ ላይ መሰብሰብ አስፈላጊ የሆነበትን ምክንያት የሚቀጥሉት ርዕሶች ያብራራሉ።