1 ክርስቲያኖች እውነትን ማወቃቸው ያስደስታቸዋል! በዓለም ያሉ ሰዎች የሚከተሉትን አኗኗር በመራቅ እንዴት መኖር እንዳለብን አስተምሮናል። እነርሱ ‘ከእግዚአብሔር ሕይወት የራቁ’ በመሆናቸው ‘አእምሮአቸው ጨልሟል።’ (ኤፌ. 4:18 የ1980 ትርጉም) አሮጌውን ሰው አስወግደን አዲሱን በመልበስ አእምሮአችንን ከዓለማዊ አስተሳሰብ ነፃ ማድረግን ተምረናል።—ኤፌ. 4:22-24
2 አሮጌው ሰው ያለማቋረጥ ወደ ሥነ ምግባር ውድቀት እያሽቆለቆለ የሚሄድ ሲሆን ወደ ርኩሰትና ሞት ይመራል። በመሆኑም የመንግሥቱን መልእክት የሚቀበሉ ሰዎች ሁሉ ቁጣን፣ ንዴትን፣ ክፋትን፣ ስድብንና የሚያሳፍር ንግግርን በሙሉ እርግፍ አድርገው እንዲተዉ እንመክራቸዋለን። የአምላክን ሞገስ ማግኘት የሚፈልጉ ሰዎች አንድን ቆሻሻ ልብስ አውልቀው እንደሚጥሉ ሁሉ አሮጌውን ሰው ያለማወላወል ሙሉ በሙሉ አውልቀው መጣል አለባቸው።—ቆላ. 3:8, 9
3 አእምሮን የሚያንቀሳቅስ አዲስ ኃይል፦ አዲሱን ሰው መልበስ አእምሮአችንን በሚያንቀሳቅሰው ኃይል መታደስንም ይጨምራል። (ኤፌ. 4:23) አንድ ሰው ይህ ኃይል ወይም የአእምሮ ዝንባሌ ወደ ትክክለኛ አቅጣጫ እንዲያመራ ማደስ የሚችለው እንዴት ነው? ይህን ማድረግ የሚቻለው የአምላክን ቃል አዘወትሮ በትጋት በማጥናትና በያዘው ትርጉም ላይ በማሰላሰል ነው። ከዚህ በኋላ ግለሰቡ አዲስ ዓይነት አስተሳሰብ በማዳበር ነገሮችን በአምላክና በክርስቶስ ዓይን ማየት ይጀምራል። አንድ ሰው ርኅራኄን፣ ቸርነትን፣ ትሕትናን፣ የዋህነትን፣ ትዕግሥትንና ፍቅርን ጨምሮ የተለያዩትን የክርስቶስ ዓይነት ባሕርያት በለበሰ መጠን ሕይወቱ ይለወጣል።—ቆላ. 3:10, 12-14
4 አዲሱን ሰው በመልበስ ራሳችንን ከዓለም እንለያለን። አኗኗራችን ልዩ ያደርገናል። እውነት የሆነውን እንናገራለን፤ እንዲሁም ንግግራችን ሌሎችን ለማነጽ የሚጠቅም ጤናማ ይሆናል። ቁጣችንን ከመቆጣጠራችንም በተጨማሪ ኩራትን፣ ምኞትን፣ መራርነትን፣ ጩኸትን፣ ስድብንና ማንኛውንም ክፋት አምላካዊ በሆኑ የጽድቅ ባሕርያት እንተካለን። መሐሪ በመሆን ወይም ልባዊ ይቅርታ በመጠየቅ ረገድ ከሚጠበቅብን በላይ አልፈን እንሄዳለን። ይህን ሁሉ የምናደርገው ከልባችን ነው።—ኤፌ. 4:25-32
5 አዲሱን ሰው ፈጽሞ አታውልቁ። አዲሱን ሰው ሳንለብስ ይሖዋን ተቀባይነት ባለው መንገድ ማገልገል አንችልም። አዲሱ ሰውነት ሰዎችን ወደ እውነት እንዲስብና ድንቅ የሆነውን አዲስ ባሕርይ ለፈጠረልን አምላክ ለይሖዋ ክብር እንዲያመጣ ፍቀዱለት።—ኤፌ. 4:24