መንፈስን የሚያድስ ሙዚቃ
1 መዝሙርና ሙዚቃ በእውነተኛው አምልኮ ውስጥ ትልቅ ቦታ አላቸው። በጥንቷ እስራኤል አሳፍና ወንድሞቹ “ለእግዚአብሔር ምስጋና አቅርቡ፤ . . . ዘምሩለት፤ ውዳሴም አቅርቡለት፤ ድንቅ ሥራውን ሁሉ ንገሩ” በማለት ዘምረዋል። (1 ዜና 16:8, 9) ዛሬም በየሳምንቱ በምናደርጋቸው የጉባኤ ስብሰባዎች ላይ ለይሖዋ እንዘምራለን። (ኤፌ. 5:19) ይህ ስሙን ለማወደስ የሚያስችል እንዴት ያለ ግሩም አጋጣሚ ነው!—መዝ. 69:30
2 በኦርኬስትራ የተዘጋጁትን የመንግሥቱ ጣዕመ ዜማዎች ማዳመጥ ስለ መንፈሳዊ ነገሮች እንድናስብ ያደርገናል። አንዲት እህት እንዲህ ብላለች:- “እነዚህን ጣዕመ ዜማዎች ሳዳምጥ ስንኞቹ ወደ አእምሮዬ ይመጣሉ። ይህም በሙዚቃው እየተዝናናሁ ስለ ይሖዋ ለማሰብ ግሩም አጋጣሚ ይሰጠኛል።”—ፊልጵ. 4:8
3 ምን ጊዜ ልናዳምጣቸው እንችላለን? በቤታችን ውስጥ የመንግሥቱን ጣዕመ ዜማዎች ማዳመጥ ደስ የሚል መንፈሳዊ ሁኔታ እንዲኖር ስለሚያደርግ ለቤተሰቡ ሰላም አስተዋጽኦ ያደርጋል። አንድ ቤተሰብ እንዲህ ሲል ጽፏል:- “ቤት ውስጥ በምንሆንበት ጊዜ እንዲሁም በመኪና ስንጓዝ ደጋግመን የምናዳምጠው ሲሆን ደስ በሚያሰኝ መንገድ የተቀናበረውን ይህንን [ሙዚቃ] መስማት ፈጽሞ አይሰለቸንም። ብዙውን ጊዜ ለክርስቲያናዊ ስብሰባዎች ስንዘጋጅ ወይም ወደ ትላልቅ ስብሰባዎች ስንጓዝ የመንግሥቱን ጣዕመ ዜማዎች ማዳመጣችን ጥሩ መንፈስ እንዲኖረን ይረዳናል።” አንዲት እህት ደግሞ እንደሚከተለው ብላለች:- “የቤት ውስጥ ሥራዎቼን ሳከናውን እነዚህን መዝሙሮች መስማት መንፈሴን ያድስልኛል፤ ልብስ በማጣጥፍበት ጊዜ እንኳ ደስ ብሎኝ እንድሠራ ይረዳኛል። ውስጤ እንደተረበሸ ሲሰማኝ አዳምጠዋለሁ። ሙዚቃው መንፈስን ያነቃቃል! . . . መዝሙሮቹ በሙሉ ልብን ደስ ያሰኛሉ።” አንተስ እነዚህን መንፈስ የሚያድሱ ሙዚቃዎች ማዳመጥ የምትችልበት አጋጣሚ አለህ?
4 በዛሬው ጊዜ ያለው አብዛኛው ሙዚቃ የዓለምን መንፈስ የሚያንጸባርቅ ነው። ወላጆች በመንግሥቱ ጣዕመ ዜማዎች በመጠቀም ልጆቻቸው ጤናማ የሆነ የሙዚቃ ምርጫ እንዲያዳብሩና በግለት የመዘመር ልማድ እንዲኖራቸው ሊረዷቸው ይችላሉ። በርካታ የመጽሐፍ ቅዱስ ተማሪዎችና ፍላጎት ያላቸው ሰዎችም ይሖዋን ስለሚያወድሱትና መንፈስን ስለሚያድሱት ስለ እነዚህ ግሩም መንፈሳዊ መዝሙሮች ብንነግራቸው ይደሰታሉ።—መዝ. 47:1, 2, 6, 7