ቅድሚያ የምትሰጠው ነገር ምንድን ነው?
1 ለዚህ ጥያቄ ምን መልስ ትሰጣለህ? እርግጥ ነው፣ ሁላችንም የአምላክን መንግሥት ማስቀደም እንፈልጋለን። (ማቴ. 6:33) ሆኖም ‘የማደርጋቸው ውሳኔዎች መንግሥቱን እንደማስቀድም ያሳያሉ?’ እያልን ራሳችንን መጠየቅ እንችላለን። መጽሐፍ ቅዱስ “ራሳችሁን ፈትኑ” በማለት ይህን እንድናደርግ ያበረታታናል። (2 ቆሮ. 13:5) ለመንግሥቱ ጉዳዮች ቅድሚያ እየሰጠን እንደሆነና እንዳልሆነ ለማወቅ ራሳችንን መፈተን የምንችለው እንዴት ነው?
2 በጊዜ አጠቃቀማችን ረገድ:- ጊዜያችንን እንዴት እንደምንጠቀምበት በመመርመር ራሳችንን መፈተን ልንጀምር እንችላለን። (ኤፌ. 5:15, 16) ለማኅበራዊ እንቅስቃሴዎች፣ ለቴሌቪዥን፣ ለኢንተርኔትና ለትርፍ ጊዜ ማሳለፊያዎች በየሳምንቱ ምን ያህል ጊዜ እናጠፋለን? ለእነዚህ ነገሮች የምናባክነውን ጊዜ መዝግበን ብንይዝና ለመንፈሳዊ እንቅስቃሴዎች ካዋልነው ጊዜ ጋር ብናወዳድረው በውጤቱ መደነቃችን አይቀርም። የቅንጦት ኑሮ ለመኖር ስንል ቅዱስ አገልግሎታችንን ለማከናወን የምናውለውን ጊዜ መሥዋዕት በማድረግ ተጨማሪ ሰዓታት እንሠራለን? በሳምንቱ መጨረሻ ላይ ለመዝናናት ስንል ከስብሰባና ከአገልግሎት ምን ያህል ጊዜ ቀርተናል?
3 ቅድሚያ ለሚሰጣቸው ነገሮች ቅድሚያ ስጡ:- አብዛኞቻችን የምንፈልገውን ሁሉ ለማድረግ የሚያስችል በቂ ጊዜ የለንም። ስለዚህ የመንግሥቱን ፍላጎቶች ለማስቀደም እንድንችል ቅድሚያ የምንሰጣቸውን ነገሮች መመርመርና ‘ከሁሉ ለሚሻለው’ ነገር ጊዜ መመደብ ይኖርብናል። (ፊልጵ. 1:10) ይህም የአምላክን ቃል ማጥናትን፣ በአገልግሎት ላይ መካፈልን፣ ቤተሰብን መንከባከብንና በክርስቲያናዊ ስብሰባዎች ላይ መገኘትን ይጨምራል። (መዝ. 1:1, 2፤ ሮሜ 10:13, 14፤ 1 ጢሞ. 5:8፤ ዕብ. 10:24, 25) ቀላል የአካል ብቃት እንቅስቃሴንና ጤናማ የሆኑ መዝናኛዎችን ጨምሮ እነዚህን በመሳሰሉ ሌሎች እንቅስቃሴዎች ላይ መካፈል ጥቅም ያስገኛል። (ማር. 6:31፤ 1 ጢሞ. 4:8) ሆኖም እምብዛም አስፈላጊ ያልሆኑት እነዚህ እንቅስቃሴዎች ለመንግሥቱ የምናውለውን ጊዜ እንዲሻሙብን መፍቀድ አይኖርብንም።
4 አንድ ወጣት ወንድም መንግሥቱን ለማስቀደም ስለፈለገ ሰብዓዊ ሥራ የሚያስገኝለትን ከፍተኛ ትምህርት ከመከታተል ይልቅ ወደ ሙሉ ጊዜ አገልግሎት ለመግባት ወሰነ። ሌላ ቋንቋ ተማረና የመንግሥቱ አስፋፊዎች ይበልጥ ወደሚያስፈልጉበት ቦታ ሄዶ ማገልገል ጀመረ። ይህ ወንድም እንዲህ ብሏል:- “በጣም አስደሳች ሕይወት እየመራሁ ነው። አገልግሎት መንፈስን የሚያድስ ሆኖልኛል! እያንዳንዱ ወጣት እንዲህ ቢያደርግና እንደ እኔ ዓይነት ስሜት ቢሰማው ደስ ይለኛል። ባለን ነገር ሁሉ ይሖዋን ከማገልገል የሚበልጥ ምንም ነገር የለም።” አዎን፣ መንግሥቱን ማስቀደማችን በረከት ያስገኝልናል። ከሁሉም በላይ ግን በሰማይ የሚኖረው አባታችንን ይሖዋን ያስደስተዋል።—ዕብ. 6:10