ደፋር ግን ሰላማውያን
1 ምሥራቹን የምንሰብክላቸው ብዙ ሰዎች ምንም እንኳ ከመጽሐፍ ቅዱስ እውነት ጋር የሚጋጭ ቢሆንም ስለሚያምኑባቸው ነገሮች በቅንነት ይናገራሉ። ምሥራቹን በድፍረት መስበክ ቢኖርብንም ‘ከሰው ሁሉ ጋር ሰላም’ እንዲኖረን እንፈልጋለን፤ የሚያስቀይም ነገር እንዳንናገርም እንጠነቀቃለን። (ሮሜ 12:18፤ ሥራ 4:29) የአምላክን መንግሥት ምሥራች በምንሰብክበት ወቅት ደፋር ግን ሰላማዊ መሆን የምንችለው እንዴት ነው?
2 የምትስማሙበትን ነጥብ ፈልጉ:- ሰላማዊ ሰው ከክርክር ይርቃል። የቤቱ ባለቤት በጥብቅ የሚያምንባቸውን ነጥቦች ትክክል እንዳልሆኑ ለማሳመን አላስፈላጊ ሙግት መግጠማችን መልእክታችንን እንዲቀበል አያደርገውም። ምናልባት የተሳሳተ ነገር ቢናገር ሊያስማማን ይችላል ብለን የምናስበውን ነጥብ ማንሳት እንችላለን። በጋራ በምናምንባቸው ነገሮች ላይ በማተኮር ግለሰቡ የሚሰማውን አሉታዊ ስሜት ማስወገድና ልቡን መንካት እንችላለን።
3 የቤቱ ባለቤት ያሉትን የተሳሳቱ አመለካከቶች ችላ ብለን ማለፋችን በሐሳቡ እንደመስማማት ወይም እውነትን እንደማለዘብ ይቆጠራል? በፍጹም። ክርስቲያን አገልጋዮች እንደመሆናችን መጠን የእኛ ኃላፊነት የሚያጋጥመንን እያንዳንዱን ስህተት ማስተካከል ሳይሆን የአምላክን መንግሥት ምሥራች መስበክ ነው። (ማቴ. 24:14) የቤቱ ባለቤት የተሳሳተ ነገር በሚናገርበት ወቅት ከመቆጣት ይልቅ ግለሰቡ ምን አመለካከት እንዳለው ለማወቅ የሚያስችል አጋጣሚ አድርገን ብንመለከተው ጥሩ ነው።—ምሳሌ 16:23
4 ክብራቸውን እንጠብቅላቸው:- የሐሰት ትምህርቶችን ስናፈርስ ደፋርና ቆራጥ መሆን የሚያስፈልገን ወቅት አለ። ይሁን እንጂ ሰላማውያን እንደመሆናችን መጠን በተሳሳተ ትምህርት የሚያምኑትንም ሆነ የሚያስተምሩትን ሰዎች ጠቅሰን ስንናገር በእነርሱ ላይ ከማሾፍ ብሎም ክብርን የሚነኩ ቃላትን ከመጠቀም እንቆጠባለን። ራስን ከፍ ከፍ የማድረግ ዝንባሌ ሰዎችን የሚያርቅ ሲሆን ትሕትናና የደግነት አቀራረብ ግን እውነትን የሚያፈቅሩ ሰዎች አእምሯቸውን እንዲከፍቱ ያደርጋል። ለሚያዳምጡን ሰዎች እንዲሁም ለእምነታቸው አክብሮት ስናሳይ ክብራቸውን እየጠበቅንላቸው ነው፤ እንዲህ ማድረጋችን ደግሞ የምንሰብከውን መልእክት ለመቀበል ቀላል ያደርግላቸዋል።
5 ሐዋርያው ጳውሎስ ይሰብክላቸው የነበሩትን ሰዎች እምነት ያከብር እንዲሁም ምሥራቹን ልባቸውን በሚነካ መንገድ ለማቅረብ ይጥር ነበር። (ሥራ 17:22-31) ጳውሎስ ‘በሚቻለው ሁሉ አንዳንዶችን ያድን ዘንድ ከሁሉም ጋር ሁሉን ነገር’ ለመሆን ፈቃደኛ ነበር። (1 ቆሮ. 9:22) እኛም የመንግሥቱን ምሥራች በድፍረት ስንሰብክ ሰላማውያን በመሆን እርሱን መምሰል እንችላለን።