‘የአምላክ ስም ይቀደስ’
1. የ2012 የአገልግሎት ዓመት የወረዳ ስብሰባ ጭብጥ ምንድን ነው? በምን ላይስ የተመሠረተ ነው?
1 የአጽናፈ ዓለሙ ሉዓላዊ ገዥ የሆነውን የይሖዋን ስም መሸከም እንዴት ያለ ታላቅ መብት ነው! ይህን ስም የመሸከም መብት የሰጠን አምላክ ራሱ ሲሆን በተለይ ደግሞ ከ1931 ጀምሮ የይሖዋ ምሥክሮች በሚለው ልዩ ስም ስንጠራ ቆይተናል። (ኢሳ. 43:10) የአምላክ አንድያ ልጅ የሆነው ኢየሱስ በናሙና ጸሎቱ ላይ ለአምላክ ስም የመጀመሪያውን ቦታ መስጠቱ ለዚህ ስም ከፍተኛ ግምት እንደነበረው ያሳያል። (ማቴ. 6:9) በ2012 የአገልግሎት ዓመት ለሚደረገው የወረዳ ስብሰባ ጭብጥ መሠረት የሆነው ኢየሱስ ያስተማረው ይህ ጸሎት ነው። የስብሰባው ጭብጥ “የአምላክ ስም ይቀደስ” የሚል ነው።
2. ከስብሰባው ምን ትምህርት እንደምናገኝ በጉጉት እንጠብቃለን?
2 የሚቀርቡት ንግግሮች፦ ቅዳሜ ዕለት የሚቀርበው “የሙሉ ጊዜ አገልጋዮች እንደመሆናችሁ መጠን የአምላክን ስም አሳውቁ” የሚለው ንግግር የሙሉ ጊዜ አገልግሎት የሚክስ የሕይወት መንገድ የሆነበትን ምክንያት ያብራራል። በተጨማሪም “የይሖዋን ስም እንዳታስነቅፉ ተጠንቀቁ” የሚል ሲምፖዚየም የሚቀርብ ሲሆን በዚህ ሲምፖዚየም ላይ አደገኛ ከሆኑ አራት ወጥመዶች መራቅ የምንችልበትን መንገድ እንማራለን። “የአምላክ ስም መቀደስ የሚኖርበት ለምንድን ነው?” የሚለው ንግግር ‘ሰዎች ለመንግሥቱ መልእክት እምብዛም ፍላጎት በማያሳዩበት ጊዜ ምሥራቹን በቅንዓት ለመስበክ ምን ሊረዳን ይችላል? እንዲሁም ውጤታማ አገልግሎት እንድናከናውን ምን ሊረዳን ይችላል?’ ለሚሉት ጥያቄዎች መልስ ይሰጣል። እሑድ ቀን በሚቀርብልን አራት ክፍል ያለው ሲምፖዚየም ላይ ደግሞ በአስተሳሰባችን፣ በአነጋገራችን፣ በምናደርጋቸው ውሳኔዎችና በጠባያችን የአምላክን ስም ማስቀደስ የምንችልበትን መንገድ እንማራለን። በተለይም አዲሶች “ይሖዋ በአርማጌዶን ጦርነት ታላቅ ስሙን ያስቀድሳል” በሚል ጭብጥ ከሚቀርበው የሕዝብ ንግግር ብዙ ጥቅም ማግኘት እንደሚችሉ ምንም ጥርጥር የለውም።
3. ምን ልዩ መብት አለን? ይህ ስብሰባ በምን ረገድ ሊረዳን ይችላል?
3 በቅርቡ ይሖዋ ስሙን ለማስቀደስ እርምጃ ይወስዳል። (ሕዝ. 36:23) እስከዚያው ድረስ ግን ከይሖዋ ቅዱስ ስም ጋር በተያያዘ የሚከናወኑ ሥራዎችን ሁሉ የመደገፍ ልዩ መብት አለን። ይህ የወረዳ ስብሰባ የአምላክን ስም በመሸከም ረገድ የተጣለብንን ከባድ ኃላፊነት ለመወጣት እንደሚረዳን ሙሉ እምነት አለን።