ክርስቲያናዊ ሕይወት
ምሥራቹን በመስበክ ተደሰት
ምሥራቹን መስበክ ከባድ ሆኖብህ ያውቃል? ብዙዎቻችን ለዚህ ጥያቄ ‘አዎ’ የሚል መልስ እንሰጣለን። ይህ የሆነው ለምንድን ነው? በክልላችን ውስጥ የምናገኛቸው ብዙ ሰዎች ለምሥራቹ ግዴለሽ ስለሆኑ ወይም ስለሚጠሉን አሊያም ደግሞ የማናውቀውን ሰው ማነጋገር ስለምንፈራ ሊሆን ይችላል። እነዚህ ነገሮች ደስታችንን ሊያጠፉብን እንደሚችሉ የታወቀ ነው። ይሁን እንጂ የምናመልከው አምላክ ደስተኛ ሲሆን እኛም በደስታ እንድናገለግለው ይፈልጋል። (መዝ 100:2፤ 1ጢሞ 1:11) ምሥራቹን መስበክ አስደሳች እንዲሆንልን የሚያደርጉ ሦስት ምክንያቶችን እስቲ እንመልከት፦
አንደኛ፣ የምናውጀው መልእክት ተስፋ ያዘለ ነው። በዛሬው ጊዜ ተስፋ የሚሰጥ ነገር እየጠፋ ቢሆንም እኛ ለሰዎች የምንሰብከው “የተሻለ ነገር እንደሚመጣ [የሚያበስር] ምሥራች” ነው። (ኢሳ 52:7) ስለ አምላክ መንግሥት የሚናገረው ምሥራች እኛም ደስተኛ እንድንሆን ሊያደርገን ይችላል። እንግዲያው ምሥራቹን ለመስበክ ከመውጣታችን በፊት፣ የአምላክ መንግሥት ለምድራችን ስለሚያመጣቸው በረከቶች እናሰላስል።
ሁለተኛ፣ የምንሰብከው ምሥራች ለሰዎች አካላዊም ሆነ መንፈሳዊ ጥቅም ያስገኛል። ምሥራቹ፣ ሰዎች መጥፎ ልማዳቸውን እንዲያስወግዱ እንዲሁም የዘላለም ሕይወት የማግኘት ተስፋ እንዲኖራቸው ይረዳቸዋል። (ኢሳ 48:17, 18፤ ሮም 1:16) አደጋ ያጋጠማቸውን ሰዎች ፈልጎ በማዳን ሥራ ላይ እንደተሰማራን አድርገን ልናስብ እንችላለን። አንዳንዶች ሕይወታቸውን ለማዳን የምንሰጣቸውን እርዳታ መቀበል ባይፈልጉም እንኳ እርዳታውን የሚቀበሉ ሰዎችን መፈለጋችንን እንቀጥላለን።—ማቴ 10:11-14
ሦስተኛውና ከሁሉ ይበልጥ ትልቅ ቦታ የሚሰጠው ምክንያት ደግሞ የስብከቱ ሥራችን ይሖዋን የሚያስከብር መሆኑ ነው። ይሖዋ፣ ምሥክርነት በመስጠት የምናከናውነውን ሥራ ከፍ አድርጎ ይመለከተዋል። (ኢሳ 43:10፤ ዕብ 6:10) በተጨማሪም ይህን ሥራ ማከናወን እንድንችል ቅዱስ መንፈሱን በልግስና ይሰጠናል። በመሆኑም ከመንፈስ ቅዱስ ፍሬ ገጽታዎች አንዱ የሆነውን ደስታን እንዲሰጥህ ይሖዋን ለምነው። (ገላ 5:22) በይሖዋ እርዳታ ፍርሃታችንን አሸንፈን በድፍረት መስበክ እንችላለን። (ሥራ 4:31) በክልላችን ውስጥ የምናገኛቸው ሰዎች የሚሰጡት ምላሽ ምንም ይሁን ምን የስብከቱን ሥራ በማከናወን ደስታ ማግኘት እንችላለን።—ሕዝ 3:3
በአገልግሎት ላይ ስትሆን የትኛው ዓይነት አመለካከት እንዲኖርህ ትፈልጋለህ? ደስተኛ መሆንህን ማሳየት የምትችለው እንዴት ነው?
ጥናትና ማሰላሰል ደስታን መልሶ ለማግኘት ይረዳል የተባለውን ቪዲዮ ከተመለከታችሁ በኋላ የሚከተሉትን ጥያቄዎች ለመመለስ ሞክሩ፦
በየወሩ በስብከቱ ሥራ ላይ በርካታ ሰዓታት የምናሳልፍ ቢሆንም እንኳ ራሳችንን በመንፈሳዊ የመመገብ ልማዳችን ቅድሚያ ሊሰጠው የሚገባው ለምንድን ነው?
የማርያምን ምሳሌ መከተል የምንችለው እንዴት ነው?
በአምላክ ቃል ላይ ለማሰላሰል የመደብከው ጊዜ መቼ ነው?
ምሥራቹን ከመስበክ ጋር በተያያዘ የሚያስደስትህ ነገር ምንድን ነው?