ሕልም
ፍቺ:- አንድ ሰው በእንቅልፍ ላይ እያለ የሚመጣበት ሐሳብ ወይም በአእምሮ ውስጥ የሚቀረጽ ምስል ሕልም ይባላል። መጽሐፍ ቅዱስ ስለ ተፈጥሯዊ ሕልሞች፣ ከአምላክ ስለሚገኙ ሕልሞችና ከምዋርት ጋር ግንኙነት ስላላቸው ሕልሞች ይናገራል።—ኢዮብ 20:8፤ ዘኍ. 12:6፤ ዘካ. 10:2
ሕልም በጊዜያችን ልዩ ትርጉም አለውን?
ተመራማሪዎች ስለ ሕልም ምን ነገር ተረድተዋል?
ዘ ወርልድ ቡክ ኢንሳይክሎፔድያ (1984፣ ጥራዝ 5፣ ገጽ 279) “እያንዳንዱ ሰው ሕልም ያያል። አብዛኞቹ አዋቂዎች በስምንት ሰዓት የእንቅልፍ ጊዜ ውስጥ ለ100 ደቂቃ ያህል ሕልም ያያሉ” ብሏል። ስለዚህ ሕልም ተፈጥሯዊና የተለመደ ክስተት ነው።
የሐርቫርድ ሕክምና ትምህርት ቤት ባልደረባ የሆኑት ዶክተር አለን ሆብሰን እንዲህ በማለት ተናግረዋል:- “ሕልም፣ ሕልም ፈቺ ሁሉ እንደየዝንባሌው በፈለገው መንገድ ሊተረጉመው የሚችል የተወሰነ ፍች የሌለው ስሜት ቀስቃሽ ነገር ነው። የሕልም ፍች የሚወሰነው በሕልሙ በራሱ ሳይሆን በተመልካቹ ዓይን ነው” ብለዋል። ዘ ኒው ዮርክ ታይምስ የተባለው መጽሔት “ሳይንስ ታይምስ” በተባለው ዓምዱ ላይ ስለዚህ ጉዳይ ሲዘግብ “ለሕልም ትልቅ ዋጋ የሚሰጡ ምሁራን የሕልምን ሥነ ልቦናዊ መልእክት ለማወቅ የተለያዩ የንድፈ ሐሳብ አመለካከቶችን የሚያንጸባርቁ ብዙ መንገዶችን ይከተላሉ። የፍሮይድን ትምህርት የሚከተል ሰው ለአንድ ሕልም አንድ ዓይነት ፍቺ ሲሰጥ የጁንጊያንን ትምህርት የሚከተል ደግሞ ሌላ ዓይነት ትርጉም ይሰጣል። የጌስታልት ቴራፒስት ደግሞ ሌላ ትርጉም ያገኝለታል። . . . ሕልም ሥነ ልቡናዊ ፍቺ አለው የሚለው አመለካከት ግን ከኒውሮሳይንቲስቶች ከፍተኛ ትችት ተሰንዝሮበታል” በማለት ገልጿል።—ሐምሌ 10, 1984፣ ገጽ ሲ12
የተለየ እውቀት የሚያስተላልፉ የሚመስሉ ሕልሞች ከአምላክ ሳይሆን ከሌላ ምንጭ ሊመጡ ይችላሉን?
ኤር. 29:8, 9:- “የሠራዊት ጌታ እግዚአብሔር እንዲህ ይላልና:- በመካከላችሁ ያሉት ነቢያቶቻችሁና ምዋርተኞቻችሁ አያታልሉአችሁ፣ እናንተም የምታልሙትን ሕልም አትስሙ። በስሜ ሐሰተኛ ትንቢትን ይናገሩላችኋልና፤ እኔም አልላክኋቸውም።”—ፊደላቱን ጋደል አድርገን የጻፍናቸው እኛ ነን።
ሐርፐርስ ባይብል ዲክሽነሪ (የሐርፐር የመጽሐፍ ቅዱስ መዝገበ ቃላት) እንዲህ በማለት ይነግረናል:- “ባቢሎናውያን በሕልም ያምኑ ስለነበር ትላልቅ ውሣኔዎች ለማድረግ በሚዘጋጁበት ዋዜማ በሕልም አማካኝነት ምክር እናገኛለን ብለው ተስፋ በማድረግ በቤተ መቅደሶች ውስጥ ያድሩ ነበር። ግሪኮች ስለ ጤንነታቸው መመሪያ ለማግኘት ሲሉ በኤስኩላፒዩስ [ልዩ ምልክቱ እባብ የሆነ ጣዖት ነው] መቅደሶች ውስጥ ያድሩ ነበር። ሮማውያን ደግሞ በሴራፒስ [ብዙ ጊዜ ከተጠቀለለ እባብ ጋር ያያይዙት ነበር] ቤተ መቅደስ ያድሩ ነበር። ግብፃውያንም ትልቅ የሕልም መፍቻ መጽሐፍ አዘጋጅተው ነበር።”—(ኒው ዮርክ፣ 1961)፣ ማዴሊን ሚለር እና ጄ ሌን ሚለር፣ ገጽ 141
በጥንት ጊዜ አምላክ ማስጠንቀቂያና መመሪያ ለመስጠት እንዲሁም ትንቢት ለማስነገር በሕልም ይጠቀም ነበር፤ ዛሬም ሕዝቦቹን የሚመራው በዚህ መንገድ ነውን?
ምንጫቸው ከአምላክ የሆኑት ሕልሞች በማቴዎስ 2:13, 19, 20፤ 1 ነገሥት 3:5፤ ዘፍጥረት 40:1–8 ላይ ተጠቅሰዋል።
ዕብ. 1:1, 2:- “ከጥንት ጀምሮ እግዚአብሔር በብዙ ዓይነትና በብዙ ጐዳና [በሕልም ጭምር] ለአባቶቻችን በነቢያት ተናግሮ፣ ሁሉን ወራሽ ባደረገው ደግሞም ዓለማትን በፈጠረበት በልጁ [ትምህርቶቹ በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ ተመዝግበው በሚገኙት በኢየሱስ ክርስቶስ] በዚህ ዘመን መጨረሻ ለእኛ ተናገረን።”
1 ቆሮ. 13:8 የ1980 ትርጉም:- “ትንቢት የመናገር ስጦታም ቢሆን [አንዳንድ ጊዜ አምላክ ለአገልጋዮቹ በሕልም አማካይነት ትንቢት ይገልጽላቸው ነበር] . . . ይጠፋል።”
2 ጢሞ. 3:16, 17 የ1980 ትርጉም:- “ቅዱስ መጽሐፍ በሙሉ በእግዚአብሔር መንፈስ መሪነት የተጻፈ ነው፤ እርሱ . . . ለማስተማር . . . ይጠቅማል። የሚጠቅመውም የእግዚአብሔር ሰው ፍጹም እንዲሆንና ማንኛውንም ሥራ ለመሥራት ብቁ ሆኖ እንዲገኝ ነው።”— ፊደላቱን ጋደል አድርገን የጻፍናቸው እኛ ነን።
1 ጢሞ. 4:1:- “መንፈስ ግን በግልጥ:- በኋለኞች ዘመናት አንዳንዶች የሚያስቱ መናፍስትንና በውሸተኞች ግብዝነት የተሰጠውን [“የተነገረውን” አዓት ] [አንዳንድ ጊዜ በሕልም የተላለፈውን] የአጋንንትን ትምህርት እያደመጡ፣ ሃይማኖትን ይክዳሉ ይላል።”