-
አስተዋጽኦ ማዘጋጀትበቲኦክራሲያዊ የአገልግሎት ትምህርት ቤት ከሚሰጠው ሥልጠና ተጠቀም
-
-
አስተዋጽኦ ማዘጋጀት
ብዙዎች አንድ ንግግር እንዲያቀርቡ ሲመደቡ ከመግቢያው አንስተው እስከ መደምደሚያው ድረስ ሁሉንም አንድ በአንድ ይጽፋሉ፤ ይህ ደግሞ አድካሚ ነው። በዚህ መንገድ አስተዋጽኦ ማዘጋጀት የንግግሩን ረቂቅ ብዙ መለዋወጥ ሊጠይቅባቸው ይችላል። ታዲያ ይህ የሚወስደው ጊዜ ቀላል አይደለም።
አንተስ ንግግርህን የምትዘጋጀው በዚህ መንገድ ነው? ይበልጥ ቀለል ያለ ዘዴ ማወቅ ትፈልጋለህ? አስተዋጽኦ ማዘጋጀት የሚቻልበትን መንገድ አንዴ ካወቅህ ሁሉንም ነገር መጻፍ አያስፈልግህም። ይህም የንግግሩን አቀራረብ ለመለማመድ በቂ ጊዜ እንድታገኝ ያስችልሃል። በዚህ መንገድ ከተዘጋጀህ ንግግሩን ማቅረብ የማትቸገር ከመሆኑም በላይ ንግግርህ ለአድማጮች ጆሮ የሚጥምና ለሥራ የሚያነሳሳ ይሆናል።
እርግጥ በጉባኤ ለሚቀርቡት የሕዝብ ንግግሮች ዋናው አስተዋጽኦ ተዘጋጅቶ ይሰጣል። ይሁን እንጂ ለአብዛኞቹ ሌሎች ንግግሮች አስተዋጽኦ ተዘጋጅቶ አይሰጥም። ምናልባት የሚሰጥህ የንግግርህ ርዕሰ ጉዳይ ወይም ጭብጥ ብቻ ይሆናል። ወይም ደግሞ ከአንድ የተወሰነ ጽሑፍ ላይ ንግግር እንድታቀርብ ልትጠየቅ ትችላለህ። አንዳንድ ጊዜ ደግሞ ጥቂት መመሪያ ብቻ ይሰጥህ ይሆናል። እንዲህ ላሉት ክፍሎች በሙሉ የራስህን አስተዋጽኦ ማዘጋጀት ያስፈልግሃል።
በገጽ 41 ላይ የሚገኘው ናሙና አጠር ያለ አስተዋጽኦ እንዴት ማዘጋጀት እንደሚቻል ይጠቁምሃል። ዋና ዋናዎቹ ነጥቦች በስተግራ በኩል ወጣ ብለው እንደሚጀምሩና ጎላ ብለው እንደተጻፉ ልብ በል። በእያንዳንዱ ዋና ነጥብ ሥር ያንን የሚደግፉ ሐሳቦች ተጠቅሰዋል። እነዚህን ሐሳቦች ለማዳበር የሚረዱ ተጨማሪ ነጥቦች ደግሞ ወደ ቀኝ ትንሽ ገባ ብለው ተጽፈዋል። ይህን አስተዋጽኦ በደንብ ተመልከተው። ሁለቱ ዋና ዋና ነጥቦች ከጭብጡ ጋር በቀጥታ እንደሚያያዙ አስተውል። ከሥር የተጠቀሱት ንዑስ ነጥቦችም ቢሆኑ እንዲያው የሚስቡ ስለሆኑ ብቻ እንዳልተጻፉ ልብ በል። ከዚህ ይልቅ እያንዳንዱ ነጥብ ከላዩ ያለውን ዋና ነጥብ የሚደግፍ ነው።
የምታዘጋጀው አስተዋጽኦ ሙሉ በሙሉ ይህንን ናሙና የሚመስል ላይሆን ይችላል። ይሁን እንጂ እስካሁን የተወያየንበት ነጥብ መሠረታዊ ሐሳብ ከገባህ ነጥቦችህን አደራጅተህ ሚዛናዊ በሆነ የጊዜ ገደብ ውስጥ ጥሩ ንግግር ለማዘጋጀት ትችላለህ። ታዲያ ምን ማድረግ ይኖርብሃል?
ማጤን፣ መምረጥና ማደራጀት
አንድ ጭብጥ ሊኖርህ ይገባል። የምትመርጠው ጭብጥ ግን በአንድ ቃል ሊገለጽ የሚችል ሰፊ ርዕሰ ጉዳይ መሆን የለበትም። ጭብጡ ልታስተላልፈው የምትፈልገው ማዕከላዊ ሐሳብ ሲሆን ርዕሰ ጉዳዩን ከምን አቅጣጫ ለማብራራት እንዳቀድህ የሚያሳይ ነው። ጭብጡ ከተሰጠህ በዚያ ውስጥ ያሉትን መሠረታዊ ቃላት በሚገባ ለማጤን ሞክር። የተሰጠህን ጭብጥ በአንድ ጽሑፍ ላይ ተመሥርተህ የምታዳብረው ከሆነ ጭብጡን በአእምሮህ ይዘህ ጽሑፉን በሚገባ አጥና። ርዕሰ ጉዳዩ ብቻ ከተሰጠህ ደግሞ ጭብጡን የምትመርጠው አንተ ነህ ማለት ነው። ይሁን እንጂ ይህን ከማድረግህ በፊት አንዳንድ ምርምር ማድረጉ ጠቃሚ ነው። ብዙውን ጊዜ ተጨማሪ ሐሳቦች ለማግኘት ሰፋ አድርገህ ማሰብ ያስፈልግሃል።
ይህን ስታደርግ ‘ይህ ትምህርት ለአድማጮች አስፈላጊ የሆነው ለምንድን ነው? ዓላማዬ ምንድን ነው?’ እያልክ ራስህን ጠይቅ። ዓላማህ እንዲሁ ትምህርቱን ማቅረብ ወይም ንግግርህን ማራኪ ማድረግ ሳይሆን አድማጮችህን አንድ ጠቃሚ ሐሳብ ማስጨበጥ መሆን አለበት። የንግግርህ ዓላማ ፈር ከያዘ በኋላ በጽሑፍ አስፍረው። በምትዘጋጅበት ጊዜ ይህን የንግግርህን ዓላማ መርሳት የለብህም።
የንግግርህን ዓላማ ካወቅህና ከዚያ ጋር የሚስማማ ጭብጥ ከመረጥህ በኋላ (ወይም የተሰጠህ ጭብጥ ከዚህ ዓላማህ ጋር እንዴት እንደሚጣጣም ካጤንክ በኋላ) በተፈለገው ነጥብ ላይ ያተኮረ ምርምር ማድረግ ትችላለህ። ለአድማጮችህ ይበልጥ ጠቃሚ ይሆናል የምትለውን ሐሳብ ፈልግ። እንዲሁ በደፈናው ብዙ ነገር በሚዳስስ ሐሳብ ሳይሆን ግንዛቤ በሚያሰፋና ጠቃሚ በሆነ ተጨባጭ ነጥብ ላይ አተኩር። አብዛኛውን ጊዜ ልትጠቀምበት ከምትችለው በላይ ብዙ ሐሳብ ስለምታገኝ የምታደርገውን ምርምር በተመለከተ ሚዛናዊና መራጭ መሆን ያስፈልግሃል።
ጭብጥህን ለማዳበርና ዓላማህን ዳር ለማድረስ የምትጠቀምባቸውን ዋና ዋና ነጥቦች ለይ። እነዚህ ነጥቦች የአስተዋጽኦህ መዋቅር ወይም መሠረት ይሆናሉ ማለት ነው። ዋና ዋና ነጥቦቹ ምን ያህል መሆን ይኖርባቸዋል? አጠር ላለ ንግግር ምናልባት ሁለት ዋና ነጥቦች በቂ ሊሆኑ ይችላሉ። ለአንድ ሰዓት ንግግር እንኳ በአብዛኛው አምስት ዋና ዋና ነጥቦች በቂ ናቸው። ዋና ዋና ነጥቦቹ ጥቂት ከሆኑ አድማጮችህ በቀላሉ ሊያስታውሷቸው ይችላሉ።
ጭብጡና ዋና ዋና ነጥቦቹ ምን እንደሆኑ ካወቅህ በኋላ ምርምር አድርገህ ያገኘሃቸውን ሐሳቦች በቅደም ተከተል አስቀምጥ። ከዋና ዋና ነጥቦችህ ጋር በቀጥታ የሚዛመደው ነጥብ የትኛው እንደሆነ ለይ። አድማጮች ንግግርህን በጉጉት እንዲያዳምጡት የሚያስችሉ ዝርዝር ማብራሪያዎችን አክልበት። ለዋና ዋና ነጥቦችህ ድጋፍ የሚሆኑ ጥቅሶች በምትመርጥበት ጊዜ የጥቅሶቹን መልእክት በደንብ ለማብራራት የሚያስችሉ ሐሳቦችን በአእምሮህ ያዝ። እያንዳንዱ ሐሳብ ከየትኛው ዋና ነጥብ ሥር መቀመጥ እንዳለበት ከለየህ በኋላ በቦታ ቦታው አስቀምጥ። ምርምር ስታደርግ ካገኘሃቸው ሐሳቦች ውስጥ አንዳንዱ አድማጮችን ሊማርክ የሚችል ቢሆንም ከዋና ዋና ነጥቦችህ መካከል ከየትኛውም ጋር የማይዛመድ ከሆነ አውጣው። ወይም በሌላ ጊዜ እንድትጠቀምበት በፋይል አስቀምጠው። የተሻሉ ናቸው ያልካቸውን ብቻ መርጠህ አስቀር። ብዙ ነጥቦችን ለማካተት ከሞከርክ መጣደፍህ ስለማይቀር ንግግርህን ጥልቀት ባለው መንገድ ማቅረብ ትቸገራለህ። በተመደበልህ ጊዜ ውስጥ አድማጮችህን የሚጠቅሙ ጥቂት ነጥቦችን ብቻ ጥሩ አድርገህ ማቅረቡ የተሻለ ነው።
ነጥቦችህን ገና በቅደም ተከተል አላደራጀህ ከሆነ አሁን እንደዚያ ማድረግ ትችላለህ። የወንጌል ጸሐፊው ሉቃስ ከርዕሰ ጉዳዩ ጋር የሚዛመዱ ብዙ ሐሳቦች ካሰባሰበ በኋላ ‘እንደ ቅደም ተከተላቸው’ በማስቀመጥ ይህን አድርጓል። (ሉቃስ 1:3 አ.መ.ት ) ነጥቦችህን በጊዜ ቅደም ተከተላቸው ወይም በርዕስ በርዕሳቸው አደራጅተህ ምናልባትም መንስዔውንና ውጤቱን ወይም ችግሩንና መፍትሔውን በማፈራረቅ ዓላማህን ለማሳካት ውጤታማ ሆኖ ባገኘኸው መንገድ ልታቀርባቸው ትችላለህ። አድማጮችህ ከአንዱ ነጥብ ወደሌላው መሸጋገርህን ማስተዋል እስኪቸገሩ ድረስ በድንገት ከአንዱ ሐሳብ ወደሌላው ማለፍ የለብህም። የምታቀርባቸው ማስረጃዎች አድማጮች ትክክለኛ መደምደሚያ ላይ እንዲደርሱ የሚያደርጉ መሆን ይኖርባቸዋል። ነጥቦችህን ስታደራጅ አድማጮች ንግግርህን እንዴት እንደሚከታተሉት አስብ። ንግግርህን አንድ በአንድ መከታተል ይችላሉ? ይዘኸው ከተነሳኸው ዓላማ ጋር በሚስማማ መንገድ ለሥራ ያነሳሳቸዋል?
በመቀጠል ደግሞ አድማጮችህ ስለ ርዕሰ ጉዳዩ የማወቅ ጉጉት እንዲያድርባቸው የሚያደርግ እንዲሁም የምታቀርበው ንግግር ምን ያህል አስፈላጊ እንደሆነ እንዲያስተውሉ የሚረዳ መግቢያ አዘጋጅ። እንዲህ በምታደርግበት ጊዜ የመጀመሪያዎቹን ጥቂት ዓረፍተ ነገሮች መጻፍህ ጥሩ ሊሆን ይችላል። በመጨረሻም የተነሳህበትን ዓላማ ዳር ለማድረስ የሚያግዝ ቀስቃሽ መደምደሚያ አዘጋጅ።
አስተዋጽኦህን ቀደም ብለህ ካዘጋጀህ ንግግሩን ከማቅረብህ በፊት አንዳንድ ጥቃቅን ማስተካከያዎችን በማድረግ ንግግሩን ይበልጥ ለማሻሻል የሚያስችል ጊዜ ታገኛለህ። ለአንዳንዶቹ ነጥቦች ድጋፍ የሚሆኑ አኃዛዊ መረጃዎች፣ ምሳሌዎች ወይም ተሞክሮዎች እንደሚያስፈልግህ ይሰማህ ይሆናል። አንድ በቅርቡ የተፈጸመ ሁኔታ ወይም የአድማጮችህን ትኩረት ሊስብ የሚችል ከአካባቢህ የተገኘ መረጃ መጠቀም አድማጮችህ የትምህርቱን አስፈላጊነት በቀላሉ እንዲያስተውሉ ሊረዳቸው ይችላል። ንግግርህን ስትከልስ ትምህርቱን ለአድማጮችህ እንደሚስማማ አድርገህ ማቅረብ የምትችልባቸው አጋጣሚዎች ይበልጥ ግልጽ ይሆኑልህ ይሆናል። ነጥቦቹን እንደገና ማጤንና አንዳንድ ማሻሻያዎችን ማድረግ አንድን ትምህርት ጠቃሚና ውጤታማ በሆነ መንገድ ለማቅረብ ወሳኝነት አለው።
አንዳንድ ተናጋሪዎች ከሌሎቹ ይበልጥ በዛ ያለ ማስታወሻ መያዝ ያስፈልጋቸው ይሆናል። ትምህርቱን ያዋቀርከው በጥቂት ዋና ነጥቦች ላይ ብቻ ከሆነ እነዚህን ዋና ነጥቦች ለመደገፍ የግድ የማያስፈልጉትን ሐሳቦች በማውጣት ነጥቦቹን በቅደም ተከተላቸው አስቀምጥ። በዚህ ረገድ ተሞክሮ እያዳበርክ ስትሄድ ሁሉንም ነገር መጻፍ እንደማያስፈልግህ ትገነዘባለህ። ይህ ጊዜ በጣም ይቆጥብልሃል፤ የንግግርህም ጥራት ይሻሻላል። እንዲህ ስታደርግ በቲኦክራሲያዊ የአገልግሎት ትምህርት ቤት ከሚሰጠው ሥልጠና እየተጠቀምህ እንዳለህ በግልጽ ይታያል።
-
-
በትምህርት ቤቱ የሚሰጡህን የተማሪ ክፍሎች መዘጋጀትበቲኦክራሲያዊ የአገልግሎት ትምህርት ቤት ከሚሰጠው ሥልጠና ተጠቀም
-
-
በትምህርት ቤቱ የሚሰጡህን የተማሪ ክፍሎች መዘጋጀት
በትምህርት ቤቱ የምታቀርበው እያንዳንዱ ክፍል እድገት ማድረግ የምትችልበትን አጋጣሚ ለማግኘት ይረዳሃል። ከልብ ጥረት የምታደርግ ከሆነ አንተም እድገት እያደረግህ እንዳለ ይታወቅሃል፤ ሌሎችም ይህንን ማስተዋላቸው አይቀርም። (1 ጢሞ. 4:15) ትምህርት ቤቱ ችሎታዎችህን ይበልጥ እያሻሻልህ እንድትሄድ ያግዝሃል።
በጉባኤ ክፍል ስለማቅረብ ስታስብ ፍርሃት ፍርሃት ይልሃል? በትምህርት ቤቱ ክፍል ስታቀርብ የመጀመሪያህ ባይሆንም እንኳ እንዲህ ዓይነት ስሜት ሊሰማህ ይችላል። ይሁን እንጂ ይህን ፍርሃትህን ሊያቃልሉልህ የሚችሉ አንዳንድ ነገሮች ይኖራሉ። እቤትህ ስትሆን ድምፅህን ከፍ አድርገህ የማንበብ ልማድ ይኑርህ። በጉባኤ ስብሰባዎች ላይ በተደጋጋሚ መልስ ለመስጠት ሞክር። አስፋፊ ከሆንህ ደግሞ ዘወትር በአገልግሎት ተካፈል። ይህም በሰዎች ፊት የመናገር ልምድ እንድታዳብር ይረዳሃል። ከዚህም በተጨማሪ ክፍልህን ቀደም ብለህ ተዘጋጅና እንደምታቀርበው ሆነህ ድምፅህን ከፍ አድርገህ ተለማመደው። ክፍልህን የምታቀርበው ቀና አመለካከት ላላቸው አድማጮች መሆኑን አስታውስ። ማንኛውንም ክፍል ከማቅረብህ በፊት ወደ ይሖዋ ጸልይ። ይሖዋ ወደ እርሱ ለሚጸልዩ አገልጋዮቹ መንፈስ ቅዱሱን በልግስና ይሰጣቸዋል።—ሉቃስ 11:13፤ ፊልጵ. 4:6, 7
በአንድ ጊዜ ተሞክሮ ያለው ተናጋሪ መሆን ወይም በማስተማር ረገድ ውጤታማ ሆኖ መገኘት ስለማይቻል ተዓምራዊ ለውጥ አደርጋለሁ ብለህ አትጠብቅ። (ሚክ. 6:8) ለትምህርት ቤቱ አዲስ ተማሪ ከሆንክ ገና በመጀመሪያው በሁሉም ረገድ የተዋጣለት ክፍል አቀርባለሁ ብለህ አታስብ። ከዚህ ይልቅ አንድ ክፍል ስታቀርብ በአንድ ምክር መስጫ ነጥብ ላይ ብቻ አተኩር። የምክር መስጫ ነጥቡ የተብራራበትን የዚህን መጽሐፍ ክፍል አጥና። የተሰጠውንም መልመጃ ለመለማመድ ሞክር። ይህም ክፍልህን ከማቅረብህ በፊት ከምክር መስጫ ነጥቡ ጋር በደንብ እንድትተዋወቅ የሚረዳህ ከመሆኑም ሌላ እንድትሻሻል ያግዝሃል።
በንባብ የሚቀርብ ክፍል መዘጋጀት
ለሌሎች ለማንበብ ስትዘጋጅ በጽሑፉ ላይ ያሉትን ቃላት ማንበብ መቻልህ ብቻውን በቂ አይደለም። የትምህርቱ መልእክት ምን እንደሆነ ለመረዳት ጥረት አድርግ። ይህን ግብ በመያዝ ክፍሉ እንደተሰጠህ ወዲያው አንብበው። ንባብህ ሐሳቡን በትክክል የሚያስተላልፍና ተገቢውን ስሜት የሚያንጸባርቅ እንዲሆን እያንዳንዱ ዓረፍተ ነገር የሚያስተላልፈውን መልእክት ለመረዳትና የእያንዳንዱን አንቀጽ ዋና ነጥብ ለማግኘት ሞክር። የሚቻል ከሆነ እንግዳ የሆኑትን ቃላት ትክክለኛ አነባበብ ለማወቅ ሌላ ሰው ጠይቅ። ትምህርቱ በደንብ ይግባህ። በዚህ ረገድ ወላጆች ትናንሽ ልጆቻቸውን መርዳት ያስፈልጋቸው ይሆናል።
ክፍልህ አንድን የመጽሐፍ ቅዱስ ምዕራፍ ወይም የተወሰኑ የመጠበቂያ ግንብ አንቀጾች በማንበብ የሚቀርብ ነውን? የምታነብበው ጽሑፍ በቋንቋህ በካሴት የተዘጋጀ ከሆነ ይህንን ካሴት በማዳመጥ የቃላቱን አነባበብ፣ አሰባበሩን፣ ግነቱን እንዲሁም የድምፅ ቃናና ፍጥነት አለዋወጡን ልብ ብሎ ማዳመጡ ሊጠቅምህ ይችላል። ከዚያም የሰማሃቸውን ነገሮች በንባብህ ለማንጸባረቅ ሞክር።
ክፍልህን መዘጋጀት ከመጀምረህ በፊት፣ የተሰጠህን የምክር መስጫ ነጥብ የሚያብራራውን ትምህርት በጥንቃቄ ማጥናት ይኖርብሃል። የተሰጠህን ክፍል ደጋግመህ ከተለማመድህ በኋላ ከቻልህ ይህንኑ ትምህርት እንደገና ከልሰው። በተቻለ መጠን ይህን ምክር ተግባራዊ ለማድረግ ጣር።
በዚህ መንገድ የምታገኘው ሥልጠና ለአገልግሎት ይጠቅምሃል። በመስክ አገልግሎት ስትካፈል ለሌሎች የምታነብባቸው ብዙ አጋጣሚዎች ይኖሩሃል። የአምላክ ቃል የሰዎችን ሕይወት የመለወጥ ኃይል ስላለው ስታነብብ ጥሩ አድርገህ ማንበብህ በጣም አስፈላጊ ነው። (ዕብ. 4:12) አንድ ወይም ሁለት ክፍል ስላቀረብህ ብቻ ንባብን ውጤታማ በሚያሰኙት ዘርፎች ሁሉ ይዋጣልኛል ብለህ አታስብ። ሐዋርያው ጳውሎስ የብዙ ዓመታት ተሞክሮ ለነበረው ክርስቲያን ሽማግሌ ሲጽፍ “እኔ እስክመጣ ድረስ ቅዱሳት መጻሕፍትን ለሕዝብ በማንበብ . . . ትጋ” ብሎታል።—1 ጢሞ. 4:13 የ1980 ትርጉም
ከጭብጡና ከመቼቱ ጋር የሚስማማ ዝግጅት
በትምህርት ቤቱ እንድታቀርበው የተሰጠህ ክፍል መቼት ያለው ከሆነ ምን ማድረግ ይኖርብሃል?
ትኩረት የሚያሻቸው ሦስት ዋና ዋና ነገሮች አሉ። እነዚህም:- (1) የተመደበልህ ጭብጥ (2) መቼትህና የምታነጋግረው ሰው እንዲሁም (3) እንድትሠራበት የተሰጠህ ምክር መስጫ ነጥብ ናቸው።
ለተሰጠህ ጭብጥ የሚስማሙ ነጥቦችን ማሰባሰብ ያስፈልግሃል። ይሁን እንጂ ብዙ ከመግፋትህ በፊት ስለ መቼትህና ስለምታነጋግረው ሰው በጥሞና አስብ። ምክንያቱም መቼትህና የምታነጋግረው ሰው ማንነት የምታቀርባቸውን ነጥቦችና የትምህርቱን አቀራረብ ይወስናሉ። የምትጠቀመው መቼት ምን ዓይነት ነው? ለምታውቀው ሰው ምሥራቹን እንዴት እንደምታቀርብ የሚያሳይ ነው? ወይስ አንድን ሰው ለመጀመሪያ ጊዜ ስታነጋግር የሚያሳይ? ግለሰቡ በዕድሜ ከአንተ ይበልጣል ወይስ ያንሳል? ልታወያየው ስላሰብከው ርዕሰ ጉዳይ ምን ዓይነት አመለካከት ሊኖረው ይችላል? ስለዚህ ርዕሰ ጉዳይስ ከአሁን ቀደም ምን የሚያውቀው ነገር ይኖራል? ውይይቱን ስታደርግ ይዘኸው የተነሣኸው ዓላማ ምንድን ነው? ለእነዚህ ጥያቄዎች የምትሰጠው መልስ ምን ማድረግ እንዳለብህ ይጠቁምሃል።
የተሰጠህን ጭብጥ ለማዳበር የሚረዳ ሐሳብ ከየት ማግኘት ትችላለህ? በዚሁ መጽሐፍ ከገጽ 33 እስከ 38 ላይ “ምርምር ማድረግ የሚቻለው እንዴት ነው?” በሚል ርዕስ የቀረበ ትምህርት አለ። ይህንን ምዕራፍ አንብብና ልታገኛቸው የምትችላቸውን ለምርምር የሚረዱ ጽሑፎች ተጠቀም። በአጭር ጊዜ ውስጥ ከምትፈልገው በላይ ብዙ ሐሳቦችን እንደምታገኝ እሙን ነው። ስለዚህ ርዕሰ ጉዳይ ምን ያህል መረጃ ማግኘት እንደምትችል ለማወቅ አቅምህ የፈቀደውን ያህል አንብብ። ይሁን እንጂ በዚህ ጊዜ ለክፍልህ ልትጠቀምበት ያሰብከውን መቼትም ሆነ የምታነጋግረውን ግለሰብ ማንነት ግምት ውስጥ ማስገባት ይኖርብሃል። ተስማሚ ሆነው ያገኘሃቸው ነጥቦች ላይ ምልክት አድርግ።
ለክፍልህ የሚሆኑትን ነጥቦች መርጠህ ከማጠናቀቅህ በፊት የተሰጠህን የምክር መስጫ ነጥብ አንብብ። ክፍል የምታቀርብበት ዋናው ምክንያት የምክር መስጫ ነጥቡን እንድትሠራበት ነው።
የተመደበልህ ጊዜ ካለቀ ማቆም ስላለብህ ነጥቦችህን በተሰጠህ ጊዜ ውስጥ መጨረስህ ንግግርህን ባሰብከው መንገድ በመደምደም እርካታ እንድታገኝ ያስችልሃል። በመስክ አገልግሎት ግን የሰዓት ጉዳይ ሁልጊዜ አሳሳቢ ላይሆን ይችላል። ስለዚህ ስትዘጋጅ ምን ያህል ጊዜ እንደ ተሰጠህ ግምት ውስጥ አስገባ። ሆኖም ትልቁ ነገር ትምህርቱን በጥሩ ሁኔታ ማቅረብህ ነው።
ስለ መቼቱ ጥቂት እንበል:- በገጽ 82 ላይ የቀረቡትን ሐሳቦች በመመርመር በአገልግሎትህ የሚጠቅምህንና ትምህርቱን ተግባራዊ በሆነ መንገድ ለማቅረብ የሚረዳህን አንድ መቼት ምረጥ። በትምህርት ቤቱ ክፍል ስታቀርብ ቆይተህ ከሆነ ይህንን አጋጣሚ ለተጨማሪ ኃላፊነት ብቁ ሆኖ ለመገኘትና ለአገልግሎት የሚረዳህን ችሎታ ለማዳበር ተጠቀምበት።
መቼቱን የሰጠህ የቲኦክራሲያዊ የአገልግሎት ትምህርት ቤት የበላይ ተመልካቹ ከሆነ በዚህ በተሰጠህ መቼት ለመሥራት ሞክር። ብዙዎቹ መቼቶች ከአገልግሎት ጋር የተያያዙ ናቸው። እንዲህ ዓይነቱን መቼት በአገልግሎት ተጠቅመህበት የማታውቅ ከሆነ በዚህ ረገድ ተሞክሮ ያላቸውን አስፋፊዎች ምክር ጠይቅ። ከቻልክ በትምህርት ቤቱ ልትጠቀምበት ያሰብከውን መቼት ተጠቅመህ የክፍልህን ነጥቦች በአገልግሎት ከምታገኘው ሰው ጋር ተወያይባቸው። ይህን ማድረግህ የሥልጠናውን ዋና ዓላማ ዳር ለማድረስ ይረዳሃል።
በንግግር የሚቀርብ ክፍል
ወንዶች አጭር ንግግር ለጉባኤው እንዲያቀርቡ ይመደባሉ። እነዚህን ክፍሎች ስትዘጋጅ ልታስብባቸው የሚገቡት መሠረታዊ ነጥቦች በሠርቶ ማሳያ የሚቀርቡትን የተማሪ ክፍሎች በተመለከተ ከተጠቀሱት ጋር ተመሳሳይ ናቸው። ጉልህ ልዩነት የሚኖረው በአድማጮችና በአቀራረብ ረገድ ነው።
አብዛኛውን ጊዜ ሁሉም አድማጮች ከትምህርቱ ሊጠቀሙ በሚችሉበት መንገድ መዘጋጀቱ የተሻለ ይሆናል። በስብሰባው ላይ ከተገኙት መካከል አብዛኞቹ መሠረታዊ የሆኑትን የመጽሐፍ ቅዱስ እውነቶች ያውቃሉ። የምታቀርበውንም ርዕሰ ጉዳይ በደንብ ያውቁት ይሆናል። ስለዚህ ርዕሰ ጉዳይ የሚያውቁት ምን ያህል ነው የሚለውን ግምት ውስጥ አስገባ። አድማጮችህ ከምታቀርበው ክፍል በሆነ መልኩ ጥቅም እንዲያገኙ ለመርዳት ጥረት አድርግ። ራስህን እንዲህ እያልክ ጠይቅ:- ‘ይህ ርዕሰ ጉዳይ እኔም ሆንኩ አድማጮቼ ለይሖዋ ያለንን አድናቆት እንድናሳድግ የሚረዳን እንዴት ነው? ትምህርቱ የአምላክን ፈቃድ እንድናስተውል የሚረዳን እንዴት ነው? የሥጋ ምኞት ገንኖ በሚታይበት ዓለም ውስጥ ጤናማ ውሳኔ ለማድረግ የሚረዳን እንዴት ነው?’ (ኤፌ. 2:3) ለእነዚህ ጥያቄዎች አጥጋቢ መልስ ለማግኘት ምርምር ማድረግ ያስፈልጋል። መጽሐፍ ቅዱስ ስትጠቅስ ጥቅሶቹን አንብበህ ብቻ ከማለፍ ይልቅ ልታብራራቸው እንዲሁም እነዚህ ጥቅሶች ወደ አንድ መደምደሚያ ለመድረስ የሚረዱት እንዴት እንደሆነ ግልጽ ልታደርግ ይገባል። (ሥራ 17:2, 3) ብዙ ነጥብ ለማካተት አትሞክር። ትምህርቱን በቀላሉ ማስታወስ በሚያስችል መንገድ አቅርበው።
በዝግጅትህ ወቅት ስለ አቀራረብህም ልታስብ ይገባል። ይህ ትኩረት ልትሰጠው የሚገባ ጉዳይ ነው። ክፍልህን ለሌሎች እንደምታቀርብ ሆነህ ተለማመድ። የተለያዩ የንግግር ባሕርያትን ለማጥናትና ምክሩን ሥራ ላይ ለማዋል የምታደርገው ጥረት ለእድገትህ ከፍተኛ አስተዋጽኦ ይኖረዋል። አዲስም ሆንክ ልምድ ያለህ ተናጋሪ በጉዳዩ እንደምታምንበት በሚያሳይ መንገድና ለትምህርቱ በሚስማማ ስሜት ለመናገር እንድትችል ጥሩ ዝግጅት አድርግ። በትምህርት ቤቱ የሚሰጥህን እያንዳንዱን ክፍል ተዘጋጅተህ ስታቀርብ ዓላማህ ይሖዋ የሰጠህን የንግግር ችሎታ ለእርሱ ክብር በሚያመጣ መንገድ መጠቀም እንደሆነ አትዘንጋ።—መዝ. 150:6
-
-
ለጉባኤ የሚቀርቡ ንግግሮችን መዘጋጀትበቲኦክራሲያዊ የአገልግሎት ትምህርት ቤት ከሚሰጠው ሥልጠና ተጠቀም
-
-
ለጉባኤ የሚቀርቡ ንግግሮችን መዘጋጀት
በቲኦክራሲያዊ የአገልግሎት ትምህርት ቤት ውስጥ የሚካተቱት ክፍሎች ለሁሉም የጉባኤ አባላት ጥቅም ታስበው የሚዘጋጁ ናቸው። ከዚህ በተጨማሪ በሌሎቹ የጉባኤ ስብሰባዎች፣ በወረዳና በልዩ እንዲሁም በአውራጃ ስብሰባዎች ላይ ጠቃሚ ትምህርቶች ይቀርባሉ። ከእነዚህ ስብሰባዎች በአንዱ ላይ ክፍል እንድታቀርብ ከተመደብህ ከባድ ኃላፊነት ተጥሎብሃል ማለት ነው። ሐዋርያው ጳውሎስ ክርስቲያን የበላይ ተመልካች የነበረው ጢሞቴዎስ ለማስተማር ሥራው እንዲጠነቀቅ አሳስቦታል። (1 ጢሞ. 4:16) ከአምላክ ጋር ስላላቸው ዝምድና ለመማር በክርስቲያናዊ ስብሰባዎች ላይ የሚገኙ ሁሉ ወደ እነዚህ ስብሰባዎች የሚመጡት ውድ ጊዜያቸውን ሠውተው ነው። አንዳንዶቹም ተጨማሪ መሥዋዕትነት ይጠይቅባቸዋል። በእርግጥም ከአምላክ ጋር ያላቸውን ዝምድና በተመለከተ ሰዎችን ማስተማር ትልቅ መብት ነው! ታዲያ ይህንን መብት በአግባቡ ልትጠቀምበት የምትችለው እንዴት ነው?
የመጽሐፍ ቅዱስ ንባብ ጎላ ያሉ ነጥቦች
በትምህርት ቤቱ የሚቀርበው ይህ ክፍል ለሳምንቱ በሚመደበው የመጽሐፍ ቅዱስ ንባብ ላይ የተመሠረተ ነው። ትምህርቱ እኛን እንዴት ይነካናል የሚለው ጉዳይ ይበልጥ ትኩረት ሊሰጠው ይገባል። በነህምያ 8:8 ላይ እንደተገለጸው ዕዝራና አብረውት የነበሩት ሰዎች የአምላክን ቃል ለሕዝቡ እያነበቡ በማብራራትና ‘ትርጉሙን በማስረዳት’ ሕዝቡ ማስተዋል እንዲያገኝ አድርገዋል። አንተም የመጽሐፍ ቅዱስ ንባብ ጎላ ያሉ ነጥቦችን በምታቀርብበት ጊዜ እንዲህ ማድረግ ትችላለህ።
ይህን ክፍል ለማቅረብ መዘጋጀት የሚኖርብህ እንዴት ነው? ከቻልክ ክፍሉ የሚቀርብባቸውን የመጽሐፍ ቅዱስ ምዕራፎች ከአንድ ሳምንት ወይም ከዚያ ከሚበልጥ ጊዜ በፊት አስቀድመህ አንብብ። ከዚያም ስለ ጉባኤህና ጉባኤው ስለሚያስፈልገው ነገር አስብ። ክፍሉን ለጉባኤው በሚጠቅም መንገድ ማቅረብ እንድትችል ጸልይ። በእነዚህ የመጽሐፍ ቅዱስ ምዕራፎች ውስጥ ጉባኤው የሚያስፈልገውን ነገር በተመለከተ ምን ምክር፣ ምሳሌ እና መሠረታዊ ሥርዓት ይገኛሉ?
ምርምር ማድረግ የግድ አስፈላጊ ነው። የመጠበቂያ ግንብ ጽሑፎች ማውጫን ምርምር ለማድረግ ልትጠቀምበት ትችላለህ። በማውጫው ላይ ያሉትን ጽሑፎች ተመርኩዘህ በመረጥካቸው ጥቅሶች ላይ ምርምር ስታደርግ እውቀት ሰጪ የሆኑ ተጨማሪ ነጥቦች፣ ፍጻሜያቸውን ስላገኙ ትንቢቶች የተሰጠ ማብራሪያ፣ ጥቅሶቹ ስለ ይሖዋ ባሕርይ የሚገልጹትን እውነት በተመለከተ ወይም ስለ መሠረታዊ ሥርዓቶች የቀረበ ትምህርት ታገኝ ይሆናል። በጣም ብዙ ነጥቦች ለማብራራት አትሞክር። ከዚህ ይልቅ በተመረጡ ጥቂት ጥቅሶች ላይ ብቻ አተኩር። ጥቂት ቁጥሮች ላይ ብቻ አተኩሮ እነርሱን በሚገባ ማብራራቱ የተሻለ ይሆናል።
ክፍልህ አድማጮች ከሳምንቱ የመጽሐፍ ቅዱስ ንባብ ያገኙትን ጥቅም እንዲናገሩ መጋበዝን የሚያካትት ሊሆን ይችላል። ለግልም ሆነ ለቤተሰብ ጥናት ወይም ለአገልግሎት የሚጠቅም ወይም በሕይወታቸው የሚሠሩበት ምን ትምህርት አግኝተዋል? ይሖዋ ከሰዎችና ከብሔራት ጋር ባደረገው ግንኙነት ስላሳያቸው ባሕርያት ምን ይነግረናል? የአድማጮች እምነት እንዲጠነክርና ለይሖዋ ያላቸው አድናቆት እንዲጨምር የሚያደርግ ምን ትምህርት ይዟል? ዝርዝርና ውስብስብ ማብራሪያ ለመስጠት ከመሞከር ይልቅ የመረጥካቸውን ነጥቦች ትርጉምና ተግባራዊ ጠቀሜታ ጎላ አድርገህ ግለጽ።
ማስተማሪያ ንግግር
ይህ ንግግር በመጠበቂያ ግንብ ወይም በንቁ! መጽሔት ርዕስ ወይም ከአንድ መጽሐፍ በተወሰደ ክፍል ላይ ተመሥርቶ የሚቀርብ ነው። በአብዛኛው በተመደበልህ ጊዜ ውስጥ ልታቀርበው ከምትችለው በላይ ብዙ ነጥቦች ይኖራሉ። ታዲያ ይህን ክፍል ማቅረብ የሚኖርብህ እንዴት ነው? አድማጮችህን ማስተማር አለብህ እንጂ እንዲሁ ትምህርቱን መሸፈንህ ብቻ በቂ አይሆንም። አንድ የበላይ ተመልካች “ለማስተማር የሚበቃ” ሊሆን ይገባል።—1 ጢሞ. 3:2
ለመዘጋጀት ስትነሣ በመጀመሪያ እንድታቀርበው የተመደበውን ጽሑፍ አጥና። ጥቅሶቹን አውጥተህ አንብብ። አሰላስል። ይህንን ማድረግ ያለብህ ክፍልህን የምታቀርብበት ቀን ከመድረሱ በፊት ነው። ንግግሩ የተመሠረተበትን ጽሑፍ ወንድሞችም አንብበውት እንደሚመጡ አትዘንጋ። የአንተ ኃላፊነት ነጥቦቹን መከለስ ወይም ጨምቆ ማቅረብ ብቻ ሳይሆን ትምህርቱን እንዴት ተግባራዊ ማድረግ እንደሚቻል ማስረዳት ነው። ተስማሚ ሆነው ያገኘሃቸውን ነጥቦች ጉባኤውን ሊጠቅም በሚችል መንገድ አቅርባቸው።
እያንዳንዱ ልጅ የየራሱ ባሕርይ እንዳለው ሁሉ እያንዳንዱ ጉባኤም ልዩ የሚያደርገው የራሱ ባሕርይ ይኖረዋል። አንድ ወላጅ የሚያስተምረው ነገር ውጤት እንዲኖረው ከፈለገ የሥነ ምግባር መመሪያዎችን በመዘርዘር ብቻ አይወሰንም። አሳማኝ በሆነ መንገድ ያስረዳል። የልጁን ባሕርይና የሚያጋጥሙትን ችግሮች ግምት ውስጥ ያስገባል። በተመሳሳይም በጉባኤ ውስጥ ያሉ አስተማሪዎች አድማጮቻቸው ምን እንደሚያስፈልጋቸው በመገንዘብ ተስማሚ የሆነ ትምህርት ለማቅረብ ይጥራሉ። ይሁን እንጂ አስተዋይ የሆነ አስተማሪ በአድማጮቹ መካከል ያሉ ግለሰቦችን የሚያሸማቅቅ ምሳሌ አይጠቀምም። በይሖዋ መንገድ መመላለስ ያስገኘላቸውን ጥቅም ይጠቅሳል። እንዲሁም የጉባኤው አባላት የሚገጥማቸውን ችግር በተሳካ ሁኔታ ለመወጣት የሚረዱ ቅዱስ ጽሑፋዊ ምክሮችን ጎላ አድርጎ ይገልጻል።
ጥሩ የማስተማር ችሎታ የአድማጮችን ልብ ለመንካት ያስችላል። ይህ ደግሞ እውነታውን ከማስቀመጥ አልፎ የነጥቦቹን ትርጉም እንዲያስተውሉ መርዳትን ይጠይቃል። እንዲሁም ለአድማጮች ከልብ አሳቢነት ማሳየትን ይጨምራል። መንፈሳዊ እረኞች በጉባኤያቸው ያሉትን ወንድሞችና እህቶች በደንብ ሊያውቋቸው ይገባል። የጉባኤው አባላት ስለሚገጥሟቸው የተለያዩ ችግሮች ከልብ የሚያስቡ ከሆነ ችግራቸውን በመረዳት፣ በርኅራኄና በአዘኔታ ስሜት የሚያበረታታ ንግግር ያቀርባሉ።
ጥሩ አስተማሪ አንድ ንግግር ግልጽ የሆነ ዓላማ ሊኖረው እንደሚገባ ያውቃል። የትምህርቱ ዋና ዋናዎቹ ነጥቦች ጎላ ብለው እንዲታዩ በሚያስችል መንገድ መቅረብ ይኖርበታል። ይህም እነዚህን ነጥቦች በቀላሉ ለማስታወስ ያስችላል። አድማጮች ሊሠሩባቸው የሚችሏቸውን ነጥቦች መጨበጥ መቻል አለባቸው።
የአገልግሎት ስብሰባ
በመንግሥት አገልግሎታችን ላይ የሚወጡትን ክፍሎች የምታቀርብበት መንገድ ትንሽ ለየት ያለ ሊሆን ይችላል። እንዲህ ዓይነቱ ክፍል ብዙውን ጊዜ ጽሑፉ ላይ ያለውን ሐሳብ በሙሉ ማቅረብን እንጂ ይበልጥ ተስማሚ የሆነው ነጥብ የትኛው ነው ብሎ መምረጥን አይጠይቅም። አድማጮች በክፍሉ ውስጥ ለቀረበው ምክር ሁሉ መሠረት የሆነው የመጽሐፍ ቅዱስ ጥቅስ በደንብ እንዲገባቸው አድርግ። (ቲቶ 1:9) በአብዛኛው የሚመደበው ጊዜ ውስን ስለሆነ ተጨማሪ ነጥቦች ማካተት አይቻልም።
በሌላ በኩል ደግሞ ክፍሉ እዚያ የመንግሥት አገልግሎታችን ላይ ላይኖር ይችላል። ምናልባት በመጠበቂያ ግንብ ላይ የወጣ ርዕስ ተጠቅሶ ሊሆን ይችላል። አለዚያም በመንግሥት አገልግሎታችን ላይ የተሰጠህ ስለ ክፍሉ የሚገልጽ ጥቂት ሐሳብ ብቻ ይሆናል። ከቀረበው ትምህርት ጋር በተያያዘ ጉባኤው የሚያስፈልገውን ነገር ግምት ውስጥ ማስገባት የአንተ ኃላፊነት ነው። የተፈለገውን ነጥብ የሚያስጨብጥ አጠር ያለ ምሳሌ ወይም ለትምህርቱ የሚስማማ ተሞክሮ መናገር ያስፈልግህ ይሆናል። የተጣለብህ ኃላፊነት ክፍሉን ማቅረብ ብቻ ሳይሆን የጉባኤው አባላት የአምላክ ቃል የሚያዝዘውን ሥራ እንዲሠሩና ይህንንም በደስታ እንዲያደርጉት በሚያበረታታ መንገድ ማስተማር እንደሆነ መዘንጋት የለብህም።—ሥራ 20:20, 21
ክፍልህን ስትዘጋጅ ስለ እያንዳንዱ የጉባኤው አባል አስብ። ስለሚያደርጉት ነገር አመስግናቸው። ክፍሉን በምታቀርብበት ጽሑፍ ላይ ያለውን ምክር ተግባራዊ ማድረጋቸው በአገልግሎት ይበልጥ ውጤታማና ደስተኛ እንዲሆኑ የሚረዳቸው እንዴት ነው?
ክፍልህ ሠርቶ ማሳያ ወይም ቃለ ምልልስ አለው? ከሆነ አስቀድመህ ጥሩ ዝግጅት ልታደርግበት ይገባል። ሠርቶ ማሳያ የሚያቀርቡትንም ሆነ ቃለ ምልልስ የምታደርግላቸውን ሰዎች ሌላ ሰው እንዲያዘጋጅልህ ትነግር ይሆናል። ይሁን እንጂ ይህ ሁልጊዜ ጥሩ ውጤት አይኖረውም። ሠርቶ ማሳያውንም ሆነ ቃለ ምልልሱን በተቻለ መጠን የስብሰባው ቀን ከመድረሱ በፊት ተለማመዱት። ይህ የንግግርህ ክፍል ስለሆነ ዋናውን ትምህርት በሚያጎለብት መንገድ እንዲቀርብ ማድረግ ይኖርብሃል።
ትላልቅ ስብሰባዎች
ግሩም መንፈሳዊ አቋም ያላቸው እንዲሁም ጥሩ የሕዝብ ተናጋሪና አስተማሪ የሆኑ ወንድሞች በትላልቅ ስብሰባዎች ላይ ክፍል እንዲያቀርቡ ይመደባሉ። እነዚህ ስብሰባዎች መንፈሳዊ ትምህርት የሚቀርብባቸው ለየት ያሉ አጋጣሚዎች ናቸው። ክፍሉን እንድታቀርብ ስትመደብ በንባብ የሚቀርበው ጽሑፍ፣ የንግግር አስተዋጽኦ፣ የመጽሐፍ ቅዱሳዊ ድራማ መመሪያ ወይም ጥቂት መመሪያዎችን የያዘ አንድ አንቀጽ ብቻ ይሰጥህ ይሆናል። እንዲህ ባሉ ስብሰባዎች ላይ ንግግር የማቅረብ መብት ስታገኝ የሚሰጥህን ክፍል ደጋግመህ አንብበው። የትምህርቱ ጠቀሜታ ግልጽ ሆኖ እስኪታይህ ድረስ በደንብ አጥናው።
በንባብ የሚቀርብ ንግግር እንዲሰጡ የተመደቡ ወንድሞች ምንም ሳይጨምሩና ሳይቀንሱ ማንበብ ይጠበቅባቸዋል። የቃላቱን ወይም የሐሳቡን አቀማመጥ አይቀይሩም። ዋና ዋና ነጥቦቹ የትኞቹ እንደሆኑና እንዴት እንደተዋቀሩ እስኪገባቸው ድረስ ያጠኑታል። በተገቢው ቦታ ላይ እያጠበቁ፣ በጋለ ስሜት፣ በወዳጃዊ መንፈስ፣ እንደሚያምኑበት በሚያሳይ መንገድና ለብዙ ተሰብሳቢዎች በሚመጥን የድምፅ መጠን ማቅረብ እስኪችሉ ድረስ ድምፃቸውን እያሰሙ ይለማመዱታል።
ከንግግር አስተዋጽኦ ክፍላቸውን እንዲያቀርቡ የሚመደቡ ወንድሞች እዚያ ላይ ካለው ሐሳብ ሳይወጡ ትምህርቱን እንዲያዳብሩ ይጠበቅባቸዋል። ተናጋሪው ከአስተዋጽኦው በቀጥታ ከማንበብ ወይም አስተዋጽኦውን በንባብ በሚቀርብ ንግግር መልክ ከማዘጋጀት ይልቅ መልእክቱን ተረድቶ በራሱ አባባል ሊያቀርበው ይገባል። ሁሉንም ዋና ዋና ነጥብ በደንብ ማብራራት እንዲችል በአስተዋጽኦው ላይ የተመደበውን እያንዳንዱን ጊዜ በጥብቅ መከተሉ በጣም አስፈላጊ ነው። ተናጋሪው በዋና ዋና ነጥቦቹ ሥር የተጠቀሱትን ሐሳቦችና ጥቅሶች ጥሩ አድርጎ ሊጠቀምባቸው ይገባል። እርሱ በግሉ የነኩትን ተጨማሪ ነጥቦች ለማስገባት ሲል የአስተዋጽኦውን ነጥቦች መተው አይኖርበትም። የትምህርቱ ዋና መሠረት የአምላክ ቃል ሊሆን እንደሚገባ ግልጽ ነው። የክርስቲያን ሽማግሌዎች ኃላፊነትም ‘ቃሉን መስበክ’ ነው። (2 ጢሞ. 4:1, 2) በመሆኑም አንድ ተናጋሪ በአስተዋጽኦው ላይ ያሉትን ጥቅሶች ትኩረት ሰጥቶ ማብራራትና ከነጥቡ ጋር እንዴት እንደሚዛመዱ ማስረዳት ይኖርበታል።
ዛሬ ነገ አትበል
በጉባኤህ በተደጋጋሚ ንግግር የመስጠት አጋጣሚ አለህ? ሁሉንም በደንብ መዘጋጀት የምትችለው እንዴት ነው? ባለቀ ሰዓት ክፍሎችህን ለመዘጋጀት ከምትጣደፍ ይልቅ አስቀድመህ ተዘጋጅ።
ጉባኤውን የሚጠቅም ክፍል ለማቅረብ አስቀድሞ በክፍሉ ላይ በደንብ ማሰብ ያስፈልጋል። እንግዲያው ክፍሉ እንደተሰጠህ የምታቀርበውን ትምህርት ወዲያውኑ የማንበብ ልማድ ሊኖርህ ይገባል። ይህም ሌላ ነገር እያደረግህም ትምህርቱን እንድታብላላው ይረዳሃል። ንግግሩን ከማቅረብህ በፊት ባሉት ቀናት ወይም ሳምንታት ትምህርቱን እንዴት በተሻለ መንገድ ተግባራዊ አድርገህ ማቅረብ እንደምትችል ለማስተዋል የሚረዱህን ሐሳቦች ትሰማ ይሆናል። የትምህርቱን አስፈላጊነት የሚያጠናክሩ ሁኔታዎችም ሊከሰቱ ይችላሉ። ክፍሉ እንደደረሰህ ማንበብና ስለእሱ ማሰብ መጀመር ጊዜ እንደሚወስድ የታወቀ ነው። ይሁንና ይህ በከንቱ የሚባክን ጊዜ አይደለም። አስቀድመህ ክፍሉን በሚገባ ማብላላትህ ያለውን ጥቅም የምታስተውለው የንግግርህን አስተዋጽኦ መዘጋጀት ስትጀምር ነው። በዚህ መንገድ መዘጋጀት በእጅጉ ውጥረት የሚቀንስ ከመሆኑም ሌላ ትምህርቱን ተግባራዊ በሆነና በጉባኤ ውስጥ ያሉትን አድማጮች በሚጠቅም መንገድ ለማቅረብ ያስችላል።
ይሖዋ ሕዝቡን ለማስተማር ካደረገው ዝግጅት ጋር በተያያዘ ላገኘኸው መብት ከፍ ያለ አድናቆት ካለህ ይሖዋን ታስከብራለህ፤ እርሱን የሚወድዱትን ሰዎችም ትጠቅማለህ።—ኢሳ. 54:13፤ ሮሜ 12:6-8
-
-
ለሕዝብ የሚቀርብ ንግግር መዘጋጀትበቲኦክራሲያዊ የአገልግሎት ትምህርት ቤት ከሚሰጠው ሥልጠና ተጠቀም
-
-
ለሕዝብ የሚቀርብ ንግግር መዘጋጀት
በአብዛኞቹ የይሖዋ ምሥክሮች ጉባኤዎች በየሳምንቱ በመጽሐፍ ቅዱስ ላይ የተመሠረተ የሕዝብ ንግግር ይቀርባል። ሽማግሌ ወይም የጉባኤ አገልጋይ ከሆንክ ጥሩ የሕዝብ ተናጋሪ ወይም አስተማሪ መሆንህ በግልጽ ይታያልን? እንደዚያ ከሆነ የሕዝብ ንግግር የማቅረብ አጋጣሚ ይሰጥህ ይሆናል። ቲኦክራሲያዊ የአገልግሎት ትምህርት ቤት በብዙ ሺህ የሚቆጠሩ ወንድሞች ለዚህ የአገልግሎት መብት ብቁ እንዲሆኑ ረድቷል። የሕዝብ ንግግር እንድታቀርብ በምትመደብበት ጊዜ ዝግጅትህን ለመጀመር በቅድሚያ ምን ማድረግ ይኖርብሃል?
አስተዋጽኦውን አጥና
ተጨማሪ ምርምር ማድረግ ከመጀመርህ በፊት አስተዋጽኦውን በማንበብና በዚያ ላይ በማሰላሰል የንግግሩን መልእክት ለማግኘት ሞክር። ጭብጡን ማለትም የንግግሩን ርዕስ አስብ። አድማጮችህን የምታስተምራቸው ስለ ምን ነገር ነው? ዓላማህ ምንድን ነው?
የንግግሩን ዋና ዋና ነጥብ ከያዙት ርዕሶች ጋር በሚገባ ተዋወቅ። እያንዳንዱ ዋና ነጥብ ከጭብጡ ጋር የሚያያዘው እንዴት ነው? በእነዚህ ነጥቦች ሥር የተወሰኑ ንዑስ ነጥቦች ተዘርዝረዋል። እነዚህን ንዑሳን ነጥቦች የሚደግፉ ሐሳቦች ደግሞ ከእነርሱ ሥር ይዘረዘራሉ። በእያንዳንዱ ንዑስ ርዕስ ሥር ያለው ሐሳብ ከፊተኛው ጋር የሚዛመደውና ወደሚቀጥለው ንዑስ ርዕስ የሚያሸጋግረው እንዴት እንደሆነ እንዲሁም የንግግሩን ዓላማ ለማሳካት ምን ሚና እንደሚጫወት ልብ በል። ጭብጡን ማለትም የንግግሩን ዓላማ ከተረዳህና ዋና ዋና ነጥቦቹ ይህንን ዓላማ የሚያሳኩት እንዴት እንደሆነ ከተገነዘብክ ትምህርቱን ለማዳበር ዝግጁ ነህ ማለት ነው።
መጀመሪያ ላይ ንግግርህን በየንዑስ ርዕሱ ከፋፍለህ ማየቱ ይጠቅምህ ይሆናል። ይህም ማለት አንዱን ንግግር የየራሳቸው ዋና ነጥብ ያላቸው አራት ወይም አምስት አጫጭር ንግግሮች ስብስብ አድርገህ ትመለከተዋለህ ማለት ነው። ከዚያም ተራ በተራ ተዘጋጃቸው።
አስተዋጽኦው የሚረዳህ ለዝግጅት ብቻ ነው። ንግግርህን በምትሰጥበት ጊዜ በቀጥታ እንደ ማስታወሻ እንድትጠቀምበት ታስቦ የተዘጋጀ አይደለም። አስተዋጽኦ የንግግሩ አፅም ብቻ ነው ለማለት ይቻላል። ይህን አፅም ሥጋ ልታለብሰውና ነፍስ ልትዘራበት ይገባል።
የጥቅሶች አጠቃቀም
ኢየሱስ ክርስቶስና ደቀ መዛሙርቱ የሚያስተምሩት ጥቅሶችን መሠረት በማድረግ ነበር። (ሉቃስ 4:16-21፤ 24:27፤ ሥራ 17:2, 3) አንተም እንደዚህ ማድረግ ትችላለህ። የንግግርህ መሠረት የመጽሐፍ ቅዱስ ጥቅሶች መሆን አለባቸው። በንግግር አስተዋጽኦው ላይ ያሉትን ዓረፍተ ነገሮች እያብራራህ በማስረዳት ብቻ መወሰን የለብህም። ከዚህ ይልቅ ጥቅሶቹ ዓረፍተ ነገሮቹን የሚደግፉት እንዴት እንደሆነ በማስተዋል እነዚህን ጥቅሶች መሠረት አድርገህ አስተምር።
ንግግርህን በምትዘጋጅበት ጊዜ እያንዳንዱን ጥቅስ አውጥተህ አንብብ። በዙሪያው ያለውን ሐሳብ ተመልከት። አንዳንዶቹ ጥቅሶች ከጉዳዩ በስተጀርባ ያለውን ሁኔታ ግልጽ ለማድረግ የገቡ ሊሆኑ ይችላሉ። በንግግርህ ወቅት የግድ ሁሉንም ጥቅስ እያነበብህ ሐሳብ ልትሰጥበት ይገባል ማለት አይደለም። ለአድማጮችህ ይበልጥ ይስማማሉ የምትላቸውን ጥቅሶች ምረጥ። በንግግሩ አስተዋጽኦ ላይ ባሉት ጥቅሶች ላይ ካተኮርህ ተጨማሪ ጥቅሶችን መጠቀም ላያስፈልግህ ይችላል።
ንግግርህ አድማጮችህን የሚጠቅም መሆኑ የተመካው በምታነብባቸው ጥቅሶች ብዛት ሳይሆን በትምህርቱ የአቀራረብ ጥራት ላይ ነው። ጥቅሶችን በምታስተዋውቅበት ጊዜ የተጠቀሱበትን ምክንያት ግልጽ አድርግ። ጥቅሶቹን ከነጥቡ ጋር ጥሩ አድርገህ ማዛመድ ይኖርብሃል። አንድ ጥቅስ ካነበብህ በኋላ ስለ ጥቅሱ ስታብራራ መጽሐፍ ቅዱስህን አትክደነው። አድማጮችህም እንደ አንተ መጽሐፍ ቅዱሳቸውን ገልጠው እንደሚቆዩ የታወቀ ነው። አድማጮችህ በትኩረት እንዲከታተሉህና ከአምላክ ቃል ይበልጥ ተጠቃሚ እንዲሆኑ መርዳት የምትችለው እንዴት ነው? (ነህ. 8:8, 12) በማብራራት፣ ምሳሌ በመጠቀምና እንዴት ተግባራዊ እንደሚሆን በማስረዳት ይህንን ማድረግ ትችላለህ።
ማብራራት። አንድን ቁልፍ የሆነ ጥቅስ ለማብራራት ስትወስን ራስህን እንዲህ እያልክ ጠይቅ:- ‘ይህ ምን ማለት ነው? በንግግሬ ውስጥ የምጠቅሰው ለምንድን ነው? አድማጮች ስለ ራሳቸው ምን ብለው እንዲያስቡ ያደርጋቸዋል?’ በጥቅሱ ዙሪያ ያለውን ሐሳብ፣ ከጥቅሱ በስተጀርባ ያለውን ሁኔታ፣ መቼቱን፣ ቃላቱ ያላቸውን ኃይል እንዲሁም ጸሐፊው በመንፈስ አነሳሽነት መልእክቱን ሲጽፍ ዓላማው ምን እንደነበረ ማጤን ያስፈልግህ ይሆናል። ይህ ደግሞ ምርምር ማድረግ ይጠይቃል። “ታማኝና ልባም ባሪያ” ባዘጋጃቸው ጽሑፎች ውስጥ ብዙ ጠቃሚ መረጃዎች ታገኛለህ። (ማቴ. 24:45-47) ስለ ጥቅሱ ሁሉንም ነገር ለማብራራት አትሞክር። ከዚህ ይልቅ ከትምህርቱ ጋር በተያያዘ አድማጮች ጥቅሱን እንዲያነብቡ ያደረግኸው ለምን እንደሆነ አብራራ።
በምሳሌ መጠቀም። በምሳሌ ማስረዳት አድማጮች ነጥቡን ይበልጥ በጥልቀት እንዲያስተውሉ እንዲሁም አንድን ነጥብ ወይም መሠረታዊ ሥርዓት እንዲያስታውሱ ይረዳል። ምሳሌ መጠቀም አድማጮችህ እየተናገርህ ያለኸውን ነገር አስተውለው ከአሁን ቀደም ከሚያውቁት ጉዳይ ጋር እንዲያዛምዱ ይረዳቸዋል። ኢየሱስ በዝነኛው የተራራ ስብከቱ ወቅት ያደረገው ይህንኑ ነበር። “የሰማይ ወፎች፣” “የሜዳ አበቦች፣” ‘የጠበበ ደጅ፣’ ‘በዓለት ላይ የተመሠረተ ቤት’ የሚሉትና እነዚህን የመሰሉት ብዙ ምሳሌዎቹ ትምህርቱን ትኩረት የሚስብ፣ ግልጽና የማይረሳ እንዲሆን አድርገውታል።—ማቴ. ምዕ. 5–7
እንዴት ተግባራዊ እንደሚሆን ማስረዳት። አንድን ጥቅስ ስታብራራና በምሳሌ ስታስረዳ አድማጮችህ እውቀት ያገኛሉ። ይሁን እንጂ ይበልጥ ውጤት የሚኖረው ያንን እውቀት እንዴት ተግባራዊ ማድረግ እንደሚችሉ ማስረዳቱ ነው። እርግጥ የመጽሐፍ ቅዱሱን መልእክት ሰምቶ እርምጃ መውሰድ የእያንዳንዱ አድማጭ ኃላፊነት እንደሆነ አይካድም። ይሁንና ምን ማድረግ እንደሚገባቸው እንዲያስተውሉ ልትረዳቸው ትችላለህ። ጥቅሱ ለአድማጮችህ ግልጽ ከሆነላቸውና ከነጥቡ ጋር ያለው ዝምድና ከገባቸው በኋላ በእምነታቸውና በአኗኗራቸው ላይ ምን በጎ ተጽዕኖ እንደሚኖረው እንዲያስተውሉ አድርግ። እየተብራራ ካለው የመጽሐፍ ቅዱስ እውነት ጋር የማይጣጣሙ አስተሳሰቦችን ወይም ድርጊቶችን መተው ምን ጥቅም እንዳለው ጎላ አድርገህ ግለጽ።
ጥቅሱ እንዴት ተግባራዊ እንደሚሆን ለማስረዳት ስታስብ አድማጮችህ የተለያየ ሁኔታ ያላቸው ሰዎች መሆናቸውን መዘንጋት የለብህም። ምናልባት ፍላጎት ያሳዩ አዲሶች፣ ወጣቶች፣ አረጋውያን እና ከተለያዩ ችግሮች ጋር የሚታገሉ ሰዎች ይኖሩ ይሆናል። ንግግርህ አድማጮች በሕይወታቸው ሊጠቀሙበት የሚችሉ እንዲሆን አድርግ። የተወሰኑ ሰዎችን በአእምሮህ ይዘህ እንደምትናገር የሚያስመስል ምክር ከመስጠት ተቆጠብ።
ለተናጋሪው የተተዉ ውሳኔዎች
ንግግርህን በተመለከተ አንዳንዶቹ ነገሮች አስቀድመው ተወስነዋል። ዋና ዋናዎቹ ነጥቦች በግልጽ ተቀምጠዋል እንዲሁም እያንዳንዱን ንዑስ ርዕስ ለማብራራት የሚያስፈልገው ጊዜ ተመድቧል። ሌሎቹ ግን ለአንተ የተተዉ ናቸው። አንዳንዶቹን ንዑሳን ነጥቦች ለማብራራት ከሌሎቹ ይልቅ ሰፋ ያለ ጊዜ ትፈልግ ይሆናል። ሁሉንም ንዑስ ነጥብ በእኩል መጠን መሸፈን አለብኝ ብለህ አታስብ። ይህ ትምህርቱን ለመሸፈን ስትል እንድትሯሯጥና አድማጮችህ ሊይዙት ከሚችሉት በላይ ብዙ ሐሳብ እንድትጭንባቸው ሊያደርግ ይችላል። የትኛውን ነጥብ በጥልቀት አብራርተህ የትኛውን ነጥብ በአጭሩ እንደምትጠቅስ ወይም እግረ መንገድህን ጠቆም አድርገህ ብቻ እንደምታልፍ ለመወሰን የሚረዳህ ምንድን ነው? ራስህን እንዲህ እያልክ ጠይቅ:- ‘የንግግሩን ዋና መልእክት ለማስተላለፍ የሚረዱኝ ነጥቦች የትኞቹ ናቸው? አድማጮቼን ይበልጥ ሊጠቅሙ የሚችሉትስ የትኞቹ ናቸው? አንድን ጥቅስና ከዚያ ጋር ዝምድና ያለውን ሐሳብ ባስቀር የማቀርበውን ማስረጃ ያዳክምብኛልን?’
ግምታዊ ሐሳብ ወይም የግል አመለካከት ላለመጨመር ጥንቃቄ አድርግ። የአምላክ ልጅ የሆነው ኢየሱስ ክርስቶስ እንኳ ‘ከራሱ አንዳች አልተናገረም።’ (ዮሐ. 14:10) ሰዎች በይሖዋ ምሥክሮች ስብሰባዎች ላይ የሚገኙት መጽሐፍ ቅዱስ ሲብራራ ለማዳመጥ እንደሆነ አስታውስ። ጥሩ ተናጋሪ ነው የሚል ስም አትርፈህ ከሆነ እንዲህ ያለ ስም ልታተርፍ የቻልከው የሰዎችን ትኩረት ወደ ራስህ ስለሳብክ ሳይሆን አድማጮችህ በአምላክ ቃል ላይ እንዲያተኩሩ ስላደረግህ እንደሆነ እሙን ነው። እንደዚያ ከሆነ ሰዎች የምትሰጠውን ንግግር ያደንቃሉ።—ፊልጵ. 1:10, 11
መሠረታዊ ነጥቦችን ብቻ የያዘውን አስተዋጽኦ በማዳበር ጥቅሶችን በጥልቀት የሚያብራራ ሕያው ንግግር አድርገኸዋል። አሁን ንግግርህን መለማመድ ያስፈልግሃል። ድምፅህን እያሰማህ ብትለማመድ ጥሩ ነው። የልምምዱ ዋና ዓላማ ሁሉም ነጥቦች በአእምሮህ ውስጥ እንዲቀረጹ ማድረግ ነው። በንግግሩ ተመስጠህ፣ ሕያው አድርገህና ግለት ባለው መንገድ ልታቀርብ ይገባል። ንግግርህን ከማቅረብህ በፊት ራስህን እንዲህ እያልክ ጠይቅ:- ‘ይህን ንግግር ሳቀርብ ዓላማዬ ምንድን ነው? ዋና ዋና ነጥቦቹ ግልጽ ሆነው ተቀምጠዋልን? ንግግሬ በጥቅሶች ላይ የተመሠረተ ነውን? እያንዳንዱ ዋና ነጥብ ከሚቀጥለው ሐሳብ ጋር በቀላሉ ይያያዛልን? ንግግሩ አድማጮች ለይሖዋና ለዝግጅቶቹ አድናቆት እንዲያድርባቸው የሚያደርግ ነውን? መደምደሚያው በቀጥታ ከጭብጡ ጋር የሚዛመድና አድማጮች ምን ማድረግ እንዳለባቸው የሚጠቁም እንዲሁም ለሥራ የሚያነሳሳ ነውን?’ ለእነዚህ ጥያቄዎች የምትሰጠው መልስ አዎንታዊ ከሆነ ጉባኤውን በሚጠቅምና ለይሖዋ ውዳሴ በሚያመጣ መንገድ ‘እውቀትን አሳምረህ ለማቅረብ’ ዝግጁ ነህ ማለት ነው!—ምሳሌ 15:2
-