የመጠበቂያ ግንብ የኢንተርኔት ቤተ መጻሕፍት
መጠበቂያ ግንብ
የኢንተርኔት ቤተ መጻሕፍት
አማርኛ
፦
  • ፡
  • መጽሐፍ ቅዱስ
  • የሕትመት ውጤቶች
  • ስብሰባዎች
  • የመጽሐፍ ቅዱስን መመሪያዎች መከተል ያለብኝ ለምንድን ነው?
    ወጣቶች የሚጠይቋቸው ጥያቄዎችና ተግባራዊ መሆን የሚችሉ መልሶች፣ ጥራዝ 2
    • ምዕራፍ 34

      የመጽሐፍ ቅዱስን መመሪያዎች መከተል ያለብኝ ለምንድን ነው?

      ከሁለት ልጆች ጋር በትምህርት ቤታችሁ ካፊቴሪያ ውስጥ ምሳችሁን እየበላችሁ እያለ በቅርቡ ወደ ትምህርት ቤታችሁ የመጣው ወጣት ወደ ካፊቴሪያው ሲገባ አያችሁት።

      በዚህ ጊዜ አንደኛዋ ልጅ “ዮናስ በጣም ወዶሻል፤ አስተያየቱ ራሱ ያስታውቃል” አለችሽ። “ዓይኑን እኮ ከአንቺ ላይ መንቀል አልቻለም!”

      ሌላኛዋም ወደ አንቺ ጠጋ ብላ “ደስ የሚለው ደግሞ አልተያዘም!” በማለት ሹክ ትልሻለች።

      ለነገሩ አንቺም ይሄን ታውቂያለሽ። ዮናስ ራሱ ቤቱ ባዘጋጀው ፓርቲ ላይ እንድትገኚ ባለፈው ጋብዞሽ ነበር። በእርግጥ ግብዣውን አልተቀበልሽም፤ በውስጥሽ ግን ‘ፓርቲው ምን ይመስል ይሆን?’ ብለሽ ማሰብሽ አልቀረም።

      ይህን እያውጠነጠንሽ እያለ የመጀመሪያዋ ልጅ:-

      “ወይኔ! ጓደኛ ባይኖረኝ ኖሮ ዮናስ አያመልጠኝም ነበር!” አለች።

      ከዚያም ግራ በመጋባት ስሜት ታይሽ ጀመር። ምን ልትልሽ እንደሆነ ገብቶሻል።

      “ቆይ አንቺ የወንድ ጓደኛ የማትይዥው ለምንድን ነው?”

      የፈራሽው ይህ ጥያቄ እንዳይነሳ ነበር! እውነቱን ለመናገር አንቺም የወንድ ጓደኛ ቢኖርሽ ደስ ይልሻል። ይሁንና ለማግባት ዝግጁ ሳይሆኑ የወንድ ጓደኛ መያዝ ተገቢ እንዳልሆነ ተነግሮሻል። ‘የመጽሐፍ ቅዱስን መመሪያ መከተል ባይኖርብኝ ኖሮ ግን . . .’ ብለሽ እያሰብሽ እያለ

      ሁለተኛዋ ልጅ “በሃይማኖትሽ ምክንያት ነው አይደል?” ብላ ጠየቀችሽ።

      ‘የማስበውን እንዴት አወቀች?’ ብለሽ በልብሽ አሰብሽ።

      ከዚያም የመጀመሪያዋ ልጅ “አንቺ ደግሞ ነጋ ጠባ መጽሐፍ ቅዱስ፣ መጽሐፍ ቅዱስ ትያለሽ። ምናለበት አንዳንዴ እንኳ ዘና ብትዪ?” በማለት አሾፈችብሽ።

      አንተስ የመጽሐፍ ቅዱስን መመሪያዎች ለመከተል ጥረት በማድረግህ ጓደኞችህ አሹፈውብህ ያውቃሉ? ከሆነ የቀረብህ ነገር እንዳለ ይሰማህ ይሆናል። ዲቦራ የተባለች አንዲት ወጣት እንዲህ ተሰምቷት ነበር። “የመጽሐፍ ቅዱስ መመሪያዎች የማያፈናፍኑ እንደሆኑ አስብ ነበር። የትምህርት ቤት ጓደኞቼ እንደ ልባቸው ስለሚሆኑ በእነሱ እቀና ነበር” ብላለች።

      እውነታውን ገምግም

      ሞክሮ ማየትን የመሰለ ነገር እንደሌለ ሲገለጽ የምንሰማ ቢሆንም እንዲህ ዓይነቱ አካሄድ የማያዋጣበት ጊዜ አለ። መዝሙራዊው አሳፍ እንዳደረገው ከሌሎች ስህተት መማር የጥበብ እርምጃ ከመሆኑም ሌላ ቅዱስ ጽሑፋዊ ድጋፍ ያለው አካሄድ ነው። በአንድ ወቅት አሳፍ የአምላክ መመሪያዎች በጣም ጥብቅ እንደሆኑ ተሰምቶት ነበር። ሆኖም የአምላክን ጎዳና የተዉ ሰዎችን ሕይወት መገምገሙ እውነታውን እንዲረዳ አስችሎታል። አሳፍ፣ እነዚህ ሰዎች “በሚያዳልጥ ስፍራ” ላይ ያሉ ያህል መሆኑን ከጊዜ በኋላ ተገንዝቧል።​—መዝሙር 73:18

      አንተም ከሌሎች ስህተት መማር እንድትችል በአንድ ወቅት የመጽሐፍ ቅዱስን መመሪያዎች ችላ ብለው ከጋብቻ በፊት የፆታ ግንኙነት የፈጸሙ አንዳንድ ወጣቶች የሰጡትን ሐሳብ እስቲ ተመልከት።

      ● በአስተሳሰባችሁና በድርጊታችሁ ላይ ተጽዕኖ ያሳደረው ምንድን ነው?

      ዲቦራ፦ “ትምህርት ቤት ሳለሁ ሁሉም ልጆች የፍቅር ጓደኛ ነበራቸው፤ በዚያ ላይ ደግሞ ሲታዩ ደስተኛ ይመስሉ ነበር። ከእነሱ ጋር በምሆንበት ጊዜ ሲሳሳሙና ሲተቃቀፉ እመለከት ነበር፤ ይህ ደግሞ የቅናት ስሜት የፈጠረብኝ ከመሆኑም ሌላ ብቻዬን እንደቀረሁ እንዲሰማኝ አድርጎኛል። ብዙውን ጊዜ ስለወደድኩት ልጅ ቁጭ ብዬ በማሰብ ረጅም ሰዓት አሳልፍ ነበር። ይህ ደግሞ ከእሱ ጋር ለመሆን ያለኝ ፍላጎት እያየለ እንዲሄድ አደረገ።”

      ማይክ፦ “የማነባቸው ጽሑፎችና የምከታተላቸው የቴሌቪዥን ፕሮግራሞች የፆታ ስሜትን የሚያነሳሱ ነበሩ። ከጓደኞቼ ጋር ስለ ፆታ ግንኙነት ማውራቴ ድርጊቱን ለመፈጸም ይበልጥ እንድነሳሳ አደረገኝ። ከአንዲት ልጅ ጋር ብቻችንን በምንሆንበት ጊዜ ‘የፆታ ግንኙነት ባንፈጽምም በመተቃቀፍ ወይም በሌላ መልኩ ፍቅራችንን መግለጽ እንችላለን’ ብዬ አስብ ነበር፤ የፆታ ግንኙነት የምፈጽምበት ደረጃ ላይ ሳልደርስ ማቆም እንደምችል ይሰማኝ ነበር።”

      አንድሩ፦ “ኢንተርኔት ላይ የብልግና ምስሎችን የመመልከት ልማድ ነበረኝ። ከዚያም የአልኮል መጠጥ በብዛት መጠጣት ጀመርኩ። እንዲሁም ለመጽሐፍ ቅዱስ የሥነ ምግባር መመሪያዎች ደንታ ከሌላቸው ልጆች ጋር ፓርቲዎች ላይ እገኝ ነበር።”

      ትሬሲ፦ “ከጋብቻ በፊት የፆታ ግንኙነት መፈጸም ስህተት መሆኑን ባውቅም ድርጊቱን አልጠላውም ነበር። ከማግባቴ በፊት የፆታ ግንኙነት የመፈጸም ሐሳብ አልነበረኝም፤ ይሁንና ስሜቴ አስተሳሰቤን አዛባው። ለተወሰነ ጊዜ ሕሊናዬ ደንዝዞ ስለነበር ምንም ዓይነት የጥፋተኝነት ስሜት አልተሰማኝም።”

      ● የመረጣችሁት ጎዳና ደስታ አስገኝቶላችኋል?

      ዲቦራ፦ “መጀመሪያ ላይ ነፃነት እንዳገኘሁ ስለተሰማኝ ፈነደቅሁ፤ እንደ እኩዮቼ መሆን በመቻሌ ተደስቼ ነበር። ደስታዬ ግን አልዘለቀም። እንደቆሸሽኩ፣ ንጽሕናዬን እንዳጣሁና ባዶ እንደሆንኩ ተሰማኝ። ርካሽ በሆነ መንገድ ድንግልናዬን በማጣቴ ከፍተኛ የጸጸት ስሜት አደረብኝ።”

      አንድሩ፦ “አንዴ ከገባሁበት በኋላ መጥፎ ድርጊቶችን መፈጸም እየቀለለኝ መጣ። በዚያው መጠን ደግሞ በጥፋተኝነት ስሜት እሠቃይ የነበረ ከመሆኑም ሌላ በራሴ እበሳጭ ነበር።”

      ትሬሲ፦ “የሥነ ምግባር ብልግና በመፈጸሜ የወጣትነት ሕይወቴ ተበላሸ። ከወንድ ጓደኛዬ ጋር ዓለማችንን የምንቀጭ መስሎኝ ነበር፤ ይሁን እንጂ እንዳሰብኩት አልሆነም። የተረፈን ነገር ቢኖር የስሜት ቁስል እንዲሁም ሐዘንና ሥቃይ ብቻ ነው። ‘ምናለ የይሖዋን ምክር በተከተልኩ ኖሮ’ ብዬ ስለምቆጭ ማታ ማታ ሥራዬ ማልቀስ ሆኖ ነበር።”

      ማይክ፦ “ጨርሶ ደስታ ራቀኝ። ያደረግኳቸው ነገሮች በሌሎች ላይ ያሳደሩትን ተጽዕኖ ላለማሰብ ብሞክርም አልተሳካልኝም። ራሴን ለማስደሰት ስል ሌሎችን መጉዳቴ ያንገበግበኛል።”

      ● የመጽሐፍ ቅዱስ የሥነ ምግባር መመሪያዎች የማያፈናፍኑ እንደሆኑ ለሚሰማቸው ወጣቶች ምን ምክር ትሰጣላችሁ?

      ትሬሲ፦ “የይሖዋን መመሪያዎች ተከተሉ፤ እንዲሁም እንደዚያ ከሚያደርጉ ሰዎች ጋር ተቀራረቡ። ይበልጥ ደስተኛ መሆን የምትችሉት እንዲህ ካደረጋችሁ ነው።”

      ዲቦራ፦ “ስለ ራሳችሁና ስለምትፈልጉት ነገር ብቻ አታስቡ። የምታደርጉት ነገር እናንተን ብቻ ሳይሆን ሌሎችንም ይነካል። የአምላክን መመሪያዎች ችላ የምትሉ ከሆነ ራሳችሁን ትጎዳላችሁ።”

      አንድሩ፦ “ተሞክሮ ስለሚጎድላችሁ እኩዮቻችሁ የሚመሩት ሕይወት አስደሳች እንደሆነ ይሰማችኋል። የእኩዮቻችሁ አመለካከት ሊጋባባችሁ ይችላል። በመሆኑም ጓደኞቻችሁን በጥበብ መምረጥ ይኖርባችኋል። በይሖዋ የምትታመኑ ከሆነ ከጸጸት ትድናላችሁ።”

      ማይክ፦ “ይሖዋ ከሰጣችሁ በጣም ውድ የሆኑ ስጦታዎች መካከል ክብራችሁና ንጽሕናችሁ ይገኙበታል። ራሳችሁን መግዛት ባለመቻላችሁ እነዚህን ስጦታዎች አሽቀንጥራችሁ ስትጥሉ ራሳችሁን ታዋርዳላችሁ። በመሆኑም ችግሮች ሲያጋጥሟችሁ ወላጆቻችሁንና ሌሎች የጎለመሱ ሰዎችን አማክሯቸው። ስህተት ከሠራችሁ ጉዳዩን በግልጽ ለመናገርና ሁኔታውን ለማስተካከል ዛሬ ነገ አትበሉ። ነገሮችን ይሖዋ በሚፈልገው መንገድ ካከናወናችሁ እውነተኛ ሰላም ይኖራችኋል።”

      የመጽሐፍ ቅዱስን መመሪያ እንዴት ታየዋለህ?

      ይሖዋ ‘ደስተኛ አምላክ’ ስለሆነ አንተም ደስተኛ እንድትሆን ይፈልጋል። (1 ጢሞቴዎስ 1:11፤ መክብብ 11:9) በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ የሰፈሩትን መመሪያዎች ብትከተል ጥቅሙ ለአንተው ነው። እርግጥ ነው፣ ይህን መመሪያ እንደ ልብህ እንዳትሆን ጠፍሮ እንዳሰረህ ነገር አድርገህ ትመለከተው ይሆናል። እንደ እውነቱ ከሆነ ግን የመጽሐፍ ቅዱስ የሥነ ምግባር መመሪያ ከአደጋ እንደሚጠብቅህ የመኪና ቀበቶ ነው።

      በእርግጥም በመጽሐፍ ቅዱስ ላይ እምነት መጣል ትችላለህ። በውስጡ የሰፈሩትን መመሪያዎች የምትከተል ከሆነ ይሖዋን የምታስደስት ከመሆኑም በላይ ራስህም ትጠቀማለህ።​—ኢሳይያስ 48:17

      በሚቀጥለው ምዕራፍ

      የአምላክ ወዳጅ መሆን ትችላለህ። እንዴት?

      ቁልፍ ጥቅስ

      “እኔ ይሖዋ የሚጠቅምህን ነገር የማስተምርህ . . . አምላክህ ነኝ።”​—ኢሳይያስ 48:17 NW

      ጠቃሚ ምክር

      የመጽሐፍ ቅዱስን መመሪያዎች መከተል የጥበብ አካሄድ መሆኑን ለታናናሾችህ እንዴት ማስረዳት እንደምትችል አስብ። ስለምታምንባቸው ነገሮች ለሌሎች መናገርህ ለእነዚህ ነገሮች ያለህ አቋም ጥብቅ እንዲሆን ለማድረግ የሚረዳ ግሩም መንገድ ነው።

      ይህን ታውቅ ነበር?

      ከይሖዋ ጋር ያለህን ወዳጅነት በአንድ ጀንበር ልታበላሸው ትችላለህ፤ ወዳጅነትህን ለማደስ ግን ዓመታት ሊፈጅብህ ይችላል።

      ላደርጋቸው ያሰብኳቸው ነገሮች

      የመጽሐፍ ቅዱስን መመሪያዎች መከተል የጥበብ አካሄድ መሆኑን መገንዘብ እንድችል እንዲህ አደርጋለሁ፦ ․․․․․

      በመጽሐፍ ቅዱስ መሥፈርቶች የማይመሩ ሰዎች ሕይወት ካስቀናኝ እንዲህ አደርጋለሁ፦ ․․․․․

      ከዚህ ርዕሰ ጉዳይ ጋር በተያያዘ ወላጆቼን ልጠይቃቸው የምፈልገው ነገር ․․․․․

      ምን ይመስልሃል?

      ● የአምላክን ሕግጋት መጣስ ምን መዘዝ እንደሚያስከትል በራስ ሕይወት ሞክሮ ማየት የማያዋጣው ለምንድን ነው?

      ● ዲቦራ፣ ማይክ፣ አንድሩና ትሬሲ ከሰጧቸው ሐሳቦች ምን ትምህርት አግኝተሃል?

      ● አንዳንዶች የመጽሐፍ ቅዱስ መመሪያዎችን ጠፍሮ እንደሚያስር ነገር አድርገው የሚመለከቷቸው ለምን ሊሆን ይችላል? እንዲህ ያለው አመለካከት አርቆ ማስተዋል የጎደለው ነው የምንለው ለምንድን ነው?

      [በገጽ 285 ላይ የሚገኝ ሥዕል]

      ለፈጸምከው መጥፎ ድርጊት ከምትቀበለው ተግሣጽ ይልቅ ድርጊቱን ለመደበቅ መሞከር የሚያስከትልብህ ሥቃይ ይብሳል።”​—ዶና

      [በገጽ 288 ላይ የሚገኝ ሥዕል]

      የመጽሐፍ ቅዱስ መመሪያዎች መፈናፈኛ የሚያሳጡህ አይደሉም፤ ከዚህ ይልቅ ጥበቃ ያደርጉልሃል

  • የአምላክ ወዳጅ መሆን የምችለው እንዴት ነው?
    ወጣቶች የሚጠይቋቸው ጥያቄዎችና ተግባራዊ መሆን የሚችሉ መልሶች፣ ጥራዝ 2
    • ምዕራፍ 35

      የአምላክ ወዳጅ መሆን የምችለው እንዴት ነው?

      ጄረሚ ከአምላክ ጋር ወዳጅነት መመሥረት ያለውን ጥቅም የተረዳው በሕይወቱ ውስጥ ካጋጠመው አሳዛኝ ሁኔታ ነበር። እንዲህ ብሏል፦ “የ12 ዓመት ልጅ ሳለሁ አባቴ ቤተሰቡን ጥሎ ሄደ። አንድ ምሽት አልጋዬ ላይ ሆኜ አባቴ የሚመለስበትን መንገድ እንዲያመቻች ይሖዋን በጸሎት ለመንኩት።”

      ከዚያም ጄረሚ በጭንቀት ተውጦ መጽሐፍ ቅዱሱን ማንበብ ጀመረ። መዝሙር 10:14 (NW) ላይ ያለው ሐሳብ ልቡን ነካው። ጥቅሱ ስለ ይሖዋ ሲናገር “አባት የሌለው ልጅ ራሱን ለአንተ በአደራ ይሰጣል። አንተ ራስህ ረዳቱ ሆነሃል” ይላል። ጄረሚ እንዲህ ብሏል፦ “ይሖዋ እያነጋገረኝ እንደሆነ እንዲሁም ረዳቴና አባቴ መሆኑን እየነገረኝ እንዳለ ሆኖ ተሰማኝ። ከእሱ የተሻለ አባት የት ላገኝ እችላለሁ?”

      አንተም ከጄረሚ ጋር የሚመሳሰል ሁኔታ አጋጥሞህ ሊሆን ይችላል፤ ይህ ባይሆንም እንኳ ይሖዋ የእሱ ወዳጅ እንድትሆን የሚፈልግ መሆኑን መጽሐፍ ቅዱስ ይናገራል። እንዲያውም መጽሐፍ ቅዱስ “ወደ አምላክ ቅረቡ፤ እሱም ወደ እናንተ ይቀርባል” ይላል። (ያዕቆብ 4:8) ይህ አባባል ምን ትርጉም እንዳለው አስተዋልክ? ይሖዋ አምላክን ልታየው ባትችልም እንዲሁም በምንም መልኩ እኩያህ ባይሆንም እንኳ ከእሱ ጋር ወዳጅነት እንድትመሠርት እየጋበዘህ ነው!

      ይሁንና ከአምላክ ጋር ወዳጅነት መመሥረት በአንተ በኩል ጥረት ማድረግ ይጠይቅብሃል። ነገሩን በምሳሌ ለማስረዳት፦ በቤትህ ውስጥ የተከልከው አበባ ቢኖር እንዲያድግ የግድ የአንተ እንክብካቤ እንደሚያስፈልገው የታወቀ ነው። አበባው እንዲመቸው ከተፈለገ በየጊዜው ውኃ ልታጠጣውና ለእድገቱ ተስማሚ በሆነ ስፍራ ልታስቀምጠው ይገባል። ከአምላክ ጋር ወዳጅነት በመመሥረት ረገድም ሁኔታው ተመሳሳይ ነው። ታዲያ ከአምላክ ጋር ያለህ ወዳጅነት እያደገ ወይም እየተጠናከረ እንዲሄድ ምን ማድረግ ትችላለህ?

      ጥናት አስፈላጊ ነው

      ወዳጅነት እንዲጠናከር ሁለቱም ወገኖች የሐሳብ ልውውጥ ማድረግ ይኸውም መነጋገርና መደማመጥ ያስፈልጋቸዋል። ከአምላክ ጋር ባለን ወዳጅነት ረገድም ይህ እውነት ነው። አምላክ የሚነግረንን መስማት የምንችለው መጽሐፍ ቅዱስን በማንበብና በማጥናት ነው።​—መዝሙር 1:2, 3

      በእርግጥ ጥናት የምትወደው ነገር ላይሆን ይችላል። ብዙ ወጣቶች ከማጥናት ይልቅ ቴሌቪዥን ማየት፣ ጌም መጫወት ወይም ከጓደኞቻቸው ጋር ጊዜ ማሳለፍ ይመርጣሉ። ይሁንና ከአምላክ ጋር ወዳጅ ለመሆን ሌላ አቋራጭ መንገድ የለም። ቃሉን በማጥናት እሱን ማዳመጥ ይኖርብሃል።

      በዚህ ረገድ ሐሳብ አይግባህ። መጽሐፍ ቅዱስን ማጥናት ሥራ ሊሆንብህ አይገባም። ማጥናት የምትወድ ሰው ባትሆንም እንኳ መጽሐፍ ቅዱስን ማጥናት አስደሳች እንዲሆንልህ ማድረግ ትችላለህ። ልትወስደው የሚገባው የመጀመሪያው እርምጃ መጽሐፍ ቅዱስን የምታጠናበት ጊዜ መመደብ ነው። ልያ የተባለች ወጣት “መጽሐፍ ቅዱስን የማነብበት ፕሮግራም አለኝ፤ ሁልጊዜ ጠዋት ከእንቅልፌ እንደተነሳሁ አንድ ምዕራፍ አነባለሁ” ብላለች። ማሪያ የተባለችው የ15 ዓመት ወጣት ፕሮግራም ደግሞ ከዚህ የተለየ ነው። “ሁሌ ማታ ማታ ከመተኛቴ በፊት መጽሐፍ ቅዱስን አነባለሁ” ብላለች።

      አንተም እንዴት ማጥናት እንደምትችል ሐሳብ ለማግኘት በገጽ 292 ላይ የሚገኘውን ሣጥን ተመልከት። ከዚያም የአምላክን ቃል ለ30 ደቂቃ ያህል ማጥናት የምትችለው መቼ እንደሆነ አስብ፤ ያወጣኸውን ፕሮግራም ከዚህ በታች ጻፍ።

      ․․․․․

      ፕሮግራም ማውጣት የመጀመሪያው እርምጃ ብቻ ነው። ማጥናት ስትጀምር መጽሐፍ ቅዱስን ማንበብ ቀላል የማይሆንበት ጊዜ እንደሚኖር ትገነዘብ ይሆናል። አንተም ጄዝሬል እንደተባለው የ11 ዓመት ልጅ ይሰማህ ይሆናል፤ “አንዳንዶቹ የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍሎች ለመረዳት ያስቸግራሉ፤ ደግሞም ያን ያህል አይማርኩኝም” በማለት በግልጽ ተናግሯል። እንደዚህ የሚሰማህ ከሆነ ተስፋ አትቁረጥ። ምንጊዜም ቢሆን፣ የመጽሐፍ ቅዱስ ጥናትህን ወዳጅህ የሆነውን ይሖዋ አምላክን ለመስማት የሚያስችል አጋጣሚ እንደሚከፍትልህ አድርገህ ልትመለከተው ይገባል። የመጽሐፍ ቅዱስ ጥናትህ አስደሳችና የሚክስ መሆኑ በምታደርገው ጥረት ላይ የተመካ ነው!

      ጸሎት ወሳኝ ነው

      ጸሎት አምላክን የምናነጋግርበት መንገድ ነው። ጸሎት እንዴት ያለ ግሩም ስጦታ እንደሆነ አስብ! ቀንም ሆነ ማታ በማንኛውም ሰዓት ይሖዋ አምላክን ማነጋገር ትችላለህ። አንተን ለማዳመጥ ምንጊዜም ዝግጁ ነው። ከዚህም በላይ የምትለውን ለመስማት ፍላጎቱ አለው። መጽሐፍ ቅዱስ “ስለ ሁሉም ነገር በጸሎትና በምልጃ ከምስጋና ጋር ልመናችሁን ለአምላክ አቅርቡ” በማለት የሚያሳስበን ለዚህ ነው።​—ፊልጵስዩስ 4:6

      ከዚህ ጥቅስ መረዳት እንደሚቻለው ይሖዋን ስለ ብዙ ነገሮች ልታነጋግረው ትችላለህ። ለምሳሌ ስለሚያጋጥሙህ ችግሮችና ስለሚያስጨንቁህ ነገሮች ልትነግረው ትችላለህ። በተጨማሪም ምስጋናህን ልትገልጽለት ትችላለህ። ስላደረጉልህ መልካም ነገሮች ጓደኞችህን አታመሰግናቸውም? ማንኛውም ጓደኛ ሊያደርግልህ ከሚችለው በላይ ብዙ ነገሮችን ላደረገልህ ለይሖዋስ ምስጋናህን ልትገልጽ አይገባም?​—መዝሙር 106:1

      አንተ በግልህ ይሖዋን እንድታመሰግን የሚያነሳሱህን አንዳንድ ነገሮች ከዚህ በታች ጻፍ።

      ․․․․․

      የሚያስጨንቁህና ስጋት እንዲያድርብህ የሚያደርጉ ነገሮች አልፎ አልፎ እንደሚያጋጥሙህ እሙን ነው። መዝሙር 55:22 “የከበደህን ነገር በእግዚአብሔር ላይ ጣል፤ እርሱ ደግፎ ይይዝሃል፤ የጻድቁንም መናወጥ ከቶ አይፈቅድም” ይላል።

      የሚያሳስቡህንና በጸሎት ወደ ይሖዋ ልታቀርባቸው የምትፈልጋቸውን ጉዳዮች ቀጥሎ ባለው ክፍት ቦታ ላይ ጻፍ።

      ․․․․․

      የራስ ተሞክሮ

      ከአምላክ ጋር ባለህ ወዳጅነት ረገድ ልትዘነጋው የማይገባ ሌላም ነገር አለ። መዝሙራዊው ዳዊት “እግዚአብሔር ቸር መሆኑን ቀምሳችሁ እዩ” በማለት ጽፏል። (መዝሙር 34:8) ዳዊት 34ኛውን መዝሙር ከማቀናበሩ ትንሽ ቀደም ብሎ በጣም አስፈሪ ሁኔታ አጋጥሞት ነበር። በወቅቱ ሊገድለው ከሚፈልገው ከንጉሥ ሳኦል እየሸሸ ነበር፤ ይህ በራሱ በጣም አስጨናቂ ነገር ሆኖ ሳለ ዳዊት ጠላቶቹ ወደሆኑት ፍልስጥኤማውያን በመሄድ መሸሸግ ግድ ሆኖበት ነበር። ዳዊት ከሞት ጋር በተፋጠጠበት በዚያ ወቅት እንዳበደ ሰው በመሆን በዘዴ ማምለጥ ችሏል።​—1 ሳሙኤል 21:10-15

      ዳዊት ከሞት ለጥቂት ሊያመልጥ የቻለው በራሱ ብልሃት እንደሆነ አልተሰማውም። ከዚህ ይልቅ ይሖዋ እንደረዳው ገልጿል። ከላይ በተጠቀሰው መዝሙር ላይ እንዲህ ሲል ጽፏል፦ “እግዚአብሔርን ፈለግሁት፤ እርሱም መለሰልኝ፤ ከፍርሀቴም ሁሉ አዳነኝ።” (መዝሙር 34:4) ከዚህ ለማየት እንደምንችለው ዳዊት “እግዚአብሔር ቸር መሆኑን ቀምሳችሁ እዩ” ብሎ ሌሎችን የመከረው ከራሱ ተሞክሮ በመነሳት ነበር።a

      ይሖዋ እንደሚያስብልህ የሚያሳይ በሕይወትህ ውስጥ ያጋጠመህ አንድ ተሞክሮ ማስታወስ ትችላለህ? ከሆነ ከዚህ በታች ጻፈው። ፍንጭ፦ ተአምር የሆነ ነገር እንዲያጋጥምህ መጠበቅ የለብህም። በዕለት ተዕለት ሕይወትህ ይሖዋ ያደረገልህን ጥቃቅን የሚመስሉ ነገሮች ለማሰብ ጥረት አድርግ፤ ምናልባትም አንዳንዶቹ እምብዛም ትኩረት የማንሰጣቸው ነገሮች ሊሆኑ ይችላሉ።

      ․․․․․

      ወላጆችህ ስለ መጽሐፍ ቅዱስ አስተምረውህ ሊሆን ይችላል። ከሆነ ተባርከሃል። ያም ሆኖ ከአምላክ ጋር የግል ዝምድና መመሥረት ያስፈልግሃል። ከአምላክ ጋር የግል ዝምድና ካልመሠረትክ በዚህ ምዕራፍ ላይ በቀረበው ሐሳብ በመጠቀም እንዲህ ማድረግ ትችላለህ። ይሖዋ የምታደርገውን ጥረት ይባርክልሃል። መጽሐፍ ቅዱስ “ደጋግማችሁ ለምኑ፣ ይሰጣችኋል፤ ሳታቋርጡ ፈልጉ፣ ታገኛላችሁ” ይላል።​—ማቴዎስ 7:7

      ተጨማሪ ሐሳብ ለማግኘት የዚህን መጽሐፍ ጥራዝ 1 ምዕራፍ 38 እና 39 ተመልከት

      በሚቀጥለው ምዕራፍ

      ስለ አምላክ ለሌሎች መናገር ይከብድሃል? ስለ እምነትህ ለሌሎች ማስረዳት የምትችለው እንዴት እንደሆነ ከሚቀጥለው ምዕራፍ ትምህርት ታገኛለህ።

      [የግርጌ ማስታወሻ]

      a አንዳንድ የመጽሐፍ ቅዱስ ትርጉሞች “ቀምሳችሁ እዩ” የሚለውን ሐረግ “ራሳችሁ ተመልከቱ፣” “ራሳችሁ ድረሱበት” እንዲሁም “ከተሞክሮ ታያላችሁ” በማለት አስቀምጠውታል።​—ኮንቴምፖራሪ ኢንግሊሽ ቨርዥን፣ ቱዴይስ ኢንግሊሽ ቨርዥን እና ዘ ባይብል ኢን ቤዚክ ኢንግሊሽ

      ቁልፍ ጥቅስ

      “በመንፈሳዊ ድሆች መሆናቸውን የሚያውቁ ደስተኞች ናቸው።”​—ማቴዎስ 5:3

      ጠቃሚ ምክር

      በየዕለቱ አራት ገጽ ገደማ ብታነብ በአንድ ዓመት ጊዜ ውስጥ ሙሉውን መጽሐፍ ቅዱስ መጨረስ ትችላለህ።

      ይህን ታውቅ ነበር?

      ይህንን መጽሐፍ ማንበብህና በመጽሐፍ ቅዱስ ላይ ተመሥርቶ የሚሰጠውን ምክር ተግባራዊ እያደረግህ መሆንህ ይሖዋ በግለሰብ ደረጃ ለአንተ ትኩረት እየሰጠህ መሆኑን የሚያሳይ ነው።​—ዮሐንስ 6:44

      ላደርጋቸው ያሰብኳቸው ነገሮች

      ከግል የመጽሐፍ ቅዱስ ጥናቴ የበለጠ ጥቅም ለማግኘት እንዲህ አደርጋለሁ፦ ․․․․․

      አዘውትሮ የመጸለይ ልማድ እንዲኖረኝ እንዲህ አደርጋለሁ፦ ․․․․․

      ከዚህ ርዕሰ ጉዳይ ጋር በተያያዘ ወላጆቼን ልጠይቃቸው የምፈልገው ነገር ․․․․․

      ምን ይመስልሃል?

      ● የግል የመጽሐፍ ቅዱስ ጥናትህ ይበልጥ አስደሳች እንዲሆን ምን ማድረግ ትችላለህ?

      ● ይሖዋ ፍጽምና የጎደላቸው የሰው ልጆች የሚያቀርቡትን ጸሎት ለመስማት የሚፈልገው ለምንድን ነው?

      ● የጸሎትህን ይዘት ማሻሻል የምትችለው እንዴት ነው?

      [በገጽ 291 ላይ የሚገኝ የተቀነጨበ ሐሳብ]

      ትንሽ ልጅ እያለሁ ጸሎቴ ሁልጊዜ ተመሳሳይ ነበር። አሁን ግን በእያንዳንዱ ቀን ስላጋጠሙኝ ጥሩም ሆነ መጥፎ ነገሮች አንስቼ ለመጸለይ እሞክራለሁ። እንዲህ ማድረጌ አሁንም አሁንም ተመሳሳይ ነገር እንዳልጸልይ ረድቶኛል፤ ምክንያቱም አንዱ ቀን ከሌላው የተለየ ነው።”​—ኢቭ

      [በገጽ 292 ላይ የሚገኝ ሣጥን/​ሥዕል]

      መጽሐፍ ቅዱስህን መርምር

      1. ልታነብ የምትፈልገውን አንድ የመጽሐፍ ቅዱስ ታሪክ ምረጥ። የምታነበውን ለመረዳት የሚያስችልህ ጥበብ እንዲሰጥህ ወደ ይሖዋ ጸልይ።

      2. ታሪኩን በትኩረት አንብበው። ተረጋግተህ አንብብ። ታሪኩን በምታነብበት ጊዜ ሁኔታውን በዓይነ ሕሊናህ ሳለው። በቦታው እንዳለህ አድርገህ በማሰብ የሚከናወነውን ነገር ለማየት፣ ባለታሪኮቹ ሲነጋገሩ ለመስማት፣ አካባቢውን ያወደውን መዓዛ ለማሽተት እንዲሁም የቀረበውን ምግብ ለማጣጣም ሞክር። ታሪኩ ሕያው ሆኖ ይታይህ!

      3. ያነበብከውን ነገር ቆም ብለህ አስብበት። ራስህን እንዲህ እያልክ ጠይቅ፦

      ● ይሖዋ ይህን ታሪክ በቃሉ ውስጥ እንዲሰፍር ያደረገው ለምንድን ነው?

      ● በታሪኩ ውስጥ ከተጠቀሱት መካከል ልከተለው የሚገባኝ የማንን ምሳሌ ነው? የማስጠንቀቂያ ምሳሌ የሚሆኑትስ እነማን ናቸው?

      ● ከዚህ ምንባብ ምን ጠቃሚ ትምህርት ማግኘት እችላለሁ?

      ● ይህ ታሪክ ስለ ይሖዋና እሱ ነገሮችን ስለሚያከናውንበት መንገድ ምን ያስተምረኛል?

      4. ወደ ይሖዋ አጠር ያለ ጸሎት አቅርብ። ከመጽሐፍ ቅዱስ ጥናትህ ምን ቁም ነገር እንዳገኘህ እንዲሁም ትምህርቱን በሕይወትህ ውስጥ እንዴት ተግባራዊ ለማድረግ እንዳሰብክ ንገረው። ይሖዋን ለሰጠህ ስጦታ ይኸውም ለቃሉ ለመጽሐፍ ቅዱስ ምንጊዜም አመስግነው!

      [ሥዕል]

      “ሕግህ ለእግሬ መብራት፣ ለመንገዴም ብርሃን ነው።”​—መዝሙር 119:105

      [በገጽ 294 ላይ የሚገኝ ሣጥን/​ሥዕል]

      ቅድሚያ ለሚገባው ቅድሚያ ስጥ

      ለመጸለይና መጽሐፍ ቅዱስን ለማጥናት ጊዜ አጥተሃል? ብዙውን ጊዜ ለእነዚህ ነገሮች ጊዜ ማግኘትህ ወይም አለማግኘትህ የተመካው ‘ለየትኞቹ ነገሮች ቅድሚያ ትሰጣለህ?’ ለሚለው ጥያቄ በምትሰጠው መልስ ላይ ነው።

      ሙከራ፦ አንድ ባልዲ ውስጥ በርከት ያሉ ትላልቅ ድንጋዮች ጨምር። ከዚያም ባልዲው የቻለውን ያህል አሸዋ ሙላው። አሁን ባልዲው በድንጋይ እና በአሸዋ ተሞልቷል።

      ቀጥለህ ደግሞ ባልዲውን በመገልበጥ አሸዋውንና ድንጋዩን ለየብቻ አስቀምጠው። አሁን ከበፊቱ በተቃራኒ መጀመሪያ አሸዋውን ባልዲው ውስጥ ጨምረው፤ ከዚያም ድንጋዮቹን ክተት። ሁሉንም ድንጋዮች ለመጨመር ቦታ አነሰህ አይደል? ይህ የሆነው ባልዲው ውስጥ መጀመሪያ አሸዋውን በመጨመርህ ነው።

      ከዚህ የምናገኘው ትምህርት ምንድን ነው? መጽሐፍ ቅዱስ “ይበልጥ አስፈላጊ የሆኑትን ነገሮች ለይታችሁ [እወቁ]” ይላል። (ፊልጵስዩስ 1:10) እንደ መዝናኛ ላሉት ትናንሽ ነገሮች ቅድሚያ ከሰጠህ ትልልቅ ለሆኑት ነገሮች ይኸውም ለመንፈሳዊ ጉዳዮች በቂ ጊዜ አይኖርህም። በሌላ በኩል ግን የመጽሐፍ ቅዱስን ምክር ተግባራዊ ካደረግህ ከመንግሥቱ ጋር ለተያያዙ ጉዳዮችም ሆነ በተወሰነ መጠን ለመዝናናት ጊዜ ይኖርሃል። ጊዜ ማግኘትህ የተመካው ባልዲው ውስጥ መጀመሪያ በምትጨምረው ይኸውም በሕይወትህ ውስጥ ቅድሚያ በምትሰጠው ነገር ላይ ነው!

      [በገጽ 290 ላይ የሚገኝ ሥዕል]

      አንድ አበባ ለማደግ እንክብካቤ እንደሚያስፈልገው ሁሉ ከአምላክ ጋር የመሠረትከው ወዳጅነትም እንዲጠናከር ጥረት ማድረግ ይኖርብሃል

  • ስለ አምላክ በድፍረት መናገር የምችለው እንዴት ነው?
    ወጣቶች የሚጠይቋቸው ጥያቄዎችና ተግባራዊ መሆን የሚችሉ መልሶች፣ ጥራዝ 2
    • ምዕራፍ 36

      ስለ አምላክ በድፍረት መናገር የምችለው እንዴት ነው?

      ስለ እምነትህ ለክፍልህ ልጆች ከመናገር ወደኋላ የምትለው ለምን ሊሆን ይችላል?

      □ ስለ መጽሐፍ ቅዱስ በደንብ ስለማላውቅ

      □ እንዳይሾፍብኝ ስለምፈራ

      □ ምን ብዬ እንደምጀምር ስለማላውቅ

      ስለ እምነትህ ለመናገር የትኛውን መንገድ ትመርጣለህ?

      □ ከአንድ ልጅ ጋር ለብቻ መወያየት

      □ በክፍሌ ተማሪዎች ፊት መናገር

      □ የጽሑፍ ሪፖርት ሳቀርብ ስለ እምነቴ መግለጽ

      አንተ ውይይቱን ብትጀምር ስለ መጽሐፍ ቅዱስ ለመነጋገር ፈቃደኛ ሊሆን ይችላል ብለህ የምታስበው ልጅ አለ? ካለ ስሙን ጻፍ። ․․․․․

      አብረውህ የሚማሩት ልጆች ስለ ፈጣሪ አንስቶ መወያየት ብዙም አይማርካቸው ይሆናል። ከዚህ ሌላ ስለ ማንኛውም ርዕስ ለምሳሌ ስለ ስፖርት፣ ስለ ፋሽን ወይም ስለ ተቃራኒ ፆታ ቢነሳ የሞቀ ጨዋታ ሊጀመር ይችላል። ስለ አምላክ ማውራት ብትጀምር ግን ያን ያህል አይጥማቸው ይሆናል።

      ይህ የሚሆነው እኩዮችህ በአምላክ ስለማያምኑ አይደለም፤ እንዲያውም ብዙ ወጣቶች በፈጣሪ መኖር ያምናሉ። ይሁንና አንዳንዶች ስለዚህ ርዕስ መወያየት ያሳፍራቸዋል። ‘ብዙም አይመችም’ ብለው ያስቡ ይሆናል።

      አንተስ?

      አብረውህ ለሚማሩት ልጆች ስለ አምላክ መናገር ቢከብድህ ምንም አያስገርምም። በሌሎች ዘንድ ተቀባይነት ማጣት ደስ አይልም፤ መሳቂያ መሆን ደግሞ ከዚህም የባሰ ነው! ስለ እምነትህ ብትናገር እንዲህ ዓይነት ሁኔታ ሊያጋጥምህ ይችላል? አዎን ይችላል። በሌላ በኩል ደግሞ እኩዮችህ ያልጠበቅኸው ምላሽ ሊሰጡህ ይችላሉ። ብዙዎቹ እንደሚከተሉት ላሉ ጥያቄዎች መልስ ማግኘት ይሻሉ፦ የዚህ ዓለም መጨረሻ ምን ይሆን? ዓለማችን በችግር የተሞላው ለምንድን ነው? እኩዮችህ ስለ እነዚህ ጉዳዮች ከትልቅ ሰው ይልቅ በዕድሜ ከሚመጥናቸው ሰው ጋር ቢወያዩ ይመርጣሉ።

      ያም ቢሆን ስለ ሃይማኖት ከእኩዮችህ ጋር መነጋገር ዳገት ሊሆንብህ ይችላል። ምናልባትም የክፍልህ ልጆች አክራሪ እንደሆንክ አድርገው እንዳያዩህ ትፈራ ይሆናል፤ አሊያም ደግሞ ‘መናገር ያለብኝን በትክክል ሳልናገር ብቀርስ’ የሚል ስጋት ያድርብህ ይሆናል። ስለ እምነትህ መናገር የሙዚቃ መሣሪያ ከመጫወት ጋር ሊመሳሰል ይችላል። መጀመሪያ ላይ አስቸጋሪ ነው አይደል? ስትለምደው ግን እየቀለለህ የሚሄድ ከመሆኑም በላይ ጥረትህ ጥሩ ውጤት ያስገኝልሃል። ታዲያ ስለ እምነትህ ለመናገር እንዴት መጀመር ትችላለህ?

      ብዙውን ጊዜ በቀላሉ ውይይት መክፈት የምትችልባቸው የተለያዩ ዘዴዎች አሉ። ለምሳሌ ያህል፣ ወቅታዊ በሆነ አንድ ጉዳይ ላይ በትምህርት ቤት ውስጥ ውይይት ቢጀመር አንተም ከመጽሐፍ ቅዱስ አንጻር ሐሳብህን መግለጽ ትችላለህ። ወይም አንድ የክፍልህን ልጅ በግል ልታነጋግረው ትችላለህ። ከዚህም የሚቀል አንድ ዘዴ አለ፦ አንዳንድ ክርስቲያን ወጣቶች እንደሚያደርጉት በመጽሐፍ ቅዱስ ላይ የተመሠረቱ ጽሑፎችን ጠረጴዛህ ላይ በማስቀመጥ ልጆቹ እንዲያዩት ማድረግ ትችላለህ። ብዙውን ጊዜ ጽሑፎቹ የልጆቹን ትኩረት ስለሚስቡ ውይይት መጀመር ቀላል ይሆንልሃል!

      ከላይ ከተጠቀሱት ዘዴዎች መካከል አንተ የትኛውን ለመጠቀም መረጥክ? ․․․․․

      አብሮህ ለሚማር ልጅ ስለ እምነትህ መናገር የምትችልበት ሌላ ዘዴ አለ? ያሰብከውን ከታች ጻፍ።

      ․․․․․

      አንዳንድ ጊዜ በትምህርት ቤት የሚሰጥህ የቤት ሥራ ወይም ፕሮጀክት በራሱ ስለ እምነትህ ለመመሥከር አጋጣሚ ይከፍትልህ ይሆናል። ለምሳሌ ስለ ዝግመተ ለውጥ ቢነሳ ምን ማድረግ ትችላለህ? ሕይወት የተገኘው በፍጥረት እንደሆነ ማስረዳት የምትችለው እንዴት ነው?

      ስለ ፍጥረት ማስረዳት

      ራየን የተባለ ወጣት “በክፍል ውስጥ ስለ ዝግመተ ለውጥ ስንማር የቀረበው ሐሳብ ከዚያ ቀደም የተማርኩትን የሚያፈርስ ነበር። የዝግመተ ለውጥ ጽንሰ ሐሳብ የተረጋገጠ እውነት እንደሆነ ተደርጎ ስለቀረበ ከዚህ የተለየ ሐሳብ ማቅረቡ አስፈራኝ” በማለት ተናግሯል። ራኬብ የተባለች ወጣትም እንደዚህ ተሰምቷት ነበር። እንዲህ ብላለች፦ “የኅብረተሰብ ትምህርት መምህሬ በሚቀጥለው ክፍለ ጊዜ የምንማረው ስለ ዝግመተ ለውጥ መሆኑን ስትናገር በጣም ፈርቼ ነበር። በዚህ አወዛጋቢ ጉዳይ ረገድ አቋሜን በክፍል ውስጥ ማስረዳት እንደሚጠበቅብኝ ታውቆኝ ነበር።”

      አንተስ በክፍል ውስጥ የዝግመተ ለውጥ ርዕስ ሲነሳ ምን ይሰማሃል? አንተ የምታምነው ‘ሁሉንም ነገሮች የፈጠረው’ አምላክ መሆኑን ነው። (ራእይ 4:11) በዙሪያህ የምትመለከታቸው ነገሮች ሁሉ ከፍተኛ የማሰብ ችሎታ ያለው ንድፍ አውጪ እንደሠራቸው የሚያሳዩ ማስረጃዎች ናቸው። ይሁን እንጂ የመማሪያ መጻሕፍቱና አስተማሪህ ሕይወት የተገኘው በዝግመተ ለውጥ ነው ይላሉ። ‘ታዲያ እኔ ማን ሆኜ ነው ከእነዚህ ሁሉ “ምሑራን” ጋር የምሟገተው?’ ብለህ ታስብ ይሆናል።

      አይዞህ፣ በዝግመተ ለውጥ ጽንሰ ሐሳብ የማታምነው አንተ ብቻ አይደለህም። በርካታ የሳይንስ ሊቃውንትም ሳይቀር የዝግመተ ለውጥን ንድፈ ሐሳብ አይቀበሉትም። ብዙ መምህራንና ተማሪዎችም ቢሆኑ በዝግመተ ለውጥ አያምኑም።

      ያም ቢሆን በፈጣሪ እንደምታምን በሚገባ ለማስረዳት መጽሐፍ ቅዱስ ስለዚህ ጉዳይ ምን እንደሚያስተምር ማወቅ ይኖርብሃል። መጽሐፍ ቅዱስ በቀጥታ ሐሳብ በማይሰጥባቸው ጉዳዮች ላይ መከራከር አያስፈልግህም። እስቲ ጥቂት ምሳሌዎችን ተመልከት፦

      የሳይንስ መማሪያ መጽሐፌ መሬትና ሥርዓተ ፀሐይ በቢሊዮን ለሚቆጠሩ ዓመታት እንደኖሩ ይገልጻል። መጽሐፍ ቅዱስ፣ ምድርን ጨምሮ መላው ጽንፈ ዓለም የመጀመሪያው የፍጥረት ቀን ከመጀመሩ በፊት እንደነበረ ይናገራል። በመሆኑም ምድርና ሥርዓተ ፀሐይ በቢሊዮን ዓመታት የሚቆጠር ዕድሜ ሊኖራቸው ይችላል።​—ዘፍጥረት 1:1

      ምድርና በውስጧ ያሉት ነገሮች በስድስት ቀናት ውስጥ ሊፈጠሩ እንደማይችሉ አስተማሪዬ ይናገራል። መጽሐፍ ቅዱስ ስድስቱ የፍጥረት ቀናት፣ ቃል በቃል የ24 ሰዓት ርዝማኔ እንደነበራቸው አይገልጽም።

      በጊዜ ሂደት በእንስሳትና በሰዎች ላይ የታዩ ለውጦች እንዳሉ የሚያሳዩ አንዳንድ ምሳሌዎችን በክፍል ውስጥ ተመልክተናል። አምላክ ሕይወት ያላቸውን ነገሮች “እንደየወገናቸው” እንደፈጠረ መጽሐፍ ቅዱስ ይናገራል። (ዘፍጥረት 1:20, 21) ሕይወት ያለው ነገር ሕይወት ከሌለው ነገር እንደመጣ ወይም አምላክ በአንድ ሴል አማካኝነት የዝግመተ ለውጥን ሂደት እንዳስጀመረ የሚገልጸውን ሐሳብ ግን መጽሐፍ ቅዱስ አይደግፍም። ቢሆንም እያንዳንዱ ‘ወገን’ ወይም ዝርያ ዓይነቱ ብዙ ሊሆን ይችላል። ስለዚህ እያንዳንዱ ፍጥረት ‘ከወገኑ’ ሳይወጣ ለውጥ ሊያካሂድ እንደሚችል መጽሐፍ ቅዱስ አይቃወምም።

      አስተማሪህ ወይም የክፍልህ ልጅ እንደሚከተሉት ያሉ ሐሳቦች ቢያነሱ በዚህ ምዕራፍ ውስጥ ካገኘኸው ትምህርት አንጻር ምን ብለህ ትመልሳለህ?

      “ሕይወት የተገኘው በዝግመተ ለውጥ መሆኑን ሳይንስ አረጋግጧል።” ․․․․․

      “አምላክን ላየው ስለማልችል በእሱ መኖር አላምንም።” ․․․․․

      ስለምታምንበት ነገር እርግጠኛ ሁን!

      ወላጆችህ ክርስቲያኖች ከሆኑ በፍጥረት የምታምነው እነሱ ስላስተማሩህ ብቻ ሊሆን ይችላል። እያደግህ ስትሄድ ግን አምላክን ‘በማሰብ ችሎታህ ተጠቅመህ’ ማምለክ ትፈልጋለህ፤ በሌላ አባባል ለምታምንባቸው ነገሮች ጽኑ መሠረት ሊኖርህ ይገባል። (ሮም 12:1) እንግዲያው ‘እኔ በግሌ ፈጣሪ መኖሩን የሚያሳምነኝ ምንድን ነው?’ ብለህ ራስህን ጠይቅ። ይህን ጥያቄ ለመመለስ የ14 ዓመቱ ሳም የሰውን አካል በምሳሌነት ይጠቅሳል። እንዲህ ብሏል፦ “እያንዳንዱ ነገር እጅግ የረቀቀና ውስብስብ ነው። እንዲሁም ሁሉም የአካል ክፍሎች ግሩም በሆነ ሁኔታ ተቀናጅተው ይሠራሉ። የሰው አካል የተገኘው በዝግመተ ለውጥ ሊሆን አይችልም!” ሆሊ የተባለችው የ16 ዓመት ወጣትም በዚህ ትስማማለች። እንዲህ ትላለች፦ “የስኳር በሽታ እንዳለብኝ ከተነገረኝ ጊዜ ጀምሮ የሰው አካል እንዴት እንደሚሠራ ብዙ ተምሬያለሁ። ለምሳሌ ቆሽት፣ በጨጓራና በአንጀት መሃል ተወሽቃ የምትገኝ አንዲት ትንሽ የአካል ክፍል ሆና ሳለ ደምና ሌሎች የአካላችን ክፍሎች በትክክል መሥራታቸውን እንዲቀጥሉ በማድረግ ረገድ ምን ያህል ትልቅ ድርሻ እንደምታበረክት መመልከቱ በጣም ያስደንቃል።”

      አንተ በግልህ ፈጣሪ መኖሩን እንድታምን የሚያደርጉህን ሦስት ምክንያቶች ከዚህ በታች ጻፍ።

      1. ․․․․․

      2. ․․․․․

      3. ․․․․․

      በአምላክና በፍጥረት የምታምን በመሆንህ የምትሸማቀቅበት ወይም የምታፍርበት ምንም ምክንያት የለም። ማስረጃዎቹን ሁሉ ስንመረምር ድንቅ የማሰብ ችሎታ ያለው ንድፍ አውጪ እንደሠራን ማመን ፍጹም ምክንያታዊ ሆኖ እናገኘዋለን።

      እንዲያውም ያላንዳች አሳማኝ ማስረጃ በጭፍን እንድናምን የሚጠይቅብን የዝግመተ ለውጥ ጽንሰ ሐሳብ እንጂ በፈጣሪ ማመን አይደለም፤ በዝግመተ ለውጥ ማመን ተአምር ሠሪ ሳይኖር በተፈጸመ ተአምር የማመን ያህል ነው! በማሰብ ችሎታህ ተጠቅመህ ጉዳዩን በጥንቃቄ ካጤንከው ስለ አምላክ ለመናገር የበለጠ ድፍረት ይኖርሃል።

      በሚቀጥለው ምዕራፍ

      በአንተ ዕድሜ ያሉ ወጣቶች ሲጠመቁ ትመለከት ይሆናል። አንተስ ለመጠመቅ ዝግጁ ነህ?

      ቁልፍ ጥቅስ

      “በምሥራቹ አላፍርም፤ እንዲያውም ምሥራቹ ለሚያምን ሁሉ . . . መዳን የሚያስገኝ የአምላክ ኃይል ነው።”​—ሮም 1:16

      ጠቃሚ ምክር

      ስለ እምነትህ ስትናገር ሐሳብህን ለምትገልጽበት መንገድ ትኩረት ልትሰጠው ይገባል። ሁኔታህ በእምነትህ እንደምታፍር የሚያሳይ ከሆነ እኩዮችህ እንዲያሾፉብህ መንገድ ትከፍታለህ። ይሁንና አብረውህ የሚማሩት ልጆች የራሳቸውን አመለካከት ሲገልጹ እንደሚያደርጉት አንተም በልበ ሙሉነት የምትናገር ከሆነ በእነሱ ዘንድ አክብሮት ማትረፍህ አይቀርም።

      ይህን ታውቅ ነበር?

      አንዳንድ ጊዜ አስተማሪዎች የዝግመተ ለውጥ ጽንሰ ሐሳብ ትክክል መሆኑን የሚያሳይ ማስረጃ እንዲያቀርቡ ሲጠየቁ ይህን ማድረግ ያቅታቸዋል፤ በዚህ ጊዜ ጽንሰ ሐሳቡን የተቀበሉት በእርግጥ አምነውበት ሳይሆን በዚህ መንገድ ስለተማሩ ብቻ መሆኑን ይገነዘባሉ።

      ላደርጋቸው ያሰብኳቸው ነገሮች

      ከክፍሌ ልጅ ጋር ስለ መጽሐፍ ቅዱስ ውይይት ለመጀመር እንዲህ ማለት እችላለሁ፦ ․․․․․

      በፈጣሪ የማምነው ለምን እንደሆነ ብጠየቅ እንዲህ እላለሁ፦ ․․․․․

      ከዚህ ርዕሰ ጉዳይ ጋር በተያያዘ ወላጆቼን ልጠይቃቸው የምፈልገው ነገር ․․․․․

      ምን ይመስልሃል?

      ● ስለምታምንባቸው ነገሮች ለሌሎች መናገር አስፈላጊ የሆነው ለምንድን ነው?

      ● በትምህርት ቤት ውስጥ በፍጥረት እንደምታምን ለመናገር ቀላል የሚሆኑልህ የትኞቹ ዘዴዎች ናቸው?

      ● ሁሉን ነገር ለፈጠረው አምላክ አመስጋኝ መሆንህን እንዴት መግለጽ ትችላለህ?​—የሐዋርያት ሥራ 17:26, 27

      [በገጽ 299 ላይ የሚገኝ የተቀነጨበ ሐሳብ]

      ትምህርት ቤት እኛ ብቻ መስበክ የምንችልበት የአገልግሎት ክልል ነው።”​—ኢራይዳ

      [በገጽ 298 ላይ የሚገኝ ሥዕል]

      ስለ እምነትህ መናገር ልክ የሙዚቃ መሣሪያ እንደ መጫወት ችሎታ ይጠይቃል፤ በተለማመድክ ቁጥር ይበልጥ ብቃት እያዳበርክ ትሄዳለህ

      [በገጽ 300 እና 301 ላይ የሚገኝ ሥዕል]

      ስለ እምነትህ በመናገር ረገድ የሚሰማህን ፍርሃት ማሸነፍ ትችላለህ

አማርኛ ጽሑፎች (1991-2025)
ውጣ
ግባ
  • አማርኛ
  • አጋራ
  • የግል ምርጫዎች
  • Copyright © 2025 Watch Tower Bible and Tract Society of Pennsylvania
  • የአጠቃቀም ውል
  • ሚስጥር የመጠበቅ ፖሊሲ
  • ሚስጥር የመጠበቅ ማስተካከያ
  • JW.ORG
  • ግባ
አጋራ