-
አብርሃምና ሣራ አምላክን ታዘዋልከመጽሐፍ ቅዱስ ታሪኮች ምን ትማራለህ?
-
-
ትምህርት 8
አብርሃምና ሣራ አምላክን ታዘዋል
በባቤል አቅራቢያ የምትገኝ ዑር የምትባል አንዲት ከተማ ነበረች፤ በከተማዋ የሚኖሩ ሰዎች ይሖዋን ሳይሆን ሌሎች አማልክትን ያመልኩ ነበር። ሆኖም በዚህች ከተማ የሚኖር ይሖዋን ብቻ የሚያመልክ አንድ ሰው ነበር። ይህ ሰው አብርሃም ይባላል።
ይሖዋ አብርሃምን ‘ቤትህንና ዘመዶችህን ትተህ እኔ ወደማሳይህ ምድር ሂድ’ አለው። ከዚያም አምላክ እንዲህ ብሎ ቃል ገባለት፦ ‘ብዙ ሕዝብ ትሆናለህ፤ እንዲሁም በአንተ አማካኝነት ለምድር ሕዝቦች ሁሉ ጥሩ ነገር አደርግላቸዋለሁ።’
አብርሃም፣ ይሖዋ ወዴት እንደሚልከው ባያውቅም በይሖዋ ታምኗል። ስለዚህ አብርሃም፣ ሚስቱ ሣራ፣ አባቱ ታራ እንዲሁም የወንድሙ ልጅ ሎጥ ዕቃቸውን ይዘው በታዛዥነት ረጅሙን ጉዞ ጀመሩ።
አብርሃምና ቤተሰቡ ይሖዋ ሊያሳያቸው ወደፈለገው ቦታ ሲደርሱ አብርሃም 75 ዓመቱ ነበር። ያ ቦታ የከነአን ምድር ይባል ነበር። እዚያ ከደረሱ በኋላ አምላክ አብርሃምን አነጋገረው፤ ‘ይህን የምታየውን ቦታ ሁሉ ለልጆችህ እሰጣቸዋለሁ’ ብሎ ቃል ገባለት። አብርሃምና ሣራ ግን አርጅተው የነበረ ሲሆን ምንም ልጅ አልነበራቸውም። ታዲያ ይሖዋ የገባውን ቃል የሚፈጽመው እንዴት ነው?
“አብርሃም . . . ወደፊት ርስት አድርጎ ወደሚቀበለው ስፍራ በመሄድ በእምነት ታዘዘ፤ ወዴት እንደሚሄድ ባያውቅም ይኖርበት የነበረውን ስፍራ ለቆ ወጣ።”—ዕብራውያን 11:8
-
-
በመጨረሻ ልጅ ወለዱ!ከመጽሐፍ ቅዱስ ታሪኮች ምን ትማራለህ?
-
-
ትምህርት 9
በመጨረሻ ልጅ ወለዱ!
አብርሃምና ሣራ ተጋብተው ለረጅም ጊዜ ኖረዋል። በዑር የነበራቸውን ምቹ ቤት ትተው በድንኳን እየኖሩ ነበር። ሆኖም ሣራ በይሖዋ ትታመን ስለነበር አላጉረመረመችም።
ሣራ ልጅ ማግኘት በጣም ትፈልግ ስለነበር አብርሃምን ‘አገልጋዬ አጋር ልጅ ብትወልድ ልጁ እንደ ራሴ ልጅ ይሆናል’ አለችው። ከጊዜ በኋላ አጋር ወንድ ልጅ ወለደች። የልጁ ስም እስማኤል ይባላል።
ከብዙ ዓመታት በኋላ ማለትም አብርሃም 99 ዓመት፣ ሣራ ደግሞ 89 ዓመት ሲሆናቸው ሦስት እንግዶች ወደ እነአብርሃም ቤት መጡ። አብርሃም እንግዶቹን ዛፍ ሥር እንዲያርፉና ምግብ እንዲበሉ ጠየቃቸው። እነዚህ እንግዶች እነማን እንደሆኑ ታውቃለህ? መላእክት ነበሩ! እነሱም አብርሃምን ‘በሚቀጥለው ዓመት በዚህ ጊዜ ሚስትህ ወንድ ልጅ ትወልዳለች’ አሉት። ሣራ ድንኳኑ ውስጥ ሆና የሚሉትን ትሰማ ነበር። ይህን ስትሰማ ‘አሁን እንዲህ ካረጀሁ በኋላ ልጅ መውለድ እችላለሁ?’ ብላ በማሰብ ሳቀች።
በቀጣዩ ዓመት ልክ የይሖዋ መልአክ እንደተናገረው ሣራ ወንድ ልጅ ወለደች። አብርሃም ልጁን ይስሐቅ ብሎ ስም አወጣለት፤ ይስሐቅ ማለት “ሳቅ” ማለት ነው።
ይስሐቅ አምስት ዓመት አካባቢ ሲሆነው ሣራ፣ እስማኤል በይስሐቅ ላይ ሲያሾፍበት አየች። ልጇን ለመጠበቅ ስትል አጋርንና እስማኤልን እንዲያባርራቸው አብርሃምን ጠየቀችው። አብርሃም መጀመሪያ ላይ እንደዚህ ማድረግ አልፈለገም ነበር። ሆኖም ይሖዋ ለይስሐቅ ጥበቃ ማድረግ ስለፈለገ አብርሃምን እንዲህ አለው፦ ‘ሣራ የምትልህን ስማ። እስማኤልን እኔ እንከባከበዋለሁ። የገባሁልህ ቃል የሚፈጸመው ግን በይስሐቅ በኩል ነው።’
“ሣራም የተስፋን ቃል የሰጠው እሱ ታማኝ እንደሆነ አድርጋ ስላሰበች . . . ዘር ለመፀነስ በእምነት ኃይል አገኘች።”—ዕብራውያን 11:11
-
-
የሎጥን ሚስት አስታውሱከመጽሐፍ ቅዱስ ታሪኮች ምን ትማራለህ?
-
-
ትምህርት 10
የሎጥን ሚስት አስታውሱ
ሎጥ፣ ከአጎቱ ከአብርሃም ጋር በከነአን ምድር ይኖር ነበር። አብርሃምና ሎጥ የነበሯቸው እንስሳት በጣም እየበዙ ስለሄዱ መሬቱ ለእነዚያ ሁሉ እንስሳት ሊበቃቸው አልቻለም። ስለዚህ አብርሃም ሎጥን እንዲህ አለው፦ ‘ከዚህ በኋላ አንድ ቦታ ላይ አብረን መኖር አንችልም። እባክህ አንተ መሄድ የምትፈልግበትን ቦታ ምረጥ፤ ከዚያም እኔ ወደ ሌላ ቦታ እሄዳለሁ።’ አብርሃም እንዲህ ብሎ መናገሩ ራስ ወዳድ ሰው እንዳልነበረ ያሳያል።
ሎጥ ሰዶም በምትባል ከተማ አቅራቢያ የሚያምር አካባቢ አየ። በአካባቢው ብዙ ውኃ እንዲሁም የለመለመ ሣር ነበር። ስለዚህ ሎጥ ያንን ቦታ መርጦ ከቤተሰቡ ጋር በዚያ መኖር ጀመረ።
በሰዶምና በአቅራቢያዋ በምትገኘው በገሞራ ከተማ የሚኖሩት ሰዎች በጣም መጥፎ ነበሩ። እንዲያውም ሰዎቹ በጣም መጥፎ ከመሆናቸው የተነሳ ይሖዋ እነዚያን ከተሞች ለማጥፋት ወስኖ ነበር። ነገር ግን ይሖዋ ሎጥንና ቤተሰቡን ሊያድናቸው ስለፈለገ እንዲያስጠነቅቋቸው ሁለት መላእክት ላከ። መላእክቱም ‘ቶሎ በሉ! ከዚህች ከተማ ውጡ። ይሖዋ ከተማዋን ሊያጠፋት ነው’ አሏቸው።
ሎጥ ግን ወዲያውኑ ከከተማዋ ከመውጣት ይልቅ እዚያው ቆየ። ስለዚህ መላእክቱ ሎጥን፣ ሚስቱንና ሁለቱን ልጆቹን እጃቸውን ይዘው በፍጥነት ከከተማዋ አስወጧቸው። እንዲህም አሏቸው፦ ‘ሩጡ! ሕይወታችሁን ለማትረፍ አምልጡ፤ ወደ ኋላ አትመልከቱ። ወደ ኋላ ከተመለከታችሁ ትሞታላችሁ!’
ሎጥና ቤተሰቡ ዞአር ወደተባለች ከተማ ሲደርሱ ይሖዋ በሰዶምና በገሞራ ላይ እሳትና ድኝ አዘነበባቸው። ሁለቱም ከተሞች ሙሉ በሙሉ ጠፉ። የሎጥ ሚስት ይሖዋን ሳትታዘዝ ወደ ኋላ በመመልከቷ የጨው ዓምድ ሆነች! ሎጥና ሴቶች ልጆቹ ግን ይሖዋን በመታዘዛቸው በሕይወት ተረፉ። የሎጥ ሚስት ይሖዋን ባለመታዘዟ ሎጥና ልጆቹ በጣም አዝነው መሆን አለበት። ይህ ታሪክ የይሖዋን መመሪያ መታዘዝ ምን ያህል አስፈላጊ እንደሆነ ያስተምረናል።
“የሎጥን ሚስት አስታውሱ።”—ሉቃስ 17:32
-
-
የአብርሃም እምነት ተፈተነከመጽሐፍ ቅዱስ ታሪኮች ምን ትማራለህ?
-
-
ትምህርት 11
የአብርሃም እምነት ተፈተነ
አብርሃም፣ ልጁ ይስሐቅ ይሖዋን እንዲወድና እሱ በገባው ቃል ላይ እምነት እንዲኖረው አስተምሮታል። ሆኖም ይስሐቅ 25 ዓመት አካባቢ ሲሆነው ይሖዋ አብርሃምን አንድ በጣም ከባድ ነገር እንዲያደርግ ጠየቀው። ይሖዋ ለአብርሃም ያቀረበው ጥያቄ ምን ነበር?
አምላክ አብርሃምን ‘እባክህ አንድ ልጅህን ወስደህ በሞሪያ ምድር በሚገኝ ተራራ ላይ መሥዋዕት አድርገህ አቅርበው’ አለው። አብርሃም፣ ይሖዋ እንዲህ እንዲያደርግ የጠየቀው ለምን እንደሆነ አላወቀም ነበር። ቢሆንም ይሖዋን ታዟል።
በማግስቱ ጠዋት አብርሃም ይስሐቅንና ሁለት አገልጋዮቹን ይዞ ወደ ሞሪያ ሄደ። ለሦስት ቀን ከተጓዙ በኋላ ከርቀት ተራራው ታያቸው። አብርሃም፣ እሱና ይስሐቅ መሥዋዕት አቅርበው እስኪመለሱ ድረስ አገልጋዮቹ እዚያው እንዲቆዩ ነገራቸው። አብርሃም ለእሳት ማንደጃ የሚሆነውን እንጨት ይስሐቅ እንዲሸከም አደረገ፤ እሱ ደግሞ ቢላውን ያዘ። ይስሐቅ አባቱን ‘መሥዋዕት የምናደርገው በግ የት አለ?’ ብሎ ጠየቀው። አብርሃምም ‘ልጄ፣ በጉን ይሖዋ ያዘጋጃል’ ብሎ መለሰለት።
በመጨረሻም ተራራው ጋ ሲደርሱ መሠዊያ ሠሩ። ከዚያም አብርሃም የይስሐቅን እጆችና እግሮች አስሮ መሠዊያው ላይ አስተኛው።
አብርሃም ቢላውን አነሳ። በዚህ ጊዜ የይሖዋ መልአክ ከሰማይ እንዲህ አለው፦ ‘አብርሃም፣ ልጁን እንዳትነካው! ልጅህን እንኳ መሥዋዕት ለማድረግ ፈቃደኛ ስለሆንክ በአምላክ ላይ እምነት እንዳለህ አሁን አወቅኩ።’ ከዚያም አብርሃም አንድ አውራ በግ ቀንዶቹ በዛፍ ቅርንጫፎች ተይዘው አየ። ወዲያውኑ ይስሐቅን ፈታውና በጉን መሥዋዕት አድርጎ አቀረበ።.
ከዚያ ቀን አንስቶ ይሖዋ አብርሃምን ‘ወዳጄ’ በማለት ይጠራው ጀመር። ለምን እንደሆነ ታውቃለህ? አብርሃም፣ ይሖዋ አንድ ነገር እንዲያደርግ ያዘዘው ለምን እንደሆነ ቢገባውም ባይገባውም ምንጊዜም ይታዘዝ ነበር።
ከዚያም ይሖዋ ለአብርሃም ‘እባርክሃለሁ፤ ዘርህን ወይም ልጆችህን አበዛልሃለሁ’ በማለት በድጋሚ ቃል ገባለት። በተጨማሪም ይሖዋ ጥሩ ሰዎችን በሙሉ በአብርሃም ቤተሰብ በኩል እንደሚባርክ ቃል ገባ።
“አምላክ ዓለምን እጅግ ከመውደዱ የተነሳ በልጁ የሚያምን ሁሉ የዘላለም ሕይወት እንዲኖረው እንጂ እንዳይጠፋ ሲል አንድያ ልጁን ሰጥቷል።”—ዮሐንስ 3:16
-