-
ሰው ሁሉ የይሖዋን ክብር ያውጅመጠበቂያ ግንብ—2004 | ጥር 1
-
-
1, 2. ይሖዋን እያወደሱ ያሉት እንዲሁም በዚህ ሥራ እንዲካፈሉ ማበረታቻ የተሰጣቸው እነማን ናቸው?
የእሴይ ልጅ ዳዊት ያደገው በቤተ ልሔም አካባቢ እረኛ ሆኖ ነበር። ፀጥ እረጭ ባለ ምሽት የአባቱን መንጎች ሲጠብቅ በከዋክብት የተሞላውን የተንጣለለ ሰማይ በመመልከት ብዙ ጊዜ ሳይደመም አልቀረም! በአምላክ ቅዱስ መንፈስ አነሳሽነት በ19ኛው መዝሙር ላይ የሚገኙትን ግሩም ቃላት ባቀናበረበትና በዘመረበት ወቅት ይህ አስደናቂ እይታ ወደ አእምሮው እንደመጣ አያጠራጥርም። እንዲህ ሲል ዘምሯል:- “ሰማያት የእግዚአብሔርን ክብር ይናገራሉ፣ የሰማይም ጠፈር የእጁን ሥራ ያወራል። ድምፃቸው ወደ ምድር ሁሉ፣ ቃላቸውም እስከ ዓለም ዳርቻ ወጣ።”—መዝሙር 19:1, 4
2 ይሖዋ ግርማ ሞገስ አላብሶ የፈጠራቸው ሰማያት ንግግርም ሆነ ቃል እንዲሁም ድምፅ ሳያሰሙ ቀንና ሌሊት የእርሱን ክብር ያውጃሉ። ፍጥረት ያለማቋረጥ የይሖዋን ክብር የሚያውጅ ሲሆን ሁሉም ሰው እንዲሰማው “ወደ ምድር ሁሉ” በወጣው በዚህ ምስክርነት ላይ ማሰላሰላችን ከቁጥር የማንገባ መሆናችንን እንድናስተውል ያደርጋል። ሆኖም ፍጥረት ያለ ድምፅ የሚሰጠው ምስክርነት በቂ አይደለም። ታማኝ የሰው ልጆችም ድምፃቸውን በማሰማት ተፈጥሮ ለሚሰጠው ምስክርነት ድጋፍ እንዲሰጡ ተበረታተዋል። ስሙ ያልተገለጸ አንድ መዝሙራዊ በመንፈስ አነሳሽነት ታማኝ አምላኪዎችን “ክብርንና ምስጋናን ለእግዚአብሔር አምጡ፤ ለስሙ የሚገባ ክብርን ለእግዚአብሔር አምጡ” ብሏቸዋል። (መዝሙር 96:7, 8) ከይሖዋ ጋር የቅርብ ዝምድና ያላቸው ሰዎች ለዚህ ማበረታቻ በደስታ ምላሽ ይሰጣሉ። ይሁን እንጂ ለአምላክ ክብር ማምጣት ምን ነገሮችን ይጨምራል?
-
-
ሰው ሁሉ የይሖዋን ክብር ያውጅመጠበቂያ ግንብ—2004 | ጥር 1
-
-
6. ጳውሎስ መዝሙር 19:4ን የተጠቀመበት እንዴት ነው?
6 ቀጥሎም ጳውሎስ “እንግዲህ ያላመኑበትን እንዴት አድርገው ይጠሩታል? ባልሰሙትስ እንዴት ያምናሉ? ያለ ሰባኪስ እንዴት ይሰማሉ?” በማለት ምክንያታዊ ጥያቄዎች አቅርቧል። (ሮሜ 10:14) ጳውሎስ እስራኤላውያንን በተመለከተ “ነገር ግን ሁሉ ምሥራቹን አልታዘዙም” ብሏል። እስራኤላውያን ያልታዘዙት ለምን ነበር? ያልታዘዙት እምነት ስላልነበራቸው እንጂ አጋጣሚውን ስላላገኙ አይደለም። ጳውሎስ መዝሙር 19:4ን በመጥቀስና ጥቅሱን ፍጥረት ያለ ድምፅ ለሚሰጠው ምሥክርነት ሳይሆን ለክርስቲያናዊው የስብከት ሥራ በመጠቀም ይህንን አሳይቷል። “ድምፃቸው በምድር ሁሉ ላይ ቃላቸውም እስከ ዓለም ዳርቻ ወጣ” ብሏል። (ሮሜ 10:16, 18) አዎን፣ ግዑዙ ፍጥረት ይሖዋን እንደሚያከብረው ሁሉ የመጀመሪያው መቶ ዘመን ክርስቲያኖችም የመዳንን ምሥራች በሁሉም ቦታ በመስበክ አምላክን “በምድር ሁሉ ላይ” አወድሰውታል። ጳውሎስ ለቆላስይስ ክርስቲያኖች በጻፈው ደብዳቤ ላይም ምሥራቹ ምን ያህል በስፋት እንደተሰራጨ ገልጿል። ምሥራቹ “ከሰማይ በታች ባለው ፍጥረት ሁሉ ዘንድ” እንደተሰበከ ተናግሯል።—ቆላስይስ 1:23
-