‘ወደ ጉንዳን መሄድ’ ለምን ያስፈልጋል?
የጥንቱ የእስራኤል ንጉሥ የነበረው ጠቢቡ ሰሎሞን “ወደ ገብረ ጉንዳን ሂድ” የሚል ምክር ሰጥቷል። እንደዚህ ያለው ለምን ነበር? ከጉንዳኖች ምን ልንማር እንችላለን?
ሰሎሞን ቀጥሎም:- “መንገድዋንም [የጉንዳንን መንገድ] ተመልክተህ ጠቢብ ሁን። አለቃና አዛዥ ገዢም ሳይኖራት መብልዋን በበጋ ታሰናዳለች፣ መኖዋንም በመከር ትሰበስባለች” ብሏል። (ምሳሌ 6:6-8) እነዚህ በጥንት ጊዜ የተነገሩ ቃሎች እውነተኛ መሆናቸውን የስነ ተፈጥሮ ተመራማሪዎች ደርሰውበታል።
ምሳሌ ተናጋሪው አጉር ጉንዳኖች ‘በተፈጥሮ ጠቢባን’ እንደሆኑ ተናግሯል። (ምሳሌ 30:24, 25) እርግጥ ነው፣ ጥበባቸው የአእምሮ ምርምር ውጤት ሳይሆን ፈጣሪ በተፈጥሮ የለገሳቸው ነው። ለምሳሌ ያህል ጉንዳኖች በተፈጥሮ ዕውቀት ተመርተው ምግባቸውን በተገቢው ጊዜ ይሰበስባሉ።
ጉንዳኖች በአስደናቂ ሁኔታ የተደራጁ ናቸው። የሚያስደንቅ ትብብር አላቸው፣ የሥራ ባልደረቦቻቸውን ሁኔታ በንቃት ይከታተላሉ፣ የተጎዳ ወይም የደከመን ጉንዳን ወደ ጉድጓዱ ይዘውት ይመጣሉ። በተፈጥሯዊ ጥበብ ለወደፊቱ ጊዜ ዝግጅት ያደርጋሉ። ተግባራቸውን ከግቡ ለማድረስም የተቻላቸውን ሁሉ ያደርጋሉ።
የጉንዳን ተፈጥሯዊ እንቅስቃሴ የሰው ልጆች ለወደፊቱ ጊዜ ማቀድ እንዳለባቸውና ጠንክረው እንዲሠሩ ትምህርት ይሆናቸዋል። ይህም በትምህርት ቤት፣ በሥራ ቦታ እና የመንፈሳዊ እንቅስቃሴዎች በሚደረግባቸው ቦታዎች ላይ ይሠራል። ጉንዳኖች ጠንክረው በመሥራታቸው እንደሚጠቀሙ ሁሉ አምላክም ‘ሰው በድካሙ ሁሉ ደስ ይለው ዘንድ’ ይፈልጋል። (መክብብ 3:13, 22፤ 5:18) ሲሠሩ እንደሚውሉት ጉንዳኖች ሁሉ እውነተኛ ክርስቲያኖችም በየቀኑ ጥሩ ተግባር ሲያከናውኑ ይውላሉ። የመሥሪያ ቤት አለቃቸው ስለሚያያቸው ሳይሆን ከታማኝነት፣ ታታሪ ለመሆን ከመፈለግ እና ምርታማ ሠራተኞች በመሆናቸው ‘እጃቸው ማድረግ የምትችለውን ሁሉ ያደርጋሉ።’ — መክብብ 9:10ን ከምሳሌ 6:9-11 ጋር አወዳድር፤ በተጨማሪም ቲቶ 2:9, 10ን ተመልከት።
‘ወደ ጉንዳን ሄደን’ ከእነርሱ የተማርነውን ብንሠራበት በእርግጥ ደስተኞች እንሆናለን። በመጽሐፍ ቅዱስ የተገለጸውን የይሖዋን ፈቃድ በትጋት የምንፈጽም ከሆነ ደስታችን ወደር አይኖረውም።