-
አሦራውያንን አትፍሯቸውየኢሳይያስ ትንቢት—ለመላው የሰው ዘር የፈነጠቀ ብርሃን ጥራዝ 1
-
-
አሥረኛው የኢሳይያስ ምዕራፍ በዋነኛነት ያተኮረው ይሖዋ የአሦራውያንን ወረራ በመጠቀም በእስራኤል ላይ የቅጣት ፍርዱን በማስፈጸሙና ኢየሩሳሌምን ለመጠበቅ በገባው ቃል ላይ ነው። ከኢሳይያስ 10 ቁጥር 20 እስከ 23 ያሉት ቁጥሮች በትንቢቱ መሐል የሚገኙ በመሆናቸው በተመሳሳይ ወቅት ላይ አጠቃላይ ፍጻሜያቸውን እንደሚያገኙ ተደርገው ሊታዩ ይችላሉ። (ከኢሳይያስ 1:7-9 ጋር አወዳድር።) ይሁን እንጂ ከቃላቱ አቀማመጥ መረዳት እንደሚቻለው እነዚህ ቁጥሮች በትክክል የሚያመለክቱት ኢየሩሳሌምም ጭምር ለነዋሪዎቿ ኃጢአት መልስ ስለምትሰጥበት የኋለኛው ጊዜ ነው።
ንጉሥ አካዝ ለደኅንነቱ ዋስትና እንዲሆነው የአሦርን እርዳታ ለማግኘት ሞክሯል። ነቢዩ ኢሳይያስ ወደፊት ከእስራኤል ቤት የተረፉት ሰዎች በፍጹም እንዲህ ያለ ከንቱ ጎዳና እንደማይከተሉ አስቀድሞ ተናግሯል። ኢሳይያስ 10:20 “በእስራኤል ቅዱስ በእግዚአብሔር ላይ በእውነት” እንደሚታመኑ ይናገራል። ይሁን እንጂ ኢሳይያስ 10 ቁጥር 21 ይህንን የሚያደርጉት ‘ጥቂት ቀሪዎች’ ብቻ እንደሆኑ ይገልጻል። ይህም እንደ ምልክት የሆነውንና ‘ጥቂት ቀሪዎች ብቻ ይመለሳሉ’ የሚል ትርጉም ያዘለ ስም ያለውን የኢሳይያስ ልጅ ያሱብን ያስታውሰናል። (ኢሳይያስ 7:3) ኢሳይያስ ምዕራፍ 10 ቁጥር 22 የተቀጠረ “ጥፋት” እንዳለ ያስጠነቅቃል። በዓመፀኛ ሕዝብ ላይ የሚፈጸመው እንዲህ ያለው ጥፋት ተገቢ ቅጣት በመሆኑ የጽድቅ እርምጃ ነው። ከዚህ የተነሣ “እንደ ባሕር አሸዋ” ካለው ትልቅ ብሔር መካከል የሚመለሱት ጥቂት ቀሪዎች ብቻ ይሆናሉ። ኢሳይያስ 10 ቁጥር 23 ደግሞ መጪው ጥፋት ምድሪቱን በሙሉ የሚጠቀልል እንደሚሆን ያስጠነቅቃል። በዚህ ጊዜ ኢየሩሳሌምም ብትሆን አትተርፍም።
-
-
አሦራውያንን አትፍሯቸውየኢሳይያስ ትንቢት—ለመላው የሰው ዘር የፈነጠቀ ብርሃን ጥራዝ 1
-
-
ከሮሜ 9:27, 28 መረዳት እንደሚቻለው በኢሳይያስ 10:20-23 ላይ የሚገኘው ትንቢት በመጀመሪያው መቶ ዘመንም ተጨማሪ ፍጻሜ ነበረው። (ከኢሳይያስ 1:9፤ ሮሜ 9:29 ጋር አወዳድር።) ጥቂት ቁጥር ያላቸው የታመኑ አይሁዳውያን የኢየሱስ ክርስቶስ ተከታዮች በመሆን ይሖዋን “በመንፈስና በእውነት” ማምለክ በመጀመራቸው ጳውሎስ በመንፈሳዊ ሁኔታ አይሁዳውያን ‘ቀሪዎች’ በመጀመሪያው መቶ ዘመን ወደ ይሖዋ ‘እንደተመለሱ’ ተናግሯል። (ዮሐንስ 4:24) ከጊዜ በኋላ ከእነዚህ ሌላ ያመኑ አሕዛብም ተጨምረው ‘የአምላክ እስራኤል’ መንፈሳዊ ብሔር ሆነዋል። (ገላትያ 6:16) በዚህ ጊዜ “ከእንግዲህ ወዲህ” ራሱን ለይሖዋ የወሰነ ብሔር ከእርሱ ዘወር በማለት በሰብዓዊ ኃይሎች እንደማይታመን የሚናገሩት የኢሳይያስ 10:20 ቃላት ፍጻሜያቸውን አግኝተዋል።
-