-
መመሪያና ጥበቃ ለማግኘት በይሖዋ ታመኑየኢሳይያስ ትንቢት—ለመላው የሰው ዘር የፈነጠቀ ብርሃን ጥራዝ 1
-
-
ከአዛጦን ጋር የተደረገ ውጊያ
5. በኢሳይያስ ዘመን የነበረው ኃያል የአሦር ንጉሥ ማን ነው? መጽሐፍ ቅዱስ ስለ እርሱ የሚናገረው ነገር ትክክለኛነት የተረጋገጠውስ እንዴት ነው?
5 በኢሳይያስ ዘመን በንጉሥ ሳርጎን ይመራ የነበረው የአሦር ግዛት ኃይሉ እጅግ ገንኖ ነበር።a ተቺዎች የዚህን ገዥ ስም ከመጽሐፍ ቅዱስ ውጭ ሌላ የትም ቦታ ተጠቅሶ ስላላገኙት ለብዙ ዓመታት ሕልውናውን ሲጠራጠሩ ኖረዋል። ይሁን እንጂ ከጊዜ በኋላ አርኪኦሎጂስቶች የሳርጎንን ቤተ መንግሥት በቁፋሮ በማግኘታቸው የመጽሐፍ ቅዱስ ዘገባ ትክክለኛነት ተረጋግጧል።
6, 7. (ሀ) ሳርጎን በአዛጦን ላይ ጥቃት እንዲሰነዘር ትእዛዝ የሰጠበት ምክንያት ምን ሳይሆን አይቀርም? (ለ) የአዛጦን ድል መመታት የፍልስጥኤምን አጎራባች አገሮች የሚነካው እንዴት ነው?
6 ኢሳይያስ፣ ሳርጎን ካደረጋቸው ወታደራዊ ዘመቻዎች መካከል ስለ አንዱ በአጭሩ ሲጠቅስ እንዲህ ብሏል:- ‘የአሦር ንጉሥ ሳርጎን ተርታንን ሰደደ እርሱም ወደ አዛጦን በመጣ ጊዜ አዛጦንን ወግቶ ያዛት።’ (ኢሳይያስ 20:1)b ሳርጎን በፍልስጥኤማውያኑ የአዛጦን ከተማ ላይ ጥቃት እንዲሰነዘር ትእዛዝ ያስተላለፈው ለምንድን ነው? በመጀመሪያ ደረጃ ፍልስጥኤም የግብጽ አጋር ነች። ከዚህም ሌላ የዳጎን ቤተ መቅደስ መቀመጫ የሆነችው አዛጦን የምትገኘው ከግብጽ ተነስቶ በፍልስጤም በኩል በሚያልፈው በባሕር ዳርቻው አቅራቢያ ባለው ጎዳና ላይ ነበር። ከዚህ የተነሣ ከተማዋ የምትገኘው ቁልፍ ቦታ ላይ ነበር። ይህችን ከተማ መቆጣጠር ግብጽን ድል ለማድረግ መንገድ እንደሚጠርግ ትልቅ እርምጃ ሊታይ ይችላል። ከዚህም በተጨማሪ የአሦራውያን መዛግብት እንደሚጠቁሙት የአዛጦን ንጉሥ የነበረው አዙራይ በአሦር ላይ ሴራ ጠንስሶ ነበር። በመሆኑም ሳርጎን ዓመፀኛውን ንጉሥ ከቦታው በማስወገድ ታናሽ ወንድሙን አሂሚታይን በዙፋኑ ላይ አስቀምጧል። ያም ሆኖ ግን ችግሩ አልተፈታም። ሌላ ዓመፅ በመፈንዳቱ ሳርጎን ጠንከር ያለ እርምጃ ወስዷል። በአዛጦን ላይ ጥቃት እንዲሰነዝሩ ትእዛዝ በማስተላለፉ ከተማዋን ከብበው ድል አደረጓት። ኢሳይያስ 20:1 የሚጠቅሰው ይህንን ሳይሆን አይቀርም።
7 የአዛጦን ድል መመታት በአጎራባቾቿ በተለይም ደግሞ በይሁዳ ላይ የስጋት ደመና እንዲያጠላ የሚያደርግ ነበር። ይሖዋ ሕዝቡ ‘በሥጋ ክንድ’ ማለትም በግብጽ ወይም በስተደቡብ ባለችው በኢትዮጵያ ወደ መታመን እንደሚያዘነብሉ ያውቃል። ከዚህ የተነሣ ኢሳይያስ በተግባራዊ መግለጫ የተደገፈ አንድ ጠንካራ ማስጠንቀቂያ እንዲያስተላልፍ ላከው።—2 ዜና መዋዕል 32:7, 8
-