የመጠበቂያ ግንብ የኢንተርኔት ቤተ መጻሕፍት
መጠበቂያ ግንብ
የኢንተርኔት ቤተ መጻሕፍት
አማርኛ
፦
  • ፡
  • መጽሐፍ ቅዱስ
  • የሕትመት ውጤቶች
  • ስብሰባዎች
  • ለንጉሥ የሚቀርቡ ስጦታዎች
    መጠበቂያ ግንብ—2015 | መጋቢት 1
    • ደስ የሚል መዓዛ ያላቸው የተለያዩ ቅመሞች

      ለንጉሥ የሚቀርቡ ስጦታዎች

      “ኮከብ ቆጣሪዎች ከምሥራቅ አገር ወደ ኢየሩሳሌም መጥተው . . . ወርቅ፣ ነጭ ዕጣንና ከርቤ በስጦታ መልክ አቀረቡለት።”—ማቴዎስ 2:1, 11

      ለአንድ የተከበረ ሰው ስጦታ መስጠት ብትፈልግ ምን ትመርጥ ነበር? በጥንት ዘመን አንዳንድ ቅመሞች የወርቅን ያህል ውድ ነበሩ፤ እንዲሁም ለነገሥታት በስጦታነት ከሚቀርቡት የከበሩ ነገሮች መካከል ይገኙበት ነበር።a ኮከብ ቆጣሪዎቹ ደስ የሚል መዓዛ ያላቸው ሁለት ቅመሞችን ‘ለአይሁድ ንጉሥ’ በስጦታነት ያቀረቡት ለዚህ ነው።—ማቴዎስ 2:1, 2, 11

      የበለሳን ዘይት

      የበለሳን ዘይት

      በተጨማሪም ንግሥት ሳባ ሰለሞንን በጎበኘችበት ወቅት ለንጉሡ ስላመጣቻቸው ነገሮች ሲገልጽ መጽሐፍ ቅዱስ እንዲህ ይላል፦ “አንድ መቶ ሃያ መክሊት ወርቅ፣ እጅግ ብዙ ቅመማ ቅመምና የከበሩ ድንጋዮች ሰጠችው፤ የሳባ ንግሥት ለንጉሥ ሰሎሞን እንደሰጠችው ዐይነት ቅመማ ቅመም ያለ ከቶ አልነበረም።”b (2 ዜና መዋዕል 9:9) ሌሎች ነገሥታትም ለሰለሞን የበለሳን ዘይት ገጸ በረከት አድርገው ልከውለታል።—2 ዜና መዋዕል 9:23, 24

      እንዲህ ዓይነቶቹ ቅመሞችና ተዛማጅነት ያላቸው ምርቶች በጥንት ዘመን በጣም ከፍ ተደርገው የሚታዩት እንዲሁም ውድ የነበሩት ለምንድን ነው? ለተለያዩ አስፈላጊ ዓላማዎች ይውሉ ስለነበር ነው፤ ለምሳሌ ውበትን ለመጠበቅና አስከሬን ለማዘጋጀት ያገለግሉ የነበረ ከመሆኑም ሌላ በሃይማኖታዊ ሥነ ሥርዓቶች ላይ ጥቅም ላይ ይውሉ ነበር። (“ቅመማ ቅመሞች በጥንት ዘመን የነበራቸው ጥቅም” የሚለውን ሣጥን ተመልከት።) ቅመሞች በጣም ተፈላጊ የነበሩ ከመሆኑም ሌላ እነሱን ማጓጓዝና መሸጥ ከፍተኛ ወጪ ስለሚጠይቅ ዋጋቸው ውድ ነበር።

      የአረቢያን በረሃ ማቋረጥ

      ብርጉድ

      ብርጉድ

      በጥንት ዘመን ቅመም የሚገኝባቸው አንዳንድ ተክሎች በዮርዳኖስ ሸለቆ ይበቅሉ ነበር። ሌሎቹ ቅመሞች የሚመጡት ግን ከውጭ አገር ነበር። በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ የተለያዩ የቅመማ ቅመም ምርቶች ተጠቅሰዋል። በጣም ከሚታወቁት መካከል የሳሮን አበባ፣ እሬት፣ በለሳን፣ ቀረፋ፣ ነጭ ዕጣንና ከርቤ ይገኙበታል። ከእነዚህ ሌላ ደግሞ እንደ ከሙን፣ ኮሰረትና እንስላል ያሉ የተለመዱ የምግብ ማጣፈጫዎች ተጠቅሰዋል።

      እነዚህን ቅመሞች የሚያስመጡት ከየት ነበር? እሬት፣ ብርጉድና ቀረፋ የሚመጡት ከአሁኗ ሕንድ፣ ስሪ ላንካና ቻይና ነበር። እንደ ከርቤና ነጭ ዕጣን ያሉት ቅመሞች የሚገኙት ከደቡብ አረቢያ አንስቶ በአፍሪካ እስካለችው ሶማሊያ ድረስ ባለው በረሃማ አካባቢ ከሚበቅሉ ዛፎችና ቁጥቋጦዎች ነው። ናርዶስ ደግሞ በሂማላያ አካባቢ ብቻ የሚገኝ የሕንድ ምርት ነበር።

      የሳሮን አበባ

      የሳሮን አበባ

      ብዙ የቅመማ ቅመም ምርቶች ወደ እስራኤል የሚላኩት በአረቢያ በኩል ነበር። አረቢያ በሁለተኛውና በአንደኛው መቶ ዘመን ዓ.ዓ. “በምሥራቅና በምዕራብ መካከል ሸቀጦችን የማጓጓዙን ሥራ መቆጣጠር” የቻለችበት አንዱ ምክንያት ይህ እንደሆነ ዘ ቡክ ኦቭ ስፓይስስ (የቅመማ ቅመም መጽሐፍ) የተባለ ጽሑፍ ገልጿል። በደቡብ እስራኤል በሚገኘው በኔጌቭ ያሉት ጥንታዊ ከተሞች፣ ምሽጎችና የሲራራ ነጋዴዎች ማረፊያ የነበሩ ሰፈሮች የቅመማ ቅመም ሻጮች ለጉዞ ይጠቀሙበት የነበረውን መንገድ ለማወቅ ያስችሉናል። በተጨማሪም እነዚህ ቦታዎች “ከደቡብ አረቢያ እስከ ሜድትራንያን ይካሄድ የነበረውን እጅግ አትራፊ የሆነ . . . ንግድ” እንደሚያሳዩ የዩኔስኮ የዓለም ቅርስ ማዕከል ዘግቧል።

      “መጠናቸው ትንሽ፣ ዋጋቸው ከፍ ያለ እንዲሁም በሸማቾች ዘንድ ሁልጊዜ ተፈላጊ የነበሩት ቅመማ ቅመሞች በተለይ በንግድ ሸቀጥነታቸው ተመራጭ ነበሩ።” —የቅመማ ቅመም መጽሐፍ

      እነዚህን ደስ የሚል መዓዛ ያላቸው ቅመማ ቅመሞች የጫኑ ሲራራ ነጋዴዎች አረቢያን በማቋረጥ እስከ 1,800 ኪሎ ሜትር የሚደርስ ርቀት አዘውትረው ይጓዙ ነበር። (ኢዮብ 6:19) መጽሐፍ ቅዱስ፣ “ሽቶ፣ በለሳን ከርቤ በግመሎቻቸው ጭነው” ከገለዓድ ወደ ግብፅ ስለወረዱ እስማኤላውያን ነጋዴዎች ይናገራል። (ዘፍጥረት 37:25) የያዕቆብ ልጆች ወንድማቸውን ዮሴፍን ለባርነት የሸጡት ለእነዚህ ነጋዴዎች ነው።

  • ለንጉሥ የሚቀርቡ ስጦታዎች
    መጠበቂያ ግንብ—2015 | መጋቢት 1
    • ለኢየሱስ የተሰጡት ሁለት ቅመሞች

      ነጭ ዕጣን እና ከርቤ የሚገኙት የትናንሽ ዛፎችን ወይም የእሾሃማ ቁጥቋጦዎችን ቅርፊት በመሰንጠቅ ከሚወጣው ሙጫ ነው።

      የነጭ ዕጣን ዛፍ ይበቅል የነበረው በደቡብ አረቢያ የባሕር ዳርቻዎች ላይ ሲሆን የከርቤ ቁጥቋጦ ደግሞ ከፊል በረሃማ በሆኑት የአሁኖቹ ሶማሊያና የመን ውስጥ ይገኝ ነበር። ሁለቱም ቅመሞች ደስ በሚል መዓዛቸው የተነሳ ተወዳጅ ነበሩ። ይሖዋም እነዚህ ቅመሞች ለእሱ በሚቀርብለት አምልኮ ውስጥ ጥቅም ላይ እንዲውሉ አዝዞ ነበር፤ የቅብዓት ዘይቱን ለማዘጋጀት ከሚያገለግሉት ነገሮች አንዱ ከርቤ ሲሆን ቅዱስ ዕጣን ይቀመምባቸው ከነበሩ ነገሮች አንዱ ደግሞ ነጭ ዕጣን ነው። (ዘፀአት 30:23-25, 34-37) ይሁን እንጂ እነዚህ ቅመሞች አገልግሎት ላይ የሚውሉት በተለያየ መንገድ ነበር።

      ነጭ ዕጣን መዓዛው እንዲወጣ ሲባል ይጤስ ነበር። በሌላ በኩል ደግሞ ከከርቤ የሚወጣው ሙጫ መጤስ ስለማያስፈልገው በቀጥታ ጥቅም ላይ ይውል ነበር። ከርቤ ስለ ኢየሱስ በሚገልጹት ዘገባዎች ላይ ሦስት ጊዜ ተጠቅሷል፦ በሕፃንነቱ በስጦታነት ቀርቦለታል፤ (ማቴዎስ 2:11) በእንጨት ላይ ተሰቅሎ ሳለ ከወይን ጋር ተቀላቅሎ ለሥቃይ ማስታገሻነት ተሰጥቶታል፤ (ማርቆስ 15:23) እንዲሁም አስከሬኑ ለቀብር በሚዘጋጅበት ወቅት ጥቅም ላይ ከዋሉት ቅመሞች አንዱ ነበር። (ዮሐንስ 19:39)

አማርኛ ጽሑፎች (1991-2025)
ውጣ
ግባ
  • አማርኛ
  • አጋራ
  • የግል ምርጫዎች
  • Copyright © 2025 Watch Tower Bible and Tract Society of Pennsylvania
  • የአጠቃቀም ውል
  • ሚስጥር የመጠበቅ ፖሊሲ
  • ሚስጥር የመጠበቅ ማስተካከያ
  • JW.ORG
  • ግባ
አጋራ