-
‘ክርስቶስ የአምላክ ኃይል ነው’ወደ ይሖዋ ቅረብ
-
-
“በቃል ኃያል”
8. ኢየሱስ ከተቀባ በኋላ ምን እንዲያደርግ ኃይል ተሰጠው? ይህን ኃይልስ የተጠቀመበት እንዴት ነው?
8 ከሁኔታዎች መረዳት እንደሚቻለው ኢየሱስ በልጅነቱ ናዝሬት ውስጥ በነበረበት ወቅት ምንም ተአምር አልፈጸመም። ይሁን እንጂ በ29 ዓ.ም. በ30 ዓመቱ ገደማ ሲጠመቅ ይህ ሁኔታ ተለወጠ። (ሉቃስ 3:21-23) መጽሐፍ ቅዱስ “አምላክ በመንፈስ ቅዱስ ቀባው፤ ደግሞም ኃይል ሰጠው፤ ኢየሱስም . . . መልካም ነገር እያደረገና በዲያብሎስ ቁጥጥር ሥር የወደቁትን እየፈወሰ በዚያ አገር ሁሉ ተዘዋወረ” በማለት ይነግረናል። (የሐዋርያት ሥራ 10:38) “መልካም ነገር እያደረገ” የሚለው አገላለጽ ኢየሱስ ኃይሉን በአግባቡ እንደተጠቀመበት የሚያመለክት ነው። በመንፈስ ቅዱስ ከተቀባ በኋላ “በሥራም ሆነ በቃል ኃያል ነቢይ” ሆነ።—ሉቃስ 24:19
9-11. (ሀ) ኢየሱስ በአብዛኛው ያስተምር የነበረው በየትኞቹ ቦታዎች ነው? ትምህርቱንስ በምን መንገድ ማቅረብ ነበረበት? (ለ) ሕዝቡ በትምህርቱ የተገረሙት ለምን ነበር?
9 ኢየሱስ በቃል ኃያል የሆነው እንዴት ነው? በአብዛኛው ያስተምር የነበረው ደጅ ላይ ማለትም በሐይቅ ዳርቻዎችና በተራራ አጠገብ እንዲሁም በጎዳናዎችና በገበያ ቦታዎች ነበር። (ማርቆስ 6:53-56፤ ሉቃስ 5:1-3፤ 13:26) ትምህርቱ የአድማጮቹን ትኩረት የማይስብ ቢሆን ኖሮ ጥለውት ይሄዱ እንደነበር የታወቀ ነው። መጻሕፍት ይታተሙ ባልነበረበት በዚያ ዘመን አድማጮች ትምህርቱን በጥሞና አዳምጠው በአእምሯቸውና በልባቸው መቅረጽ ያስፈልጋቸው ነበር። በመሆኑም የኢየሱስ ትምህርት አድማጮችን የሚመስጥ፣ ግልጽና በቀላሉ ሊታወስ የሚችል መሆን ነበረበት። ይህን ማድረግ ለኢየሱስ አስቸጋሪ አልነበረም። የተራራ ስብከቱን እንደ ምሳሌ እንመልከት።
10 በ31 ዓ.ም. አንድ ቀን ጠዋት በገሊላ ባሕር አቅራቢያ በሚገኝ አንድ ኮረብታ ላይ ብዙ ሕዝብ ተሰበሰበ። አንዳንዶቹ ከይሁዳና ከኢየሩሳሌም ከ100 እስከ 110 ኪሎ ሜትር ርቀት ተጉዘው የመጡ ናቸው። ሌሎቹ ደግሞ በስተ ሰሜን ከሚገኙት ከጢሮስና ከሲዶና የባሕር ዳርቻዎች የመጡ ናቸው። ኢየሱስ ቀርበው ሊዳስሱት ይሞክሩ የነበሩትን የታመሙ ሰዎች በሙሉ ፈወሳቸው። ሁሉንም ከፈወሰ በኋላ ማስተማር ጀመረ። (ሉቃስ 6:17-19) አስተምሮ ሲጨርስ ሰዎቹ በትምህርቱ እጅግ ተገረሙ። ለምን?
11 በተራራው ስብከት ላይ ተገኝቶ የነበረ አንድ ሰው ከተወሰኑ ዓመታት በኋላ እንዲህ ሲል ጽፏል፦ “ሕዝቡ በትምህርት አሰጣጡ እጅግ ተደነቁ፤ የሚያስተምራቸው . . . እንደ ባለሥልጣን ነበርና።” (ማቴዎስ 7:28, 29) አድማጮቹ ኢየሱስ እንደ ባለሥልጣን ይናገር እንደነበር ማስተዋል ችለዋል። አምላክን ወክሎ ይናገር የነበረ ሲሆን ትምህርቱም በአምላክ ቃል የተደገፈ ነበር። (ዮሐንስ 7:16) ትምህርቶቹ ግልጽ፣ ምክሮቹ አሳማኝ እንዲሁም የሚያቀርባቸው ማስረጃዎች ሊታበሉ የማይችሉ ናቸው። ትምህርቱ ወሳኝ በሆኑ ቁም ነገሮች ላይ ያተኮረ ከመሆኑም በላይ የአድማጮቹን ልብ የሚነካ ነበር። ደስታ ማግኘት፣ መጸለይ፣ የአምላክን መንግሥት መፈለግና ሕይወታቸውን አስተማማኝ በሆነ መሠረት ላይ መገንባት የሚችሉት እንዴት እንደሆነ አስተምሯቸዋል። (ማቴዎስ 5:3 እስከ 7:27) ያስተማረው ትምህርት እውነትንና ጽድቅን የተጠሙ ሰዎችን ልብ ለተግባር አነሳስቷል። እነዚህ ሰዎች ራሳቸውን ‘ለመካድና’ ሁሉን ትተው እሱን ለመከተል ፈቃደኞች ሆነዋል። (ማቴዎስ 16:24፤ ሉቃስ 5:10, 11) ኢየሱስ በቃል ኃያል ነው መባሉ ምንኛ ተገቢ ነው!
“በሥራ . . . ኃያል”
12, 13. ኢየሱስ ‘በሥራ ኃያል’ የነበረው በምን መንገድ ነው? የፈጸማቸው ተአምራት ብዙ ዓይነት ናቸው እንድንል የሚያደርገንስ ምንድን ነው?
12 ኢየሱስ ‘በሥራም ኃያል’ ነበር። (ሉቃስ 24:19) ኢየሱስ ‘በይሖዋ ኃይል’ የፈጸማቸው ከ30 የሚበልጡ ተአምራት በወንጌሎች ውስጥ በቀጥታ ተጠቅሰው እናገኛለን።b (ሉቃስ 5:17) ኢየሱስ የፈጸማቸው ተአምራት በሺዎች በሚቆጠሩ ሰዎች ሕይወት ላይ ለውጥ አምጥተዋል። ለምሳሌ ያህል፣ በአንድ ወቅት 5,000 ወንዶችን በሌላ ወቅት ደግሞ 4,000 ወንዶችን በተአምር መግቧል። ሴቶችና ልጆች ሲጨመሩ በእነዚህ ጊዜያት ኢየሱስ የመገባቸው ሰዎች ጠቅላላ ቁጥር በብዙ ሺዎች የሚቆጠር እንደሚሆን ይገመታል።—ማቴዎስ 14:13-21፤ 15:32-38
13 ኢየሱስ ብዙ ዓይነት ተአምራት ፈጽሟል። አጋንንትን በማስወጣት በእነሱ ላይ ሥልጣን እንዳለው አሳይቷል። (ሉቃስ 9:37-43) ውኃን ወደ ወይን በመለወጥ ግዑዝ በሆኑ ነገሮችም ላይ ኃይል እንዳለው አሳይቷል። (ዮሐንስ 2:1-11) በአንድ ወቅት “ኢየሱስ በባሕሩ ላይ እየተራመደ” ወደ እነሱ ሲመጣ በማየታቸው ደቀ መዛሙርቱ እጅግ ተገርመዋል። (ዮሐንስ 6:18, 19) በበሽታም ላይ ሥልጣን የነበረው ሲሆን አካላዊ ጉድለቶችን፣ ሥር የሰደዱ ሕመሞችንና ለሞት ሊዳርጉ የሚችሉ በሽታዎችን ፈውሷል። (ማርቆስ 3:1-5፤ ዮሐንስ 4:46-54) እነዚህን ፈውሶች ያከናወነው በተለያዩ መንገዶች ነው። አንዳንዶቹ የተፈወሱት ዳስሷቸው ሲሆን ገና በሩቅ ሳለ የተፈወሱም አሉ። (ማቴዎስ 8:2, 3, 5-13) ከዚህም በተጨማሪ አንዳንዶቹ የተፈወሱት ወዲያውኑ ሲሆን አንዳንዶቹ ግን ቀስ በቀስ ነው።—ማርቆስ 8:22-25፤ ሉቃስ 8:43, 44
‘ኢየሱስ በባሕሩ ላይ ሲራመድ ተመለከቱ’
14. ኢየሱስ በሞት ላይ እንኳ ሥልጣን እንዳለው ያሳየው እንዴት ነው?
14 የሚያስገርመው ኢየሱስ በሞት ላይ እንኳ ሥልጣን እንዳለው አሳይቷል። በሦስት የተለያዩ አጋጣሚዎች ኢየሱስ የሞቱ ሰዎችን እንዳስነሳ የሚገልጹ ታሪኮች በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ ሰፍረው እናገኛለን። አንዲትን የ12 ዓመት ልጅ፣ የአንዲትን መበለት አንድያ ልጅና እህቶቹ በጣም ይወዱት የነበረን አንድ ሰው ከሞት አስነስቷል። (ሉቃስ 7:11-15፤ 8:49-56፤ ዮሐንስ 11:38-44) የገጠሙት ሁኔታዎች በሙሉ ከአቅሙ በላይ አልነበሩም። የ12 ዓመቷን ልጅ ያስነሳት ወዲያው እንደሞተች ነበር። የመበለቲቱን ልጅ ያስነሳው በቃሬዛ ተሸክመው ወደ ቀብር እየወሰዱት ሳለ ነበር፤ ስለዚህ ያስነሳው በዚያው በሞተበት ዕለት መሆን አለበት። አልዓዛርን ደግሞ ያስነሳው ሞቶ ከተቀበረ ከአራት ቀን በኋላ ነበር።
-