የመጠበቂያ ግንብ የኢንተርኔት ቤተ መጻሕፍት
መጠበቂያ ግንብ
የኢንተርኔት ቤተ መጻሕፍት
አማርኛ
፦
  • ፡
  • መጽሐፍ ቅዱስ
  • የሕትመት ውጤቶች
  • ስብሰባዎች
  • የአምላክ መንግሥት ምንድን ነው?
    ለዘላለም በደስታ ኑር!—አሳታፊ የመጽሐፍ ቅዱስ መማሪያ
    • ምዕራፍ 31. በሰማይ የነገሠው ኢየሱስ ክርስቶስ በክብራማው የይሖዋ ዙፋን ፊት ቆሞ

      ምዕራፍ 31

      የአምላክ መንግሥት ምንድን ነው?

      የመጽሐፍ ቅዱስ ዋነኛ መልእክት በአምላክ መንግሥት ላይ ያተኮረ ነው። ይሖዋ ምድርን ገነት ለማድረግ ያለውን የመጀመሪያ ዓላማ ዳር የሚያደርሰው በዚህ መንግሥት አማካኝነት ነው። ለመሆኑ የአምላክ መንግሥት ምንድን ነው? በአሁኑ ጊዜ በመግዛት ላይ እንዳለ እንዴት እናውቃለን? እስካሁን ምን ነገሮችን አከናውኗል? ወደፊትስ ምን ነገሮችን ያከናውናል? ይህ ምዕራፍና ቀጣዮቹ ሁለት ምዕራፎች ለእነዚህ ጥያቄዎች መልስ ይሰጣሉ።

      1. የአምላክ መንግሥት ምንድን ነው? ንጉሡስ ማን ነው?

      የአምላክ መንግሥት ይሖዋ አምላክ ያቋቋመው መስተዳድር ነው። የዚህ መንግሥት ንጉሥ ኢየሱስ ክርስቶስ ሲሆን የሚገዛውም ከሰማይ ነው። (ማቴዎስ 4:17፤ ዮሐንስ 18:36) መጽሐፍ ቅዱስ ስለ ኢየሱስ ሲናገር “ለዘላለም ንጉሥ ሆኖ ይገዛል” ይላል። (ሉቃስ 1:32, 33) የአምላክ መንግሥት ንጉሥ የሆነው ኢየሱስ ወደፊት በምድር ላይ ያሉ ሰዎችን ሁሉ ይገዛል።

      2. ከኢየሱስ ጋር አብረው የሚገዙት እነማን ናቸው?

      ኢየሱስ የሚገዛው ብቻውን አይደለም። “ከየነገዱ፣ ከየቋንቋው፣ ከየሕዝቡና ከየብሔሩ” የተውጣጡ ሰዎች ‘በምድር ላይ ነገሥታት ሆነው ይገዛሉ።’ (ራእይ 5:9, 10) ከክርስቶስ ጋር የሚገዙት ሰዎች ምን ያህል ናቸው? ኢየሱስ ወደ ምድር ከመጣ ወዲህ በሚሊዮኖች የሚቆጠሩ ክርስቲያኖች የእሱ ተከታዮች ሆነዋል። ሆኖም ወደ ሰማይ ሄደው ከኢየሱስ ጋር የሚገዙት 144,000 የሚያህሉ ሰዎች ብቻ ናቸው። (ራእይ 14:1-4⁠ን አንብብ።) በምድር ላይ የሚቀሩት ሌሎች ክርስቲያኖች በሙሉ የአምላክ መንግሥት ተገዢዎች ይሆናሉ።—መዝሙር 37:29

      3. የአምላክን መንግሥት ሰዎች ከሚያስተዳድሯቸው መንግሥታት የተሻለ የሚያደርገው ምንድን ነው?

      የመንግሥት ባለሥልጣናት ጥሩ ነገሮችን ማድረግ ቢፈልጉም እንኳ የፈለጉትን ሁሉ ለማድረግ የሚያስችል ኃይል የላቸውም። በተጨማሪም የጊዜ ጉዳይ ነው እንጂ፣ ራስ ወዳድ በሆኑና ሰዎችን መርዳት በማይፈልጉ ሌሎች ባለሥልጣናት መተካታቸው አይቀርም። የአምላክ መንግሥት ንጉሥ የሆነው ኢየሱስ ግን በማንም አይተካም። አምላክ ያቋቋመው መንግሥት “ፈጽሞ የማይጠፋ” ነው። (ዳንኤል 2:44) ኢየሱስ መላዋን ምድር የሚገዛ ሲሆን አንዱን ከሌላው አያበላልጥም። አፍቃሪ፣ ደግና ፍትሐዊ ከመሆኑም በላይ ሰዎችም ልክ እንደ እሱ እነዚህን ባሕርያት እንዲያንጸባርቁ ያስተምራል።—ኢሳይያስ 11:9⁠ን አንብብ።

      ጠለቅ ያለ ጥናት

      የአምላክን መንግሥት ሰዎች ከሚያስተዳድሩት ከየትኛውም መንግሥት የተሻለ የሚያደርገው ምን እንደሆነ እንመለከታለን።

      ኢየሱስ ክርስቶስ በሰማይ ካለው ዙፋኑ ሆኖ ምድርን ሲገዛ። አብረውት የሚገዙት ሰዎች ከጀርባው ተቀምጠዋል። ከበስተኋላቸው ከይሖዋ ዙፋን የሚፈነጥቀው ብርሃን ይታያል

      4. መላዋ ምድር በአንድ ታላቅ መስተዳድር ሥር ትሆናለች

      ኢየሱስ ክርስቶስ እስከ ዛሬ ድረስ በምድር ላይ ከተነሱት ገዢዎች ሁሉ የበለጠ ሥልጣን አለው። ማቴዎስ 28:18⁠ን አንብቡ፤ ከዚያም በሚከተለው ጥያቄ ላይ ተወያዩ፦

      • ኢየሱስ በምድር ላይ ካለ ከየትኛውም ገዢ የበለጠ ሥልጣን አለው የምንለው ለምንድን ነው?

      በዓለም ላይ ያሉት መንግሥታት በየጊዜው ይቀያየራሉ፤ ደግሞም አንድ መንግሥት የሚያስተዳድረው የዓለማችንን የተወሰነ ክፍል ነው። የአምላክ መንግሥትስ? ዳንኤል 7:14⁠ን አንብቡ፤ ከዚያም በሚከተሉት ጥያቄዎች ላይ ተወያዩ፦

      • የአምላክ መንግሥት “የማይጠፋ” መሆኑ ምን ጥቅም አለው?

      • መላዋን ምድር የሚገዛ መሆኑ ምን ጥቅም አለው?

      5. የሰዎች አገዛዝ መተካት አለበት

      የሰዎች አገዛዝ በአምላክ መንግሥት ሊተካ የሚገባው ለምንድን ነው? ቪዲዮውን ተመልከቱ፤ ከዚያም በሚከተለው ጥያቄ ላይ ተወያዩ፦

      ቪዲዮ፦ የአምላክ መንግሥት ምንድን ነው?—ተቀንጭቦ የተወሰደ (1:41)

      • የሰዎች አገዛዝ ምን ውጤት አስከትሏል?

      መክብብ 8:9⁠ን አንብቡ፤ ከዚያም በሚከተሉት ጥያቄዎች ላይ ተወያዩ፦

      • የሰዎች አገዛዝ በአምላክ መንግሥት ሊተካ እንደሚገባ ይሰማሃል? እንዲህ ብለህ የመለስከው ለምንድን ነው?

      6. የአምላክ መንግሥት ገዢዎች ያለንበትን ሁኔታ ይረዱልናል

      ንጉሣችን ኢየሱስ በአንድ ወቅት ሰው ሆኖ ስለኖረ ‘በድካማችን ይራራልናል።’ (ዕብራውያን 4:15) ይሖዋ ከኢየሱስ ጋር እንዲገዙ የመረጣቸው 144,000 ታማኝ ወንዶችና ሴቶች “ከየነገዱ፣ ከየቋንቋው፣ ከየሕዝቡና ከየብሔሩ” የተውጣጡ ናቸው።—ራእይ 5:9

      • ኢየሱስና ከእሱ ጋር የሚገዙት ሰዎች በሙሉ በአንድ ወቅት እንደ እኛው ሰው የነበሩ መሆናቸውን ማወቃችን የሚያጽናናን ለምንድን ነው?

      በተለያዩ ዘመናት የኖሩና የተለያየ አስተዳደግ ያላቸው በመንፈስ የተቀቡ ወንዶችና ሴቶች

      ይሖዋ ከኢየሱስ ጋር እንዲገዙ የመረጣቸው ወንዶችና ሴቶች የተለያየ ዘርና አስተዳደግ ያላቸው ናቸው

      7. የአምላክ መንግሥት ሰዎች ከሚያስተዳድሩት ከየትኛውም መንግሥት የላቁ ሕጎች አሉት

      መንግሥታት ለዜጎቻቸው ጥቅምና ጥበቃ ያስገኛሉ ብለው የሚያስቧቸውን ሕጎች ያወጣሉ። የአምላክ መንግሥትም ተገዢዎቹ ሊያከብሯቸው የሚገቡ ሕጎች አሉት። አንደኛ ቆሮንቶስ 6:9-11⁠ን አንብቡ፤ ከዚያም በሚከተሉት ጥያቄዎች ላይ ተወያዩ፦

      • ሁሉም ሰው አምላክ ያወጣቸውን የሥነ ምግባር ደንቦች ቢከተል ዓለማችን ምን መልክ የሚኖራት ይመስልሃል?a

      • ይሖዋ የመንግሥቱ ተገዢዎች እነዚህን ሕጎች እንዲያከብሩ መጠበቁ ምክንያታዊ ይመስልሃል? እንዲህ ብለህ የመለስከው ለምንድን ነው?

      • እነዚህን ሕጎች የማይታዘዙ ሰዎች ሊለወጡ እንደሚችሉ የሚያሳይ ምን ማስረጃ አለ?—ቁጥር 11⁠ን ተመልከት።

      ብዙ ሰዎች በሚተላለፉበት መንገድ ላይ ትራፊኩን እያስተናበረ ያለ ፖሊስ። የተለያየ ዕድሜ ያላቸው ሰዎች መንገዱን እያቋረጡ ነው

      መንግሥታት ለዜጎቻቸው ጥበቃና ጥቅም የሚያስገኙ የተለያዩ ሕጎችን ያወጣሉ። የአምላክ መንግሥት ለተገዢዎቹ ጥበቃና ጥቅም የሚያስገኙ የላቁ ሕጎች አሉት

      አንድ ሰው እንዲህ ብሎ ቢጠይቅህስ? “የአምላክ መንግሥት ምንድን ነው?”

      • ምን ብለህ ትመልሳለህ?

      ማጠቃለያ

      የአምላክ መንግሥት በሰማይ ያለ መስተዳድር ሲሆን ወደፊት መላዋን ምድር ይገዛል።

      ክለሳ

      • የአምላክ መንግሥት ገዢዎች እነማን ናቸው?

      • የአምላክ መንግሥት ሰዎች ከሚያስተዳድሩት ከየትኛውም መንግሥት የተሻለ የሆነው በየትኞቹ መንገዶች ነው?

      • ይሖዋ ከመንግሥቱ ተገዢዎች የሚጠብቃቸው አንዳንድ ነገሮች ምንድን ናቸው?

      ግብ

      ምርምር አድርግ

      ኢየሱስ የአምላክ መንግሥት የሚገኝበትን ቦታ በተመለከተ ምን አስተምሯል?

      “የአምላክ መንግሥት በሰዎች ልብ ውስጥ ያለ ነገር ነው?” (ድረ ገጻችን ላይ የወጣ ርዕስ)

      የይሖዋ ምሥክሮች፣ ከሰዎች መንግሥት ይልቅ ለአምላክ መንግሥት ታማኝ ለመሆን የሚመርጡት ለምንድን ነው?

      ለአምላክ መንግሥት ታማኝ መሆን (1:43)

      መጽሐፍ ቅዱስ፣ ይሖዋ ከኢየሱስ ጋር እንዲገዙ የመረጣቸውን 144,000 ሰዎች አስመልክቶ ምን ይላል?

      “ወደ ሰማይ የሚሄዱት እነማን ናቸው?” (ድረ ገጻችን ላይ የወጣ ርዕስ)

      እስር ቤት የነበረች አንዲት ሴት በዓለም ላይ ፍትሕ ሊያሰፍን የሚችለው አምላክ ብቻ ነው ብላ እንድታምን ያደረጋት ምንድን ነው?

      “የፍትሕ ጥያቄዬ መልስ ያገኘበት መንገድ” (ንቁ! ኅዳር 2011)

      a ከእነዚህ የሥነ ምግባር ደንቦች መካከል አንዳንዶቹ ክፍል 3 ላይ ይብራራሉ።

  • ገለልተኛ መሆን ማለት ምን ማለት ነው?
    ለዘላለም በደስታ ኑር!—አሳታፊ የመጽሐፍ ቅዱስ መማሪያ
    • ምዕራፍ 45. አንዲት እህት ብሔራዊ መዝሙር ሲዘመር አክብሮት በሚያሳይ መንገድ ቆማ፤ ሆኖም እንደ ሌሎቹ ተማሪዎች ብሔራዊ መዝሙር አልዘመረችም ወይም እጇን ደረቷ ላይ አላደረገችም

      ምዕራፍ 45

      ገለልተኛ መሆን ማለት ምን ማለት ነው?

      ኢየሱስ ተከታዮቹ “የዓለም ክፍል” መሆን እንደሌለባቸው አስተምሯል። (ዮሐንስ 15:19) ይህም ገለልተኛ መሆንን ማለትም በዓለም የፖለቲካ ጉዳዮችና ጦርነቶች ላይ የትኛውንም ወገን አለመደገፍን ይጨምራል። እንደ እውነቱ ከሆነ ገለልተኛ መሆን ቀላል የማይሆንበት ጊዜ አለ። በዚህ አቋማችን ምክንያት ሰዎች ሊያሾፉብን ይችላሉ። ታዲያ ምንጊዜም ገለልተኛ በመሆን ለይሖዋ አምላክ ታማኝ እንደሆንን ማሳየት የምንችለው እንዴት ነው?

      1. እውነተኛ ክርስቲያኖች ለዓለም መንግሥታት ምን አመለካከት አላቸው?

      ክርስቲያኖች መንግሥትን ያከብራሉ። ኢየሱስ እንዳለው ‘የቄሳር የሆነውን ለቄሳር ለመስጠት’ ማለትም የአገሪቱን ሕጎች ለመታዘዝ ጥረት እናደርጋለን፤ ለምሳሌ ቀረጥ እንድንከፍል የሚያዝዙ ሕጎችን እንጠብቃለን። (ማርቆስ 12:17) መጽሐፍ ቅዱስ የዓለም መንግሥታት እየገዙ ያሉት ይሖዋ እንዲገዙ ስለፈቀደላቸው እንደሆነ ያስተምራል። (ሮም 13:1) በመሆኑም መንግሥታት ያላቸው ሥልጣን ከአምላክ አንጻር ሲታይ አነስተኛ ወይም የተገደበ መሆኑን እንገነዘባለን። የሰው ልጆችን ችግሮች መፍታት የሚችለው አምላክና እሱ በሰማይ ያቋቋመው መንግሥት ብቻ እንደሆነ እናምናለን።

      2. ገለልተኛ መሆናችንን ማሳየት የምንችለው እንዴት ነው?

      ልክ እንደ ኢየሱስ ሁሉ እኛም ፖለቲካ ውስጥ አንገባም። ኢየሱስ ምድር ላይ ሳለ ሕዝቡ እሱ የፈጸመውን ተአምር አይተው ሊያነግሡት በሞከሩ ጊዜ ፈቃደኛ አልሆነም። (ዮሐንስ 6:15) ለምን? ምክንያቱም በኋላ ላይ እንደተናገረው ‘መንግሥቱ የዚህ ዓለም ክፍል አይደለም።’ (ዮሐንስ 18:36) እኛም የኢየሱስ ደቀ መዛሙርት እንደመሆናችን መጠን ገለልተኛ መሆናችንን በተለያዩ መንገዶች እናሳያለን። ለምሳሌ ያህል፣ በጦርነት አንካፈልም። (ሚክያስ 4:3⁠ን አንብብ።) እንደ ባንዲራ ያሉ ብሔራዊ ዓርማዎችን የምናከብር ቢሆንም ለአምላክ የምንሰጠውን ዓይነት ክብር አንሰጣቸውም። (1 ዮሐንስ 5:21) በተጨማሪም የትኛውንም የፖለቲካ ፓርቲ ወይም የፓርቲውን ዕጩ አንደግፍም ወይም አንቃወምም። በእነዚህና በሌሎች መንገዶች ለአምላክ መንግሥት ሙሉ በሙሉ ታማኝ እንደሆንን እናሳያለን።

      ጠለቅ ያለ ጥናት

      የገለልተኝነት አቋምን ሊፈትኑ የሚችሉ ሁኔታዎችን እንመለከታለን፤ በተጨማሪም ይሖዋን የሚያስደስቱ ውሳኔዎችን ማድረግ የምትችለው እንዴት እንደሆነ እንመረምራለን።

      የገለልተኝነት አቋሙን የጠበቀ አንድ ሰው። ተቀናቃኝ የፖለቲካ ፓርቲ ዕጩዎች ለሕዝቡ ለሚሰጡት ንግግር ምንም ትኩረት አይሰጥም

      3. እውነተኛ ክርስቲያኖች ገለልተኞች ናቸው

      ኢየሱስና ተከታዮቹ ጥሩ ምሳሌ ትተውልናል። ሮም 13:1, 5-7⁠ን እንዲሁም 1 ጴጥሮስ 2:13, 14⁠ን አንብቡ። ከዚያም ቪዲዮውን ተመልከቱና በሚከተሉት ጥያቄዎች ላይ ተወያዩ፦

      ቪዲዮ፦ እውነተኛ ክርስቲያኖች ገለልተኞች ናቸው—ክፍል 1 (4:28)

      • ባለሥልጣናትን ልናከብር የሚገባው ለምንድን ነው?

      • ለእነሱ እንደምንገዛ ማሳየት የምንችልባቸው አንዳንድ መንገዶች የትኞቹ ናቸው?

      በጦርነት ወቅት አንዳንድ አገሮች፣ ሁለቱንም ወገኖች እየደገፉ ገለልተኛ እንደሆኑ ይናገራሉ። በእርግጥ ገለልተኛ መሆን ማለት ምን ማለት ነው? ዮሐንስ 17:16⁠ን አንብቡ። ከዚያም ቪዲዮውን ተመልከቱና በሚከተለው ጥያቄ ላይ ተወያዩ፦

      ቪዲዮ፦ እውነተኛ ክርስቲያኖች ገለልተኞች ናቸው—ክፍል 2 (3:11)

      • ገለልተኛ መሆን ማለት ምን ማለት ነው?

      ባለሥልጣናት ከአምላክ ሕግ ጋር የሚጋጭ ነገር እንድናደርግ ቢጠይቁንስ? የሐዋርያት ሥራ 5:28, 29⁠ን አንብቡ። ከዚያም ቪዲዮውን ተመልከቱና በሚከተሉት ጥያቄዎች ላይ ተወያዩ፦

      ቪዲዮ፦ እውነተኛ ክርስቲያኖች ገለልተኞች ናቸው—ክፍል 3 (1:18)

      • ሰዎች ያወጡት ሕግ ከአምላክ ሕግ ጋር በሚጋጭበት ጊዜ የትኛውን ሕግ ልንታዘዝ ይገባል?

      • ክርስቲያኖች ለባለሥልጣናት የማይታዘዙባቸውን አንዳንድ ሁኔታዎች መጥቀስ ትችላለህ?

      4. በሐሳብም ሆነ በድርጊት ገለልተኛ ሁን

      አንደኛ ዮሐንስ 5:21⁠ን አንብቡ። ከዚያም ቪዲዮውን ተመልከቱና በሚከተሉት ጥያቄዎች ላይ ተወያዩ፦

      ቪዲዮ፦ እውነተኛ ክርስቲያኖች ድፍረት ያስፈልጋቸዋል—የገለልተኝነት አቋም ለመጠበቅ (2:49)

      • በቪዲዮው ላይ አዬንጌ የፖለቲካ ፓርቲ አባል ላለመሆን እንዲሁም ለባንዲራ ሰላምታ እንደመስጠት ባሉ ብሔራዊ ሥነ ሥርዓቶች ላለመካፈል የወሰነው ለምንድን ነው?

      • ያደረገው ውሳኔ ትክክል ይመስልሃል?

      የገለልተኝነት አቋማችንን ሊፈትኑ የሚችሉ ሌሎች ሁኔታዎች የትኞቹ ናቸው? ቪዲዮውን ተመልከቱ፤ ከዚያም በሚከተሉት ጥያቄዎች ላይ ተወያዩ፦

      ቪዲዮ፦ ከመጠበቂያ ግንብ የምናገኛቸው ትምህርቶች—በተከፋፈለ ዓለም ውስጥ የገለልተኝነት አቋማችሁን ጠብቁ (5:16)

      • የተለያዩ አገሮች የሚሳተፉበትን ስፖርታዊ እንቅስቃሴ ስንመለከት ገለልተኝነታችንን መጠበቅ የምንችለው እንዴት ነው?

      • ፖለቲከኞች የሚያደርጉት ውሳኔ እኛን የሚነካን በሚሆንበት ጊዜም እንኳ ገለልተኝነታችንን መጠበቅ የምንችለው እንዴት ነው?

      • የዜና ዘገባዎች ወይም አብረውን ጊዜ የሚያሳልፉ ሰዎች በገለልተኝነት አቋማችን ላይ ምን ተጽዕኖ ሊያሳድሩ ይችላሉ?

      1. ምልክቶች ይዘው የተቃውሞ ሰልፍ የወጡ የተበሳጩ ሰዎች 2. በስፖርት ውድድር ላይ ባንዲራ ይዞ ድጋፉን እየገለጸ ያለ ሰው 3. አንድ ተማሪ ብሔራዊ መዝሙር ሲዘምር 4. የጦር መሣሪያ የያዘ ወታደር 5. ሁለት የፖለቲካ ፓርቲ ዕጩዎች ሲከራከሩ 6. አንዲት ሴት ስትመርጥ

      ክርስቲያኖች በአስተሳሰብም ሆነ በድርጊት ገለልተኝነታቸውን መጠበቅ የሚኖርባቸው በየትኞቹ ሁኔታዎች ሥር ነው?

      አንድ ሰው እንዲህ ብሎ ቢጠይቅህስ? “ለባንዲራ ሰላምታ የማትሰጠው ወይም ብሔራዊ መዝሙር የማትዘምረው ለምንድን ነው?”

      • ምን ብለህ ትመልሳለህ?

      ማጠቃለያ

      ክርስቲያኖች በሐሳባቸው፣ በንግግራቸውና በድርጊታቸው ከፖለቲካ ጉዳዮች ገለልተኛ ለመሆን ከፍተኛ ጥረት ያደርጋሉ።

      ክለሳ

      • ለመንግሥታት ምን የማድረግ ግዴታ አለብን?

      • ከፖለቲካ ጉዳዮች ገለልተኛ መሆን ያለብን ለምንድን ነው?

      • የገለልተኝነት አቋማችንን ሊፈትኑ የሚችሉ ሁኔታዎች የትኞቹ ናቸው?

      ግብ

      ምርምር አድርግ

      የገለልተኝነት አቋማችንን ለመጠበቅ ስንል ምን መሥዋዕትነት መክፈል ሊያስፈልገን ይችላል?

      ይሖዋ ፈጽሞ አላሳፈረንም (3:14)

      ቤተሰቦች ገለልተኝነታቸውን ለሚፈትኑ ሁኔታዎች አስቀድመው መዘጋጀት የሚችሉት እንዴት ነው?

      በሕዝባዊ ዝግጅቶች ወቅት የገለልተኝነት አቋማችንን መጠበቅ (4:25)

      ለአገር ከመዋጋት በላይ ክብር የሚያስገኝ ነገር አለ የምንለው ለምንድን ነው?

      “በአምላክ ዘንድ ሁሉ ነገር ይቻላል” (5:19)

      ከሥራ ምርጫ ጋር የተያያዘ ውሳኔ ስታደርግ የዓለም ክፍል እንዳልሆንክ ማሳየት የምትችለው እንዴት ነው?

      “እያንዳንዱ የራሱን ሸክም ሊሸከም ይገባዋል” (መጠበቂያ ግንብ መጋቢት 15, 2006)

አማርኛ ጽሑፎች (1991-2025)
ውጣ
ግባ
  • አማርኛ
  • አጋራ
  • የግል ምርጫዎች
  • Copyright © 2025 Watch Tower Bible and Tract Society of Pennsylvania
  • የአጠቃቀም ውል
  • ሚስጥር የመጠበቅ ፖሊሲ
  • ሚስጥር የመጠበቅ ማስተካከያ
  • JW.ORG
  • ግባ
አጋራ