የመጠበቂያ ግንብ የኢንተርኔት ቤተ መጻሕፍት
መጠበቂያ ግንብ
የኢንተርኔት ቤተ መጻሕፍት
አማርኛ
፦
  • ፡
  • መጽሐፍ ቅዱስ
  • የሕትመት ውጤቶች
  • ስብሰባዎች
  • የአምላክ ጥበብ በፍጥረት ላይ ይንጸባረቃል
    መጠበቂያ ግንብ—2008 | ግንቦት 1
    • የአምላክ ጥበብ በፍጥረት ላይ ይንጸባረቃል

      “ከምድር እንስሳት ይልቅ የሚያስተምረን፣ ከሰማይ ወፎችም ይልቅ ጠቢባን የሚያደርገን፣ እርሱ [ነው]።”—ኢዮብ 35:11

      አእዋፍ አስገራሚ ችሎታ አላቸው። እነዚህ ፍጥረታት በቀላሉ በአየር ላይ መንሳፈፍ መቻላቸው የአውሮፕላን ንድፍ አውጪዎችን ያስደምማል። አንዳንድ የአእዋፍ ዝርያዎች አቅጣጫን ለመለየት የሚያስችል ምንም ምልክት የሌለውን ሰፊ ውቅያኖስ አቋርጠው ብዙ ሺህ ኪሎ ሜትሮች በመጓዝ የሚፈልጉበት ቦታ ይደርሳሉ።

      የፈጣሪያቸውን ጥበብ በግልጽ የሚያንጸባርቀው ሌላው የአእዋፍ አስደናቂ ችሎታ ደግሞ የተለያዩ ድምፆችን በማሰማትና በመዘመር መግባባት መቻላቸው ነው። እስቲ አንዳንድ ምሳሌዎችን እንመልከት።

      አእዋፍ የሚግባቡበት መንገድ

      አንዳንድ የአእዋፍ ዝርያዎች መግባባት የሚጀምሩት ገና ሳይፈለፈሉ ነው። ለአብነት ያህል፣ ክዌል የተባለች የቆቅ ዝርያ ለስምንት ቀን ያህል በየቀኑ አንድ አንድ እንቁላል ትጥላለች። እያንዳንዱ እንቁላል ቀኑን ጠብቆ ቢፈለፈል ሁሉም ጫጩቶች እኩል አይፈለፈሉም። ይህ ከሆነ ደግሞ እናቲቱ ያልተፈለፈሉትን እንቁላሎች መታቀፍና የተፈለፈሉትን ጫጩቶች መንከባከብ ስለሚጠበቅባት ሁኔታውን አስቸጋሪ ያደርግባታል። ይሁን እንጂ ስምንቱም እንቁላሎች የሚፈለፈሉት በስድስት ሰዓት ውስጥ ነው። ይህ እንዴት ሊሆን ይችላል? ተመራማሪዎች እንደሚሉት ከሆነ በዋነኝነት ከሚጠቀሱት ምክንያቶች አንዱ፣ ጫጩቶቹ ገና በእንቁላል ውስጥ እያሉ እርስ በርስ መግባባት መቻላቸው ነው።

      አእዋፍ ካደጉ በኋላ ብዙውን ጊዜ የሚዘምረው ወንዱ ነው። በተለይ ይህን የሚያደርገው በመራቢያው ወቅት ሲሆን የሚዘምረውም ክልሉን ለማስጠበቅ ወይም ተጓዳኙን ለመማረክ ነው። በሺህ የሚቆጠሩት የአእዋፍ ዝርያዎች እያንዳንዳቸው የራሳቸው “ቋንቋ” ያላቸው ሲሆን ይህ ደግሞ እንስቶቹ የራሳቸው ዝርያ የሆኑ ተጓዳኞችን ለማግኘት ያስችላቸዋል።

      ብዙውን ጊዜ አእዋፍ ማለዳ ላይና ጀንበር ስትጠልቅ የሚዘምሩበት በቂ ምክንያት አላቸው። በእነዚህ ጊዜያት አየሩ ጸጥ ያለ ሲሆን ጫጫታም አይሰማም። ማለዳ ላይ እንዲሁም ጀንበር ስትጠልቅ የሚሰማው የአእዋፍ ዝማሬ በቀኑ መሃል ከሚሰማው በ20 እጥፍ እንደሚበልጥ ተመራማሪዎች ይናገራሉ።

      አብዛኛውን ጊዜ የሚዘምሩት ወንዶቹ ቢሆኑም ሁለቱም ጾታዎች የተለያየ መልእክት የሚያስተላልፉ ድምፆችን ያሰማሉ። ለምሳሌ ያህል፣ ቻፊንች የተባለው የወፍ ዝርያ ዘጠኝ ዓይነት ድሞፆችን ማውጣት ይችላል። አደጋ ሊያስከትልባቸው የሚችል እንደ ነጣቂ ወፍ ያለ ነገር በአየር ላይ ሲያንዣብብ ሲመለከቱ የሚያሰሙት ድምፅ ከመሬት አደጋ ሲያጋጥማቸው ከሚያወጡት ድምፅ ይለያል።

      ከሁሉ የላቀ ስጦታ

      በእርግጥም፣ አእዋፍ በተፈጥሮ ያገኙት ጥበብ አስደናቂ ነው። ይሁንና እርስ በርስ በመግባባት ችሎታ ረገድ ሰዎችን የሚተካከላቸው የለም። ኢዮብ 35:11 አምላክ ሰዎችን “ከሰማይ ወፎችም ይልቅ ጠቢባን” አድርጎ እንደሠራቸው ይናገራል። ሰዎችን የተለየ የሚያደርጋቸው በድምፅ ወይም በምልክት ውስብስብ የሆኑ ሐሳቦችን መግለጽ መቻላቸው ነው።

      ከሌሎች ፍጥረታት በተለየ መልኩ የሰው ልጆች ውስብስብ ቋንቋዎችን የመማር ችሎታ ኖሯቸው ይወለዳሉ። አሜሪካን ሳይንቲስት የተባለ መጽሔት በኢንተርኔት ባስተላለፈው ዘገባ ላይ እንደሚከተለው ብሏል:- “ድክድክ የሚሉ ሕፃናት ወላጆቻቸው ሆን ብለው ባያስተምሯቸውም እንኳ መናገር ይችላሉ፤ ሌላው ቀርቶ መስማት የተሳናቸው ልጆች ቤታቸው ውስጥ የምልክት ቋንቋ የሚያስተምራቸው ሰው ባይኖርም የራሳቸውን የምልክት ቋንቋ ይፈጥራሉ።”

  • የአምላክ ጥበብ በፍጥረት ላይ ይንጸባረቃል
    መጠበቂያ ግንብ—2008 | ግንቦት 1
    • አንተስ ምን ይሰማሃል?

      ማራኪ የሆነ የወፍ ዝማሬ ስታደምጥ ወይም አንድ ሕፃን ልጅ አፍ መፍታት ሲጀምር ምን ይሰማሃል? በፍጥረታት ላይ የአምላክ ጥበብ መንጸባረቁን አስተውለሃል?

      መዝሙራዊው ዳዊት ስለ አፈጣጠሩ ካሰላሰለ በኋላ ወደ አምላክ እንዲህ በማለት ለመጸለይ ተገፋፍቷል:- “ግሩምና ድንቅ ሆኜ ተፈጥሬአለሁና አመሰግንሃለሁ፤ ሥራህ ድንቅ ነው፤ ነፍሴም ይህን በውል ተረድታለች።” (መዝሙር 139:14) በፍጥረት ላይ የተንጸባረቀውን የአምላክን ጥበብ በአድናቆት መመርመርህ ፈጣሪ አስተማማኝ መመሪያ በመስጠት ረገድ ከፍተኛ ችሎታ እንዳለው ይበልጥ እርግጠኛ እንድትሆን ያደርግሃል።

  • የአምላክ ኃይል በከዋክብት ላይ ይንጸባረቃል
    መጠበቂያ ግንብ—2008 | ግንቦት 1
    • የአምላክ ኃይል በከዋክብት ላይ ይንጸባረቃል

      “ዐይናችሁን አንሡ፤ ወደ ሰማይ ተመልከቱ፤ እነዚህን ሁሉ የፈጠረ ማን ነው? የከዋክብትን ሰራዊት አንድ በአንድ የሚያወጣቸው፣ በየስማቸው የሚጠራቸው እርሱ ነው። ከኀይሉ ታላቅነትና ከችሎታው ብርታት የተነሣ፣ አንዳቸውም አይጠፉም።”—ኢሳይያስ 40:26

      ፀሐያችን መካከለኛ መጠን ያላት ኮከብ ብትሆንም ከምድር 330,000 ጊዜ ትበልጣለች። በምድር አቅራቢያ የሚገኙት አብዛኞቹ ከዋክብት ከፀሐይ የሚያንሱ ናቸው። እንደ ቪ382 ሲግኒ ያሉ ሌሎች ከዋክብት ግን ፀሐያችንን ከ27 እጥፍ በላይ ይበልጧታል።

      ፀሐያችን ምን ያህል ኃይል ታመነጫለች? እሳት ከሚነድበት አንድ አካባቢ 100 ኪሎ ሜትር ርቀት ላይ የምትገኝ ብትሆንና ሙቀቱ ቢሰማህ፣ እሳቱ ምን ያህል ኃይለኛ እንደሆነ መገመት አያዳግትህም። ፀሐይ ከምድር በአማካይ 150 ሚሊዮን ኪሎ ሜትር ርቃ ትገኛለች። ይሁን እንጂ አንዳንድ ጊዜ ፀሐይዋ ልታቃጥለን ትችላለች! በጣም የሚገርመው ነገር ፀሐይ ከምታመነጨው ኃይል ውስጥ ወደ ምድር የሚደርሰው ከሁለት ቢሊዮን አንድ እጅ ያህሉ ብቻ ነው። እንደዛም ሆኖ ይህ ኃይል በምድር ያሉትን ፍጥረታት በሕይወት ለማቆየት በቂ ነው።

      እንዲያውም የፀሐይ ኃይል እንደ ምድር ያሉ 31 ትሪሊዮን ፕላኔቶች ቢኖሩ በሁሉም ውስጥ ያሉትን ፍጥረታት በሕይወት ለማቆየት እንደሚያስችል የሳይንስ ሊቃውንት ይናገራሉ። ወይም በሌላ አነጋገር የፀሐይን ኃይል ለአንድ ሴኮንድ ብቻ ማጠራቀም ቢቻል ዩናይትድ ስቴትስ ይህን ኃይል “አሁን ባላት ፍጆታ ለ9,000,000 ዓመታት ያህል ልትጠቀምበት ትችላለች” በማለት የስፔስ ዌዘር ፕሬዲክሽን ሴንተር ድረ ገጽ ይናገራል።

      የፀሐይ ኃይል የሚመነጨው አቶሞች እንዲሰባበሩ በማድረግ ከፍተኛ ኃይል እንዲፈጠር የሚያደርገው የኑክሌር ማብለያ ከሚገኝበት ከፀሐይዋ እምብርት ውስጥ ነው። ፀሐይ በጣም ግዙፍ ስትሆን ውስጠኛው ክፍሏ ደግሞ ጥቅጥቅ ያለ ነው፤ በመሆኑም በውስጠኛው ክፍል የሚፈጠረው ኃይል ወደ ላይኛው የፀሐይ ክፍል ለመድረስ በሚሊዮን የሚቆጠሩ ዓመታት ይፈጅበታል። ስፔስ ዌዘር ፕሬዲክሽን ሴንተር በድረ ገጹ ላይ እንደገለጸው “ፀሐይ አሁን ኃይል ማመንጨቷን ብታቆም በምድር ላይ ጉልህ ለውጥ ለመታየት 50,000,000 ዓመታት ሊወስድ ይችላል!”

      እስቲ ይህንን ሐቅ ተመልከት:- ምሽት ላይ ቀና ብለህ ስትመለከት በጠራው ሰማይ ላይ እንደ ፀሐይ ከፍተኛ መጠን ያለው ኃይል የሚያመነጩ በሺዎች የሚቆጠሩ ከዋክብት ታያለህ። የሳይንስ ሊቃውንት ደግሞ በጽንፈ ዓለም ውስጥ በቢሊዮኖች የሚቆጠሩ ከዋክብት እንዳሉ ያምናሉ!

      እነዚህ ሁሉ ከዋክብት እንዴት ተገኙ? ምክንያቱን መረዳት ባይችሉም አብዛኞቹ ተመራማሪዎች ጽንፈ ዓለም ከዛሬ 14 ቢሊዮን ዓመታት ገደማ በፊት በድንገት ወደ ሕልውና መምጣቱን ያምናሉ። መጽሐፍ ቅዱስ “በመጀመሪያ እግዚአብሔር ሰማያትንና ምድርን ፈጠረ” በማለት ይናገራል። (ዘፍጥረት 1:1) ከፍተኛ ኃይል የሚያመነጩ ከዋክብትን የፈጠረው አካል ‘ብርቱ ችሎታ ያለው’ ተብሎ መጠራቱ ምንም አያስደንቅም።—ኢሳይያስ 40:26

አማርኛ ጽሑፎች (1991-2025)
ውጣ
ግባ
  • አማርኛ
  • አጋራ
  • የግል ምርጫዎች
  • Copyright © 2025 Watch Tower Bible and Tract Society of Pennsylvania
  • የአጠቃቀም ውል
  • ሚስጥር የመጠበቅ ፖሊሲ
  • ሚስጥር የመጠበቅ ማስተካከያ
  • JW.ORG
  • ግባ
አጋራ