-
ከሚያምኑት ወገን እንሁንመጠበቂያ ግንብ—1999 | ታኅሣሥ 15
-
-
16, 17. (ሀ) ጳውሎስ ለአገልግሎቱ ድፍረት ያገኘው እንዴት ነው? (ለ) በአንዱ የክርስቲያናዊ አገልግሎት ዘርፍ መካፈል የሚያስፈራን ከሆነ ምን እርምጃዎች መውሰድ ይኖርብናል?
16 ጳውሎስ በተሰሎንቄ ለሚገኙ ክርስቲያኖች እንደሚከተለው ሲል ጽፎላቸዋል:- “እንደምታውቁት በፊልጵስዩስ አስቀድመን መከራ ተቀብለን ተንገላትተንም፣ በብዙ ገድል የእግዚአብሔርን ወንጌል ለእናንተ እንናገር ዘንድ በአምላካችን ደፈርን።” (1 ተሰሎንቄ 2:2) ጳውሎስና ጓደኞቹ በፊልጵስዩስ ‘የተንገላቱት’ እንዴት ነበር? አንዳንድ ሃይማኖታዊ ምሁራን እንደሚሉት ጳውሎስ የተጠቀመበት ግሪክኛ ቃል መሰደብን፣ መዋረድን ወይም ለሥቃይ መዳረግን ያመለክታል። በፊልጵስዩስ የሚገኙ ባለሥልጣናት በዱላ ደብድበዋቸዋል፣ ወኅኒ ቤት ጨምረዋቸዋል እንዲሁም በእግር ግንድ ውስጥ አስገብተው አስረዋቸዋል። (ሥራ 16:16-24) ጳውሎስ ይህ ሁሉ ስቃይ ሲደርስበት ምን ተሰማው? ፍርሃት፣ በሁለተኛ ሚስዮናዊ ጉዞው ቀጥሎ ከሚጎበኛቸው ከተማዎች አንዷ ወደሆነችው ወደ ተሰሎንቄ እንዳይሄድ አድርጎታልን? በፍጹም፣ እንዲያውም ይበልጥ ‘ደፋር’ ሆኗል። ፍርሃትን በማሸነፍ በድፍረት መስበኩን ቀጥሏል።
17 ጳውሎስ ይህን ድፍረት ያገኘው ከየት ነው? ከራሱ? በፍጹም፤ “በአምላካችን” ደፈርን ሲል ተናግሯል። ለመጽሐፍ ቅዱስ ተርጓሚዎች የተዘጋጀ አንድ የማመሳከሪያ ጽሑፍ ይህ አባባል “አምላክ ፍርሃትን ከልባችን ውስጥ አውጥቶ ጣለልን” ተብሎም ሊተረጎም እንደሚችል ይገልጻል። በተለይ አገልግሎት ሲባል የሚያስፈራህ ከሆነ ወይም ደግሞ በተወሰኑ የአገልግሎቱ ዘርፎች ለመካፈል ድፍረቱ ከሌለህ ተመሳሳይ እርዳታ ለማግኘት ለምን ይሖዋን አትማጸነውም? ፍርሃትን ከልብህ ውስጥ አውጥቶ እንዲጥልልህ ጠይቀው። ለሥራው ድፍረትን እንዲሰጥህ ጠይቀው። በተጨማሪም አንዳንድ ሌሎች እርምጃዎችን ውሰድ። አንተን በሚያስፈራህ የአገልግሎቱ ዘርፍ በመካፈል ልምድ ካለው ሰው ጋር ለመሥራት ዝግጅት አድርግ። ይህም በንግድ አካባቢዎች ማገልገልን፣ መንገድ ላይ መመሥከርን፣ መደበኛ ባልሆነ መንገድ መስበክን ወይም በስልክ መመሥከርን የሚመለከት ሊሆን ይችላል። መጀመሪያ ላይ ምናልባት የአገልግሎት ጓደኛህ ቀዳሚ ለመሆን ፈቃደኛ ሊሆን ይችላል። ከሆነ እሱን በማየት መማር ትችላለህ። ሆኖም ከዚያ በኋላ ራስህ ለመሞከር አንድትችል ድፍረት ማግኘት አለብህ።
18. በአገልግሎታችን ደፋሮች ከሆንን ምን በረከቶችን እናገኛለን?
18 ድፍረት ካገኘህ ምን ውጤት ሊገኝ እንደሚችል አስብ። ተስፋ ሳትቆርጥ ከጸናህ እውነትን ለሌሎች በማካፈል ረገድ ከዚህ በፊት ያላገኘሃቸውን ጥሩ ጥሩ ተሞክሮዎች ልታገኝ እንደምትችል የታወቀ ነው። (ገጽ 25ን ተመልከት።) ለአንተ አስቸጋሪ የሆነ ነገር በመሥራት ይሖዋን እያስደሰትከው እንዳለህ በማወቅ እርካታ ልታገኝ ትችላላችሁ። ፍርሃትህን በማሸነፍ ረገድ የይሖዋ በረከትና ድጋፍ አይለይህም። እምነትህ ጠንካራ ይሆናል። የራስህን እምነት ሳትገነባ የሌሎችን እምነት እገነባለሁ ማለት ዘበት ነው።—ይሁዳ 20, 21
-
-
ድፍረት አግኝተዋልመጠበቂያ ግንብ—1999 | ታኅሣሥ 15
-
-
ድፍረት አግኝተዋል
ለመስበክ ድፍረት ማግኘት ሁልጊዜ ቀላል ላይሆን ይችላል። እንዲያውም ሐዋርያው ጳውሎስ በአንድ ወቅት “በብዙ ገድል” እንደሰበከ ተናግሯል። (1 ተሰሎንቄ 2:2) ለመስበክ ‘መጋደል’ የሚክስ ነውን? ሁልጊዜ አስደናቂ ተሞክሮዎችን እናገኛለን ማለት ላይሆን ይችላል፤ ሆኖም የአምላክ አገልጋዮች በድፍረት በመስበካቸው ደስታ አግኝተዋል። አንዳንድ ምሳሌዎችን ተመልከት።
ታር የምትባል አንዲት የስምንት ዓመት ልጅ አስተማሪዋ በሁለተኛው የዓለም ጦርነት ወቅት ማጎሪያ ካምፕ ውስጥ የታሰሩ አይሁዶች መለያ ምልክት እንዲሆን ቢጫ ቀለም ያለው የዳዊት ኮከብ በልብሳቸው ላይ ይሰፋላቸው እንደነበር ስትናገር በትኩረት ትከታተል ነበር። ታር ልናገር አልናገር ብላ አመነታች። “ዓይኔን ሳልጨፍን ጸለይኩ” በማለት ታስታውሳለች። ከዚያም እጅዋን አውጥታ በእነዚያ ካምፖች ውስጥ የይሖዋ ምሥክሮችም እንደነበሩና የወይን ጠጅ ቀለም ያለው ባለ ሦስት ማዕዘን ምልክት ልብሳቸው ላይ ይሰፋላቸው እንደነበር ተናገረች። አስተማሪዋም ተደሰተችና አመሰገነቻት። ታር የሰጠችው ሐሳብ ከአስተማሪዋ ጋር ተጨማሪ ውይይት ለማድረግ መንገድ ከፈተ። እንዲያውም በኋላ አስተማሪዋ የይሖዋ ምሥክሮች የናዚን ጥቃት በጽናት ተቋቁመዋል የተባለውን የቪዲዮ ካሴት ጠቅላላ የክፍሏ ተማሪዎች እንዲያዩት አደረገች።
በምዕራብ አፍሪካዊቷ አገር በጊኒ የምትኖር ኢረን የምትባል አንዲት ወጣት ያልተጠመቀች አስፋፊ አገልግሎቷን ለማሻሻል ፈለገች። ኢረንን መጽሐፍ ቅዱስ የምታስጠናት ሚስዮናዊት እህት ኢረን በትምህርት ቤቷ ላሉ ተማሪዎች የመጠበቂያ ግንብ እና የንቁ! መጽሔቶችን ለማበርከት እንድትሞክር አበረታታቻት። የክፍሏ ተማሪዎች ተቀባይ ስላልሆኑ ኢረን ይህን ማድረጉ ያስፈራት ነበር። ሆኖም ሚስዮናዊቷ እህት በምትሰጣት ማበረታቻ በመደፋፈር ኢረን በመጀመሪያ ከሁሉም ይበልጥ ተቃዋሚ ትመስላት ለነበረችው ተማሪ ለማበርከት ወሰነች። የሚያስገርመው ግን ተማሪዋ ፍላጎት ከማሳየቷም በላይ መጽሔቶችን በጉጉት ተቀበለች። ሌሎች ተማሪዎችም መጽሔቶችን ወሰዱ። ኢረን በዚያ ወር ያበረከተችው የመጽሔት ብዛት ባለፉት አምስት ወራት ካበረከተቻቸው መጽሔቶች የሚበልጥ ነበር።
በትሪንዳድ የሚገኝ አንድ ሽማግሌ ለአንዲት የትምህርት ቤት አስተዳዳሪ ንቁ! ትምህርታዊ መጽሔት መሆኑን ለመንገር ፈራ ተባ ይል ነበር። ሆኖም አንድ ቀን ድፍረት አገኘ። “ወደ ቅጥር ግቢው ስገባ ጸለይኩ። የትምህርት ቤቱ አስተዳዳሪ በጣም ጥሩ ሰው ሆና ሳገኛት ማመን አቃተኝ” ሲል ተናግሯል። “ዛሬ ያሉ ወጣቶች ምን ተስፋ አላቸው?” የተባለውን ንቁ! መጽሔት ወሰደች፤ እንዲያውም በክፍል ውስጥ ለማስተማሪያነት እንዲያገለግል ተስማማች። ከዚያን ወዲህ በተለያዩ ርዕሶች የወጡ 40 መጽሔቶችን ወስዳለች።
ወጣቱ ቮን መስበክ በጣም ያስፈራው ነበር። “በጣም እረበሻለሁ፣ ውስጥ እጄን ያልበኛል፣ ቀስ ብዬ መናገር ስለማልችል በጣም እፈጥናለሁ።” ያም ሆኖ ግን የሙሉ ጊዜ አገልጋይ ሆነ። አሁንም ቢሆን በድፍረት መናገር ያስቸግረው ነበር። አንድ ቀን ሥራ ፍለጋ ሲባዝን ውሎ ሳይሳካለት ይቀራል። “እንዲያው በዚህ እንኳ ብካስ” ብሎ በማሰብ ባቡር ላይ ለአንድ ሰው ለመመሥከር ያስባል። ሆኖም ባቡሩ ውስጥ ያሉትን ትላልቅ የንግድ ሰዎች ያይና መናገር ይፈራል። በመጨረሻም እንደምንም ብሎ ጎኑ የተቀመጡትን አንድ ትልቅ ሰው ማነጋገር ይጀምራል። ከዚያም ረዥም ውይይት አደረጉ። “ከወጣት የማይጠበቁ ጥሩ ጥሩ ጥያቄዎችን ትጠይቃለህ። የሃይማኖት ምሁር ነህ እንዴ?” ሲል አንዱ ነጋዴ ጠየቀው። ቮን “አይ፣ የሃይማኖት ምሁር እንኳን አይደለሁም። እኔ የይሖዋ ምሥክር ነኝ” ሲል መለሰ። ሰውዬውም ፈገግ በማለት “አሃ፣ አሁን ገባኝ” አለ።
እነዚህም ሆኑ ሌሎች በርካታ ምሥክሮች ለመመሥከር የሚያስችል ድፍረት በማግኘታቸው ደስተኞች ናቸው። አንተስ እንዲህ ማድረግ ትችላለህ?
-