-
ደግነት—በአምላክ ዘንድ ውድ የሆነ ባሕርይመጠበቂያ ግንብ—2012 | መስከረም 1
-
-
ደግነት የሰው ተፈጥሯዊ ባሕርይ ከመሆኑም በላይ በአምላክ ዘንድ ከፍ ተደርጎ የሚታይ ነገር ነው፤ ስለሆነም አምላክ “አንዳችሁ ለሌላው ደጎችና ከአንጀት የምትራሩ ሁኑ” ብሎ መናገሩ ምክንያታዊ ነው። (ኤፌሶን 4:32) በተጨማሪም “እንግዳ ተቀባይ መሆንን አትርሱ” የሚለው ማሳሰቢያ ለማናውቃቸው ሰዎችም ደግነት እንድናሳይ ያበረታታናል።—ዕብራውያን 13:2
-
-
ደግነት—በአምላክ ዘንድ ውድ የሆነ ባሕርይመጠበቂያ ግንብ—2012 | መስከረም 1
-
-
ሐዋርያው ጳውሎስ፣ ለማናውቃቸው ሰዎች ደግነት ስለ ማሳየት ከተናገረ በኋላ “አንዳንዶች ይህን ሲያደርጉ ሳያውቁት መላእክትን አስተናግደዋል” ማለቱ ትኩረት የሚስብ ነው። መላእክትን የማስተናገድ አጋጣሚ ብታገኝ ምን ሊሰማህ እንደሚችል አስበው! ይሁን እንጂ፣ ጳውሎስ አንዳንዶች መልእክትን ያስተናገዱት “ሳያውቁት” እንደሆነ ተናግሯል። በመሆኑም ጳውሎስ የተናገረው ሐሳብ፣ እንግዶችን ማለትም የማናውቃቸውን ሰዎች ጨምሮ ለሌሎች ደግነት የማሳየት ልማድ ካለን ባልጠበቅነው መንገድ ወሮታ ልናገኝ እንደምንችል ያሳያል።
አብዛኞቹ ማጣቀሻ ያላቸው የመጽሐፍ ቅዱስ ትርጉሞች ጳውሎስ የተናገረውን ሐሳብ በዘፍጥረት ምዕራፍ 18 እና 19 ላይ ከሰፈሩት ስለ አብርሃምና ስለ ሎጥ ከሚገልጹ ዘገባዎች ጋር ያያይዟቸዋል። በእነዚህ ዘገባዎች ላይ አስፈላጊ የሆኑ መልእክቶችን የያዙ መላእክት፣ እንግዶች መስለው ተገልጠው እንደነበር እናነባለን። ወደ አብርሃም የመጡት መላእክት የያዙት መልእክት አምላክ ልጅ እንደሚሰጠው ለአብርሃም የገባውን ቃል እንደሚፈጽምለት የሚገልጽ ሲሆን ለሎጥ የደረሰው መልእክት ደግሞ ሰዶምና ገሞራ በሚባሉት ከተሞች ላይ ከሚመጣው ጥፋት መዳን ስለሚያገኝበት መንገድ የሚገልጽ ነበር።—ዘፍጥረት 18:1-10፤ 19:1-3, 15-17
ከላይ ያሉትን ጥቅሶች ስታነብ አብርሃምም ሆነ ሎጥ ደግነት ያሳዩት ለማያውቋቸው መንገደኞች እንደነበረ ትገነዘባለህ። እርግጥ ነው፣ በጥንት ዘመን መንገደኛን በእንግድነት መቀበል እንደ ጥሩ ባሕል ይታይ ነበር፤ መንገደኛው ወዳጅ ዘመድም ሆነ ለአገሩ እንግዳ የሆነ ሰው፣ እንዲህ ዓይነት መስተንግዶ ይደረግለት ነበር። እንዲያውም የሙሴ ሕግ እስራኤላውያን በምድራቸው የሚኖሩ የባዕድ አገር ሰዎች የሚያስፈልጓቸውን መሠረታዊ ነገሮች በመስጠት ረገድ ንፉግ እንዳይሆኑ ያዝዝ ነበር። (ዘዳግም 10:17-19) አብርሃምና ሎጥ ግን ከጊዜ በኋላ በሕጉ ውስጥ የተካተተው ይህ ትእዛዝ ከሚጠይቀው የበለጠ ነገርም አድርገዋል። ለእንግዶች ደግነት ለማሳየት ለየት ያለ ጥረት ያደረጉ ሲሆን እንዲህ በማድረጋቸውም ተባርከዋል።
አብርሃም ደግነት በማሳየቱ በእጅጉ ተክሷል
አብርሃም ያሳየው ደግነት ልጅ እንዲያገኝ አስችሎታል፤ ይሁንና ይህ ለእሱ ብቻ ሳይሆን ለእኛም በረከት አስገኝቷል። እንደዚህ የምንለው ለምንድን ነው? አብርሃምና ልጁ ይስሐቅ በአምላክ ዓላማ አፈጻጸም ረገድ ወሳኝ ሚና ተጫውተዋል። እነዚህ ሰዎች መሲሑ ኢየሱስ በተገኘበት የዘር ሐረግ ውስጥ ቁልፍ የሆነ ቦታ ነበራቸው። በተጨማሪም አብርሃምና ይስሐቅ በእምነት ተነሳስተው ያደረጉት ነገር አምላክ በፍቅሩና በጸጋው የሰው ልጆች መዳን የሚያገኙበትን መንገድ የሚያዘጋጀው እንዴት እንደሚሆን የሚያሳይ ጥላ ሆኖ አገልግሏል።—ዘፍጥረት 22:1-18፤ ማቴዎስ 1:1, 2፤ ዮሐንስ 3:16
-