የመጠበቂያ ግንብ የኢንተርኔት ቤተ መጻሕፍት
መጠበቂያ ግንብ
የኢንተርኔት ቤተ መጻሕፍት
አማርኛ
፦
  • ፡
  • መጽሐፍ ቅዱስ
  • የሕትመት ውጤቶች
  • ስብሰባዎች
  • የፍቅር ጓደኝነት ለመመሥረት ደርሻለሁ?
    ወጣቶች የሚጠይቋቸው ጥያቄዎችና ተግባራዊ መሆን የሚችሉ መልሶች፣ ጥራዝ 2
    • ምዕራፍ 1

      የፍቅር ጓደኝነት ለመመሥረት ደርሻለሁ?

      “የወንድ ጓደኛ እንድይዝ ከየአቅጣጫው ከፍተኛ ግፊት ይደረግብኛል። በዚህ ላይ ደግሞ ቆንጆ የሆኑ ወንዶች ሞልተዋል።”​—ዊትኒ

      “አንዳንዶቹ ሴቶች ዓይን አውጥተው ይጠይቁኛል፤ በዚህ ጊዜ እሺ ለማለት ይቃጣኛል። ሆኖም ወላጆቼን ብጠይቃቸው እንደማይፈቅዱልኝ አውቃለሁ።”​—ፊሊፕ

      ከምትወዳትና እሷም ለአንተ የተለየ የፍቅር ስሜት ካላት ወጣት ጋር አብረህ ጊዜ የማሳለፍ ከፍተኛ ፍላጎት ይኖርህ ይሆናል፤ እንዲህ ዓይነቱ ስሜት ገና በልጅነትህም እንኳ ሊያድርብህ ይችላል። ጄኒፈር “ሌሎች ልጆች የፍቅር ጓደኛ ይዘው ስመለከት እኔም ገና በ11 ዓመቴ የወንድ ጓደኛ የመያዝ ፍላጎት አድሮብኝ ነበር” በማለት ታስታውሳለች። ብሪትኒ ደግሞ “ግለሰቡ ማንም ይሁን ማን በትምህርት ቤት አንድ የፍቅር ጓደኛ ካልያዛችሁ የሆነ ችግር እንዳለባችሁ ይሰማችኋል” ብላለች።

      አንተስ? የፍቅር ጓደኛ ለመያዝ ደርሰሃል? ለዚህ ጥያቄ መልስ ለማግኘት በቅድሚያ ልናነሳው የሚገባ መሠረታዊ የሆነ ጥያቄ አለ፦

      “የፍቅር ጓደኝነት” ሲባል ምን ማለት ነው?

      ለሚከተሉት ጥያቄዎች መልስ የምትለው ላይ ምልክት አድርግ፦

      ከአንዲት ወጣት ጋር በተደጋጋሚ ጊዜ እየተገናኛችሁ ትጫወታላችሁ። የፍቅር ጓደኝነት ጀምረሃል ማለት ይቻላል?

      □ አዎ

      □ አይ

      ደስ የምትልህ አንዲት ወጣት አለች፤ እሷም ለአንተ ልዩ ስሜት አላት። በቀን ውስጥ ብዙ ጊዜ በሞባይል መልእክት ትላላካላችሁ አሊያም በስልክ ታወራላችሁ። የፍቅር ጓደኝነት ጀምረሃል ማለት ይቻላል?

      □ አዎ

      □ አይ

      ከጓደኞችህ ጋር ጊዜ ስታሳልፍ ሁልጊዜ ከአንዲት ወጣት ጋር ነጠል ብለህ ታወራለህ። የፍቅር ጓደኝነት ጀምረሃል ማለት ይቻላል?

      □ አዎ

      □ አይ

      የመጀመሪያውን ጥያቄ ለመመለስ ብዙም እንደማትቸገር ግልጽ ነው። ይሁን እንጂ ሁለተኛውንና ሦስተኛውን ጥያቄ ለመመለስ አመንትተህ ይሆናል። ለመሆኑ “የፍቅር ጓደኝነት” ሲባል ምን ማለት ነው? ለአንዲት ወጣት የፍቅር ስሜት ካለህና እሷም እንደ አንተ የሚሰማት ከሆነ የምትገናኙበት መንገድ ምንም ይሁን ምን በመካከላችሁ መፈላለጉ እስካለ ድረስ የፍቅር ጓደኝነት ጀምራችኋል ሊባል ይችላል። በመሆኑም ከላይ የቀረቡት የሦስቱም ጥያቄዎች መልስ አዎ የሚለው ነው። አንተና አንዲት ወጣት አንዳችሁ ለሌላው የፍቅር ስሜት ካላችሁና በየጊዜው የምታወሩ ከሆነ የምትገናኙት በስልክም ይሁን በአካል ወይም ደግሞ በግልጽም ይሁን በድብቅ የፍቅር ጓደኝነት ጀምራችኋል ማለት ነው። ይህን ለማድረግ ዝግጁ ነህ? ሦስት ጥያቄዎችን መመርመራችን መልሱን ለማግኘት ይረዳሃል።

      የፍቅር ጓደኝነት መመሥረት የምትፈልገው ለምንድን ነው?

      በብዙ ባሕሎች ውስጥ አንድ ወንድና አንዲት ሴት የፍቅር ጓደኝነት መመሥረታቸው በሚገባ ለመተዋወቅ እንደሚያስችላቸው ጥሩ አጋጣሚ ተደርጎ ይታያል። ይሁን እንጂ የፍቅር ጓደኝነት የሚመሠረትበት ዓላማ ክብር ያለው መሆን ይኖርበታል፤ ዓላማው አንድ ወንድና አንዲት ሴት በትዳር መጣመር ይችሉ እንደሆነና እንዳልሆነ ለመወሰን የሚያስችል አጋጣሚ መፍጠር ሊሆን ይገባል።

      እርግጥ ነው፣ አንዳንድ እኩዮችህ የፍቅር ጓደኝነት መመሥረትን በቁም ነገር አይመለከቱት ይሆናል። ምናልባትም ምንም የጋብቻ እቅድ ሳይኖራቸው ተቃራኒ ፆታ ካለው አንድ ግለሰብ ጋር ልዩ ቅርርብ መፍጠር ያስደስታቸው ይሆናል። እንዲያውም አንዳንዶች እንዲህ ዓይነት ጓደኝነት የሚመሠርቱት ተፈላጊ መሆናቸውን ለማሳየት ሊሆን ይችላል፤ አሊያም ከተቃራኒ ፆታ ጋር አብረው መታየቱን እንደ ጀብዱ ይቆጥሩት ይሆናል። ይሁንና ይህ ዓይነቱ ጓደኝነት አብዛኛውን ጊዜ በአጭሩ ይቀጫል። ሄዘር የተባለች አንዲት ወጣት “የፍቅር ጓደኝነት የመሠረቱ ብዙ ወጣቶች በአንድ ወይም በሁለት ሳምንት ጊዜ ውስጥ ይለያያሉ” በማለት ተናግራለች። አክላም እንዲህ ብላለች፦ “እነዚህ ወጣቶች የፍቅር ጓደኝነትን የሚመለከቱት ጊዜያዊ እንደሆነ አድርገው ነው፤ በመሆኑም እንዲህ ያለው ግንኙነት ለፍቺ እንጂ ለትዳር ሕይወት አያዘጋጃቸውም።”

      ከአንዲት ወጣት ጋር የፍቅር ጓደኝነት ስትጀምር ስሜቷን ግምት ውስጥ ማስገባት ይኖርብሃል። ዓላማህ ጤናማ ሊሆን ይገባል። እስቲ አስበው፦ አንድ ልጅ አሻንጉሊቱን ሲፈልግ እያነሳ እንደሚጫወትበትና ሲሰለቸው ደግሞ እንደሚጥለው ሁሉ አንድ ሰውም በስሜትህ እንዲጫወት ትፈልጋለህ? ቼልሲ የተባለች ወጣት እንዲህ ብላለች፦ “የፍቅር ጓደኝነት የሚመሠረተው ደስ የሚል ስሜት ስለሚፈጥር ብቻ እንደሆነ የሚሰማኝ ጊዜ አለ። ይሁን እንጂ አንደኛው ወገን ጓደኝነቱን በቁም ነገር እየተመለከተው ሌላኛው እንደ ዋዛ የሚያየው ከሆነ እንዲህ ዓይነቱ ግንኙነት የደስታ ስሜት ይፈጥራል ብሎ ማሰብ ከባድ ነው።”

      ለመሆኑ ዕድሜህ ስንት ነው?

      ወጣቶች በስንት ዓመታቸው የፍቅር ጓደኝነት ቢጀምሩ ጥሩ ነው ትላለህ? ․․․․․

      ይህንኑ ጥያቄ ለወላጆችህ ካቀረብክላቸው በኋላ የሚሰጡህን መልስ ጻፍ። ․․․․․

      አንተ የጻፍከው ዕድሜ ወላጆችህ ከነገሩህ ያነሰ እንደሚሆን መገመት ይቻላል። በእርግጥ ላያንስም ይችላል። የማያንስ ከሆነ፣ ትክክለኛ ፍላጎታቸውን በደንብ የሚያውቁበት ዕድሜ ላይ እስኪደርሱ ድረስ የፍቅር ጓደኝነት ከመመሥረት በመቆጠብ አስተዋይነት የሚንጸባረቅበት ውሳኔ ካደረጉት በርካታ ወጣቶች አንዱ ነህ ማለት ነው። የ17 ዓመቷ ዳንየል እንዲህ ዓይነት ውሳኔ አድርጋለች። እንዲህ ብላለች፦ “ከሁለት ዓመት በፊት የነበረኝን አመለካከት መለስ ብዬ ሳስበው የትዳር ጓደኛዬ እንዲሆን ከምፈልገው ሰው እጠብቀው የነበረው ነገር አሁን ከምፈልገው በጣም የተለየ ነው። በመሠረቱ አሁንም እንኳ እንዲህ ዓይነቱን ውሳኔ ማድረግ እችላለሁ ብዬ በራሴ አልተማመንም። ለተወሰኑ ዓመታት ራሴን ከፈተሽኩ በኋላ የሰከነ አቋም እንዳለኝ እርግጠኛ ስሆን ያን ጊዜ የፍቅር ጓደኝነት ስለ መመሥረት ማሰብ እጀምራለሁ።”

      የፍቅር ጓደኝነት ለመመሥረት አለመጣደፍ የጥበብ እርምጃ ነው የምንልበት ሌላም ምክንያት አለ። መጽሐፍ ቅዱስ፣ የፆታ ፍላጎትና የፍቅር ስሜት የሚያይልበትን ጊዜ ለማመልከት “አፍላ የጉርምስና ዕድሜ” የሚለውን ሐረግ ይጠቀማል። (1 ቆሮንቶስ 7:36) ‘በአፍላ የጉርምስና ዕድሜ’ ላይ እያለህ ከአንዲት ወጣት ጋር ልዩ ቅርርብ መፍጠርህ የፆታ ስሜትህን ይበልጥ ሊያቀጣጥለውና መጥፎ ድርጊት ወደ መፈጸም ሊመራህ ይችላል። እርግጥ ለእኩዮችህ ይህ ምንም ማለት ላይሆን ይችላል። አብዛኞቹ የፆታ ግንኙነት የመፈጸም ከፍተኛ ፍላጎት አላቸው። አንተ ግን እንዲህ ዓይነቱ አመለካከት ተጽዕኖ እንዳያሳድርብህ ማድረግ ትችላለህ። (ሮም 12:2) መጽሐፍ ቅዱስ ‘የፆታ ብልግና ከመፈጸም እንድትርቅ’ ያሳስብሃል። (1 ቆሮንቶስ 6:18 ኒው ኢንተርናሽናል ቨርዥን) ‘አፍላ የጉርምስና ዕድሜህ’ እስኪያልፍ ድረስ የፍቅር ጓደኝነት ከመመሥረት በመቆጠብ ‘ክፉ ነገርን ማስወገድ’ ትችላለህ።​—መክብብ 11:10

      ለማግባት ዝግጁ ነህ?

      ይህንን ጥያቄ ለመመለስ እንድትችል ከዚህ በታች ከተዘረዘሩት ነጥቦች አኳያ ራስህን በጥንቃቄ መርምር፦

      ከሌሎች ጋር ያለህ ግንኙነት፦ ከወላጆችህ ብሎም ከወንድሞችህና ከእህቶችህ ጋር ያለህ ግንኙነት ምን ይመስላል? ብዙ ጊዜ ከእነሱ ጋር ስትነጋገር ከቁጥጥር ውጭ ትሆናለህ? ምናልባትም ስሜትህን ለመግለጽ ሻካራ ቃል ወይም የሽሙጥ አነጋገር ትጠቀማለህ? በዚህ ረገድ እነሱ ስለ አንተ ምን ይላሉ? የቤተሰብህን አባላት የምትይዝበት መንገድ የትዳር ጓደኛ ብትኖርህ እንዴት እንደምትይዛት ይጠቁማል።​—ኤፌሶን 4:31⁠ን አንብብ።

      አመለካከትህ፦ ለነገሮች ያለህ አመለካከት አዎንታዊ ነው ወይስ አሉታዊ? ምክንያታዊ ነህ ወይስ ሁልጊዜ እኔ ያልኩት ካልሆነ ትላለህ? ውጥረት የሚፈጥሩ ሁኔታዎችን በረጋ መንፈስ መያዝ ትችላለህ? ትዕግሥተኛ ነህ? የአምላክን መንፈስ ፍሬ ከአሁኑ ለማፍራት ጥረት ማድረግህ ትዳር ስትመሠርት ጥሩ ባል ለመሆን ይረዳሃል።​—ገላትያ 5:22, 23⁠ን አንብብ።

      የገንዘብ አያያዝ፦ በገንዘብ አያያዝ ረገድ እንዴት ነህ? ብዙ ጊዜ ትበደራለህ? በአንድ ሥራ ላይ መቆየት ትችላለህ? ካልሆነ ምክንያቱ ምንድን ነው? የሥራው ጸባይ ነው ወይስ የአሠሪህ ባሕርይ? ወይስ ማስተካከል የሚያስፈልጉህ አንዳንድ መጥፎ ባሕርያት ወይም ልማዶች አሉህ? ከአሁኑ ገንዘብ አያያዝ ካልተማርክ እንዴት አድርገህ ቤተሰብ ማስተዳደር ትችላለህ?​—1 ጢሞቴዎስ 5:8⁠ን አንብብ።

      መንፈሳዊነት፦ የይሖዋ ምሥክር ከሆንክ ጥሩ መንፈሳዊ አቋም አለህ? ማንም ሳይጎተጉትህ የአምላክን ቃል ለማንበብ፣ በአገልግሎት ለመካፈልና በክርስቲያናዊ ስብሰባዎች ላይ ለመሳተፍ ጥረት ታደርጋለህ? የምታገባት ሴት ጠንካራ መንፈሳዊ አቋም ያለው ባል ያስፈልጋታል ቢባል አትስማማም?​—መክብብ 4:9, 10⁠ን አንብብ።

      ማድረግ የምትችለው ነገር

      ዝግጁ ሳትሆን የፍቅር ጓደኝነት እንድትጀምር የሚደረግብህ ጫና በደንብ ያልተማርከውን ትምህርት እንድትፈተን ከመገደድ ጋር ሊመሳሰል ይችላል። ይህ ምክንያታዊ እንዳልሆነ ግልጽ ነው! ፈተና ላይ የሚቀርቡትን ጥያቄዎች መመለስ እንድትችል ትምህርቱን ለማጥናት ጊዜ ያስፈልግሃል።

      የፍቅር ጓደኝነት በመመሥረት ረገድም ሁኔታው ተመሳሳይ ነው። ቀደም ሲል እንደተመለከትነው የፍቅር ጓደኝነት መመሥረት እንደ ዋዛ የሚታይ ነገር አይደለም። በመሆኑም ከአንዲት ወጣት ጋር የፍቅር ጓደኝነት ስለመጀመር ከማሰብህ በፊት በጣም አስፈላጊ የሆነን አንድ “ትምህርት” ለማጥናት ይኸውም ወዳጅነት መመሥረት የሚቻልበትን መንገድ ለመማር በቂ ጊዜ ያስፈልግሃል። እንዲህ ካደረግህ ከጊዜ በኋላ የምትሆንህን ወጣት ስታገኝ ጠንካራ ግንኙነት ለመመሥረት የተሻለ አቋም ይኖርሃል። ጥሩ ጋብቻ የሁለት ጥሩ ጓደኛሞች ጥምረት መሆኑን አትዘንጋ።

      የፍቅር ጓደኝነት ሳትጀምር መቆየትህ ነፃነትህን እንደሚገድብብህ ማሰብ የለብህም። እንዲያውም ‘የወጣትነትህን ጊዜ አስደሳች’ በሆነ መንገድ ለማሳለፍ የበለጠ ነፃነት ይሰጥሃል። (መክብብ 11:9) ከዚህም በተጨማሪ ጥሩ ባሕርያትን በማዳበርና ከምንም በላይ ደግሞ መንፈሳዊነትህን በማጠናከር ራስህን ለማዘጋጀት የሚያስችል ጊዜ ይኖርሃል።​—ሰቆቃወ ኤርምያስ 3:27

      እስከዚያው ድረስ ግን ተቃራኒ ፆታ ካላቸው ወጣቶች ጋር ጥሩ ጊዜ ማሳለፍ ትችላለህ። ይህን ለማድረግ ከሁሉ የተሻለው መንገድ ምንድን ነው? ትልልቅ ሰዎች ባሉበት በቡድን ሆኖ (ከወንዶችም ሆነ ከሴቶች ጋር) መጫወት ይቻላል። ታሚ የተባለች ወጣት እንዲህ ብላለች፦ “እንደዚያ ሲሆን ይበልጥ የሚያስደስት ይመስለኛል። ብዙ ጓደኞች ቢኖሩን የተሻለ ነው።” ሞኒካም በዚህ ሐሳብ ትስማማለች። “በቡድን ሆኖ መጫወት በጣም ጥሩ ነው፤ ምክንያቱም የተለያየ ባሕርይ ያላቸውን ሰዎች ማወቅ ትችላላችሁ” በማለት ተናግራለች።

      በሌላ በኩል ግን ያለ ዕድሜህ በአንድ ሰው ላይ ብቻ ትኩረት የምታደርግ ከሆነ ራስህን ለአደጋ ታጋልጣለህ። ስለዚህ አትቸኩል። ከዚህ ይልቅ ይህንን ዕድሜህን ወዳጅነት መመሥረትና ዘላቂ እንዲሆን ማድረግ የምትችለው እንዴት እንደሆነ ለመማር ተጠቀምበት። እንዲህ ካደረግህ አንድ ቀን የፍቅር ጓደኝነት ለመመሥረት ስትወስን የራስህን ፍላጎትም ሆነ የዕድሜ ልክ የትዳር አጋርህ ከምትሆነው ሴት የምትጠብቃቸውን ባሕርያት በሚገባ ታውቃለህ።

      ተጨማሪ ሐሳብ ለማግኘት የዚህን መጽሐፍ ጥራዝ 1 ምዕራፍ 29 እና 30 ተመልከት

      በሚቀጥለው ምዕራፍ

      ወላጆችህ ሳያውቁ የፍቅር ጓደኝነት ለመጀመር ተፈትነሃል? እንዲህ ማድረግ ከምታስበው በላይ ብዙ ችግሮች ያስከትላል።

      ቁልፍ ጥቅስ

      “አስተዋይ ግን ርምጃውን ያስተውላል።”​—ምሳሌ 14:15

      ጠቃሚ ምክር

      የፍቅር ጓደኝነት ለመጀመርና ጋብቻ ለመመሥረት ዝግጁ መሆን እንድትችል 2 ጴጥሮስ 1:5-7⁠ን ካነበብክ በኋላ ልታዳብረው የሚገባህን አንድ ባሕርይ ምረጥ። ከአንድ ወር በኋላ ስለዚህ ባሕርይ ምን ያህል እንዳወቅክና ይህን ባሕርይ በማዳበር ረገድ ምን ማሻሻያ እንዳደረክ ራስህን ገምግም።

      ይህን ታውቅ ነበር?

      በርካታ ጥናቶች እንደሚያሳዩት ከሆነ ዕድሜያቸው 20 ዓመት ሳይሞላ ትዳር የሚመሠርቱ ወጣቶች በአምስት ዓመት ጊዜ ውስጥ የመፋታታቸው አጋጣሚ ሰፊ ነው።

      ላደርጋቸው ያሰብኳቸው ነገሮች

      ለጋብቻ ዝግጁ ለመሆን የሚከተሉትን ባሕርያት ማዳበር ያስፈልገኛል፦ ․․․․․

      እነዚህን ባሕርያት ለማፍራት እንዲህ አደርጋለሁ፦ ․․․․․

      ከዚህ ርዕሰ ጉዳይ ጋር በተያያዘ ወላጆቼን ልጠይቃቸው የምፈልገው ነገር ․․․․․

      ምን ይመስልሃል?

      ● ተቃራኒ ፆታ ካላቸው ወጣቶች ጋር አብረህ ጊዜ ለማሳለፍ ምን ብታደርግ የተሻለ ነው?

      ● ያለ ዕድሜው የፍቅር ጓደኝነት ለመጀመር የሚፈልግ ወንድም ካለህ እርምጃው ትክክል እንዳልሆነ ልታስረዳው የምትችለው እንዴት ነው?

      ● የማግባት ሐሳብ ሳይኖርህ ከአንዲት ወጣት ጋር የፍቅር ጓደኝነት ብትመሠርት ስሜቷን ልትጎዳ የምትችለው እንዴት ነው?

      [በገጽ 18 ላይ የሚገኝ የተቀነጨበ ሐሳብ]

      እንደ እኔ አመለካከት፣ ከአንድ ሰው ጋር የፍቅር ጓደኝነት መጀመር የሚኖርባችሁ ያንን ሰው በሕይወታችሁ ውስጥ ትልቅ ቦታ የምትሰጡት ከሆነና ወደፊት አብራችሁ መኖር እንደምትችሉ ከተሰማችሁ ነው። ትኩረታችሁን የሳበው ግለሰቡ እንጂ የፍቅር ጓደኝነት መመሥረቱ አይደለም።”​—አምበር

      [በገጽ 16 እና 17 ላይ የሚገኝ ሥዕል]

      አንድ ልጅ አዲስ አሻንጉሊት ሲያገኝ ተጫውቶበት ሲሰለቸው እንደሚጥለው ሁሉ አንተም የማግባት እቅድ ሳይኖርህ የፍቅር ጓደኝነት የምትመሠርት ከሆነ በሌላ ሰው ስሜት እየተጫወትክ ነው

  • በድብቅ የፍቅር ጓደኝነት ብጀምር ምን ችግር አለው?
    ወጣቶች የሚጠይቋቸው ጥያቄዎችና ተግባራዊ መሆን የሚችሉ መልሶች፣ ጥራዝ 2
    • ምዕራፍ 2

      በድብቅ የፍቅር ጓደኝነት ብጀምር ምን ችግር አለው?

      ጄሲካ አጣብቂኝ ውስጥ ገብታ ነበር። ችግሩ የጀመረው ጄረሚ የተባለ የክፍሏ ልጅ ዓይኑን እንደጣለባት ባወቀችበት ጊዜ ነበር። ጄሲካ እንዲህ ብላለች፦ “በጣም ቆንጆ ልጅ ነው፤ በዚያ ላይ ጓደኞቼ በጣም ጨዋ ልጅ እንደሆነና እንደ እሱ ያለ ጓደኛ እንደማላገኝ ይነግሩኝ ነበር። ብዙ ወጣቶች ከእሱ ጋር የፍቅር ጓደኝነት ለመጀመር የሞከሩ ቢሆንም እሱ ግን አንዳቸውንም አልፈለጋቸውም። እሱ የወደደው እኔን ብቻ ነበር።”

      ብዙም ሳይቆይ ጄረሚ የፍቅር ጓደኛው እንድትሆን ጄሲካን ጠየቃት። ጄሲካም የይሖዋ ምሥክር ስለሆነች የእሷ እምነት ተከታይ ካልሆነ ሰው ጋር የፍቅር ጓደኝነት መመሥረት እንደማይፈቀድላት ነገረችው። “ጄረሚ ግን ‘ለምን ወላጆችሽ ሳያውቁ አንጀምርም?’ የሚል ሐሳብ አቀረበልኝ” በማለት ተናግራለች።

      አንተስ ዓይንህን የጣልክባት አንዲት ወጣት እንዲህ ዓይነት ሐሳብ ብታቀርብልህ ምን ምላሽ ትሰጣለህ? ጄሲካ በጄረሚ ሐሳብ እንደተስማማች ስታውቅ ትገረም ይሆናል። ጄሲካ “ከእሱ ጋር የፍቅር ጓደኝነት ከመሠረትኩ ይሖዋን እንዲወድ ልረዳው እንደምችል ተሰምቶኝ ነበር” ብላለች። ታዲያ መጨረሻቸው ምን ሆነ? ይህን በኋላ ላይ እንመለስበታለን። በመጀመሪያ ግን አንዳንዶች እንዲህ ባለ ወጥመድ ውስጥ የሚወድቁት እንዴት እንደሆነ እስቲ እንመልከት።

      እንዲህ የሚያደርጉት ለምንድን ነው?

      አንዳንዶች በድብቅ የፍቅር ጓደኝነት የሚመሠርቱት ለምንድን ነው? ዴቪድ የተባለ አንድ ወጣት “ወላጆቻቸው እንደማይፈቅዱላቸው ስለሚያውቁ አይነግሯቸውም” በማለት ምክንያቱን በአጭሩ አስቀምጦታል። ጄን ደግሞ እንዲህ በማለት ሌላኛውን ምክንያት ጠቅሳለች፦ “በድብቅ የፍቅር ጓደኝነት መመሥረት በራስህ ለመመራት እንደምትፈልግ የምትገልጽበት አንዱ መንገድ ነው። አንተ ትልቅ ሰው እንደሆንክ ብታስብም ወላጆችህ እንደዚያ አድርገው እንደማይመለከቱህ ከተሰማህ ለእነሱ ሳትነግራቸው የፈለግኸውን ነገር ለማድረግ ትወስናለህ።”

      አንተስ አንዳንዶች በድብቅ የፍቅር ጓደኝነት ለመጀመር እንዲነሳሱ የሚያደርጓቸውን ሌሎች ምክንያቶች መጥቀስ ትችላለህ? ያሰብካቸውን ምክንያቶች ከዚህ በታች አስፍራቸው።

      ․․․․․

      መጽሐፍ ቅዱስ ለወላጆችህ መታዘዝ እንዳለብህ የሚሰጠውን መመሪያ እንደምታውቅ ግልጽ ነው። (ኤፌሶን 6:1) ወላጆችህ የፍቅር ጓደኝነት መጀመርህ ተገቢ እንዳልሆነ የሚሰማቸው ከሆነ እንዲህ ያሉበት በቂ ምክንያት መኖር አለበት። ሆኖም እንደሚከተሉት ያሉ ሐሳቦች ወደ አእምሮህ ቢመጡ ሊገርምህ አይገባም፦

      ● ከእኔ በቀር ሁሉም የፍቅር ጓደኛ ስላላቸው የቀረብኝ ነገር እንዳለ ይሰማኛል።

      ● የእኔ እምነት ተከታይ ካልሆነች ወጣት ጋር ፍቅር ይዞኛል።

      ● ለማግባት ዕድሜዬ ገና ቢሆንም ከአንዲት ክርስቲያን ጋር የፍቅር ጓደኝነት መጀመር እፈልጋለሁ።

      ወላጆችህ እንዲህ እንደምታስብ ቢያውቁ ምን እንደሚሉህ ታውቅ ይሆናል። ደግሞም ወላጆችህ ትክክል እንደሆኑ ልብህ ያውቀዋል። ያም ሆኖ ግን ማናሚ እንደተባለችው ወጣት ይሰማህ ይሆናል፦ “የፍቅር ጓደኝነት እንድመሠርት የሚደረግብኝ ግፊት በጣም ከባድ ከመሆኑ የተነሳ እንዲህ ዓይነቱን ግንኙነት ላለመጀመር የወሰድኩት አቋም ትክክል መሆኑን የምጠራጠርበት ጊዜ አለ። በዛሬው ጊዜ ያሉ ወጣቶች የፍቅር ጓደኛ አለመያዝ የማይታሰብ ነገር እንደሆነ ይሰማቸዋል። በዚያ ላይ ደግሞ የፍቅር ጓደኛ ሳይኖረኝ ብቻዬን መታየት ደስ የሚል ነገር አይደለም!” እንዲህ የሚሰማቸው አንዳንድ ወጣቶች ከወላጆቻቸው ተደብቀው የፍቅር ጓደኝነት ጀምረዋል። እንዴት?

      “ለማንም እንዳንናገርባቸው ነገሩን”

      “በድብቅ የፍቅር ጓደኝነት መጀመር” የሚለው ሐሳብ በራሱ ይህ ድርጊት በተወሰነ መጠንም ቢሆን ማታለል እንዳለበት ይጠቁማል፤ ደግሞም ግንኙነቱ ድብቅ እንዲሆን ስትሉ አንዳንድ ጊዜ መዋሸታችሁ አይቀርም። አንዳንዶች የመሠረቱት የፍቅር ጓደኝነት እንዳይታወቅባቸው ሲሉ በዋነኝነት የሚገናኙት በስልክ ወይም በኢንተርኔት አማካኝነት ነው። ሰዎች ፊት ሲሆኑ ተራ ጓደኛሞች ይመስላሉ፤ በኢንተርኔትና በሞባይል ስልክ አማካኝነት የሚለዋወጡት መልእክት ቢታይ እንዲሁም በስልክ የሚያወሩት ነገር ቢሰማ ግን ታሪኩ ሌላ ነው።

      የፍቅር ጓደኝነት የጀመሩ ወጣቶች ግንኙነታቸው እንዳይታወቅባቸው የሚጠቀሙበት ሌላው ዘዴ ደግሞ ከጓደኞቻቸው ጋር በቡድን ሆነው ለመገናኘት ፕሮግራም ማዘጋጀት ነው፤ ይህን የሚያደርጉት ግን ከሌሎቹ ገንጠል ብለው ለማውራት እንዲያመቻቸው ሲሉ ነው። ጄምስ እንዲህ ብሏል፦ “በአንድ ወቅት የተወሰንን ወጣቶች በአንድ ዝግጅት ላይ እንድንገኝ ተጋብዘን ነበር፤ በኋላ ላይ እንደገባኝ ግን ለካስ ዝግጅቱ የተደረገው ከመካከላችን ሁለቱ አብረው የሚሆኑበትን አጋጣሚ ለማመቻቸት ነበር። ከዚያም ለማንም እንዳንናገርባቸው ነገሩን።”

      ጄምስ እንደተናገረው በድብቅ የፍቅር ጓደኝነት የጀመሩ ወጣቶች መገናኘት እንዲችሉ አብዛኛውን ጊዜ ጓደኞቻቸው ይተባበሯቸዋል። ካሮል “ብዙውን ጊዜ፣ ቢያንስ ከጓደኞቻቸው አንዱ ስለ ጉዳዩ ያውቃል፤ ሆኖም ቢናገር ጓደኛው እንደሚቀየመው ስለሚያውቅ ዝምታን ይመርጣል” ብላለች። እንዲያውም በድብቅ የፍቅር ጓደኝነት የጀመሩ ወጣቶች አንዳንዴ ዓይን ያወጣ ውሸት ይናገራሉ። ቤዝ የተባለች የ17 ዓመት ወጣት “ብዙዎች የፍቅር ጓደኝነት መጀመራቸው እንዳይታወቅባቸው ሲሉ የት እንደሚሄዱ ወላጆቻቸው ሲጠይቋቸው ይዋሻሉ” ብላለች። የ19 ዓመቷ ሚሳኪ ተመሳሳይ ነገር ታደርግ ነበር፤ እንዲህ ብላለች፦ “የሌለ ታሪክ በመፍጠር ለመሸወድ እሞክር ነበር። ሆኖም የወላጆቼን አመኔታ ላለማጣት ስል፣ ከጀመርኩት የፍቅር ጓደኝነት ጋር የተያያዘ ካልሆነ በቀር ሌላ ምንም ዓይነት ውሸት ላለመናገር እጠነቀቅ ነበር።”

      በድብቅ የፍቅር ጓደኝነት መመሥረት የሚያስከትላቸው ችግሮች

      በድብቅ የፍቅር ጓደኝነት የመጀመር ፍላጎት ካለህ አሊያም በአሁኑ ወቅት እንዲህ እያደረግህ ከሆነ የሚከተሉትን ሁለት ጥያቄዎች ራስህን መጠየቅ ያስፈልግሃል፦

      ይህ አካሄዴ ወዴት ይመራኛል? የወደድካትን ወጣት በቅርቡ የማግባት ሐሳብ አለህ? ኢቫን የተባለ የ20 ዓመት ወጣት “የማግባት እቅድ ሳይኖራችሁ የፍቅር ጓደኝነት መመሥረት የማትሸጡትን ዕቃ የማስተዋወቅ ያህል ነው” በማለት ተናግሯል። እንዲህ ማድረግ ምን ያስከትላል? ምሳሌ 13:12 (የ1954 ትርጉም) “የምትዘገይ ተስፋ ልብን ታሳዝናለች” ይላል። የምትወዳትን ወጣት ልብ ማሳዘን ትፈልጋለህ? ልታስብበት የሚገባው ሌላው ነጥብ ደግሞ በድብቅ የፍቅር ጓደኝነት መጀመርህ ወላጆችህና ስለ አንተ የሚያስቡ ሌሎች ትልልቅ ሰዎች ሊሰጡህ ይችሉ የነበረውን ጠቃሚ ምክር የሚያሳጣህ መሆኑ ነው። በዚህም የተነሳ የፆታ ብልግና ለመፈጸም ትጋለጥ ይሆናል።​—ገላትያ 6:7

      ይሖዋ አምላክ ስለ ድርጊቴ ምን ይሰማዋል? መጽሐፍ ቅዱስ “ተጠያቂዎች በሆንበት በእሱ ዓይኖች ፊት ሁሉም ነገር የተራቆተና ገሃድ የወጣ ነው” ይላል። (ዕብራውያን 4:13) አንተ ወይም አንድ ጓደኛህ በድብቅ የፍቅር ጓደኝነት ጀምራችሁ ይሆናል፤ ይህንን ሌሎች እንዳያውቁ የምትሸፋፍን ከሆነ ቀድሞውንም ቢሆን ይሖዋ ጉዳዩን እንደሚያውቀው ማስታወስ ይኖርብሃል። የምትዋሽ ከሆነ ደግሞ ነገሩ ሊያሳስብህ ይገባል። ምክንያቱም ይሖዋ አምላክ ውሸትን አጥብቆ ይጠላል። ይሖዋ እንደሚጸየፋቸው በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ ከተዘረዘሩት ነገሮች መካከል በዋነኝነት የተጠቀሰው “ሐሰተኛ ምላስ” ነው!​—ምሳሌ 6:16-19

      ድብብቆሹን ማቆም

      በድብቅ የፍቅር ጓደኝነት ጀምረህ ከሆነ ጉዳዩን በተመለከተ ከወላጆችህ ወይም ከአንድ የጎለመሰ ክርስቲያን ጋር መነጋገርህ የጥበብ እርምጃ እንደሆነ ጥርጥር የለውም። በድብቅ የፍቅር ጓደኝነት የጀመረ ጓደኛ ካለህ ድርጊቱን ለመሸፋፈን በመሞከር ከእሱ ጋር መተባበር የለብህም። (1 ጢሞቴዎስ 5:22) ደግሞስ የጓደኛህ አካሄድ ጎጂ ውጤቶችን ቢያስከትል ምን ይሰማሃል? በተወሰነ መጠንም ቢሆን ተጠያቂ የምትሆን አይመስልህም?

      ነጥቡን በምሳሌ ለማስረዳት፣ የስኳር በሽታ እያለበት ጣፋጭ ምግቦችን በድብቅ የሚበላ አንድ ጓደኛ አለህ እንበል። ስለ ሁኔታው ብታውቅና ጓደኛህ ለማንም እንዳትናገርበት ቢለምንህ ምን ታደርጋለህ? ይበልጥ የሚያሳስብህ የጓደኛህን ሚስጥር መጠበቅህ ነው ወይስ ሕይወቱን ለማዳን እርምጃ መውሰድህ?

      አንድ ጓደኛህ በድብቅ የፍቅር ግንኙነት እንደጀመረ የምታውቅ ከሆነም ሁኔታው ተመሳሳይ ነው። ‘ብናገር ጓደኝነታችን ያከትማል’ የሚል ስጋት ሊያድርብህ አይገባም! ይዋል ይደር እንጂ እውነተኛ ጓደኛ ይህን ያደረግኸው ለእሱ ጥቅም ብለህ መሆኑን መገንዘቡ አይቀርም።​—መዝሙር 141:5

      በሚስጥር መያዝ ሁልጊዜ ስህተት ነው?

      የፍቅር ጓደኝነትን በሚስጥር መያዝ ሁልጊዜ ስህተት ነው ማለት አይደለም። ለምሳሌ፣ አንድ ወንድና አንዲት ሴት ለመጠናናት ፈለጉ እንበል፤ ሆኖም ጉዳዩን ለጊዜው ብዙ ሰው እንዲያውቀው አልፈለጉም። ቶማስ የተባለ አንድ ወጣት እንደተናገረው ይህን ያደረጉት “ሰዎች ‘መቼ ነው የምትጋቡት?’ እንደሚሉት ያሉ ጥያቄዎችን በማንሳት እንዳያሸማቅቋቸው ፈርተው ሊሆን ይችላል።”

      በእርግጥም ሌሎች ተገቢ ያልሆነ ግፊት ማድረጋቸው ጎጂ ውጤት ሊኖረው ይችላል። (ማሕልየ መሓልይ 2:7) በመሆኑም አንዳንድ ጥንዶች ጓደኝነት እንደጀመሩ ጉዳዩን ብዙ ሰው እንዲያውቀው አለማድረጉ የጥበብ እርምጃ እንደሆነ ይሰማቸው ይሆናል። (ምሳሌ 10:19) የ20 ዓመቷ አና እንዲህ ብላለች፦ “እንደዚህ ማድረጋቸው ሁለቱ ሰዎች ዘላቂ የሆነ ጥምረት መመሥረት ይችሉ እንደሆነ አስበውበት ለመወሰን ጊዜ ይሰጣቸዋል። እንዲህ ዓይነት ውሳኔ ላይ ከደረሱ ያን ጊዜ ጉዳዩን ለሰዎች ማሳወቅ ይችላሉ።”

      በሌላ በኩል ግን የፍቅር ጓደኝነት ስትጀምር ስለ ግንኙነታችሁ ማወቅ ከሚገባቸው ሰዎች ለምሳሌ ከወላጆችህ ወይም ከእሷ ወላጆች ጉዳዩን መደበቅ ስህተት ይሆናል። የፍቅር ጓደኝነት መጀመርህን ለወላጆችህ በግልጽ መናገር ከከበደህ ምክንያትህ ምን እንደሆነ ራስህን መጠየቅ ይገባሃል። መናገር የከበደህ ወላጆችህ ምርጫህን የሚቃወሙበት በቂ ምክንያት እንደሚኖራቸው ስለምታውቅ ይሆን?

      “ምን ማድረግ እንዳለብኝ አወቅሁ”

      መግቢያው ላይ የተጠቀሰችው ጄሲካ ከእሷ ጋር የሚመሳሰል ሁኔታ ያጋጠማትን የአንዲት ክርስቲያን ተሞክሮ ስትሰማ ከጄረሚ ጋር በድብቅ የጀመረችውን የፍቅር ግንኙነት ለማቆም ወሰነች። ጄሲካ “ያቺ እህት ግንኙነቷን እንዴት እንዳቆመች ስሰማ እኔም ምን ማድረግ እንዳለብኝ አወቅሁ” ብላለች። ጄሲካ ከጄረሚ ጋር ያላትን ግንኙነት ማቋረጥ ቀላል ሆኖላት ነበር? አልሆነላትም! “በሕይወቴ የወደድኩት እሱን ብቻ ነበር፤ ለበርካታ ሳምንታት ሥራዬ ማልቀስ ብቻ ሆኖ ነበር” ብላለች።

      ይሁንና ጄሲካ ይሖዋን ትወዳለች። ለተወሰነ ጊዜ የተሳሳተ ጎዳና ተከትላ የነበረ ቢሆንም እንኳ ትክክል የሆነውን ነገር ለማድረግ ከልቧ ትፈልጋለች። ግንኙነቱን ማቋረጧ ያስከተለባት ሥቃይ እያደር እየቀነሰ ሄደ። ጄሲካ “አሁን ከይሖዋ ጋር ያለኝ ግንኙነት ከመቼውም ጊዜ ይበልጥ የተሻለ ነው። ይሖዋ የሚያስፈልገንን መመሪያ በትክክለኛው ወቅት ስለሚሰጠን በጣም አመስጋኝ ነኝ!” በማለት ተናግራለች።

      በሚቀጥለው ምዕራፍ

      የፍቅር ጓደኝነት ለመጀመር ደርሰህ ብሎም የምትወዳት ወጣት አግኝተህ ይሆናል፤ ይሁንና አንተም ሆንክ እሷ አንዳችሁ ለሌላው ትሆኑ እንደሆነና እንዳልሆነ ማወቅ የምትችሉት እንዴት ነው?

      ቁልፍ ጥቅስ

      ‘በሁሉም ነገር በሐቀኝነት ለመኖር እንመኛለን።’​—ዕብራውያን 13:18

      ጠቃሚ ምክር

      የፍቅር ጓደኝነት መጀመርህን አገር እንዲያውቅልህ ማድረግ አያስፈልግህም። ይሁንና ማወቅ ለሚገባቸው ሰዎች መናገር ይኖርብሃል። አብዛኛውን ጊዜ የአንተም ሆኑ የእሷ ወላጆች ጉዳዩን ማወቅ ይኖርባቸዋል።

      ይህን ታውቅ ነበር?

      የፍቅር ግንኙነት ዘላቂ እንዲሆን በመተማመን ላይ የተመሠረተ ሊሆን ይገባል። በድብቅ የፍቅር ጓደኝነት መጀመር የወላጆችህን አመኔታ የሚያሳጣህ ከመሆኑም ሌላ ከፍቅር ጓደኛህ ጋር ያለህ ግንኙነት ጠንካራ መሠረት እንዳይኖረው ያደርጋል።

      ላደርጋቸው ያሰብኳቸው ነገሮች

      የእምነት ባልንጀራዬ ከሆነች አንዲት ክርስቲያን ጋር በድብቅ የፍቅር ጓደኝነት ጀምሬ ከሆነ እንዲህ አደርጋለሁ፦ ․․․․․

      አንድ ጓደኛዬ በድብቅ የፍቅር ግንኙነት ጀምሮ ከሆነ እንዲህ አደርጋለሁ፦ ․․․․․

      ከዚህ ርዕሰ ጉዳይ ጋር በተያያዘ ወላጆቼን ልጠይቃቸው የምፈልገው ነገር ․․․․․

      ምን ይመስልሃል?

      ● በገጽ 22 ላይ ደመቅ ብለው የተጻፉትን ሦስት ነጥቦች መለስ ብለህ ተመልከት። አንተስ አንዳንድ ጊዜ እንደዚያ ይሰማሃል? ከሆነ የአንተን ስሜት የሚያንጸባርቀው የትኛው ነው?

      ● በድብቅ የፍቅር ጓደኝነት ሳትጀምር ለዚህ ሁኔታ መፍትሔ ማግኘት የምትችለው እንዴት ነው?

      ● አንድ ጓደኛህ በድብቅ የፍቅር ጓደኝነት እንደጀመረ ብታውቅ ምን ታደርጋለህ? እንዲህ የምታደርገው ለምንድን ነው?

      [በገጽ 27 ላይ የሚገኝ የተቀነጨበ ሐሳብ]

      በድብቅ የጀመርኩትን የፍቅር ጓደኝነት አቆምኩ። በእርግጥ በየቀኑ ትምህርት ቤት ልጁን ሳየው ውስጤ ይረበሽ ነበር። ይሁን እንጂ ይሖዋ አምላክ ሁሉንም ነገር ማወቅ የሚችል ሲሆን እኛ ግን እንዲህ ማድረግ አንችልም። ከእኛ የሚፈለገው በይሖዋ መታመን ብቻ ነው።”​—ጄሲካ

      [በገጽ 25 ላይ የሚገኝ ሥዕል]

      አንድ ጓደኛህ በድብቅ የጀመረው የፍቅር ግንኙነት እንዳይታወቅበት መሸፋፈንህ የስኳር በሽታ እያለበት ጣፋጭ ምግቦችን በድብቅ ለሚበላ ጓደኛህ ከመሸፋፈን ተለይቶ አይታይም

  • ይህ ሰው ይሆነኛል?
    ወጣቶች የሚጠይቋቸው ጥያቄዎችና ተግባራዊ መሆን የሚችሉ መልሶች፣ ጥራዝ 2
    • ምዕራፍ 3

      ይህ ሰው ይሆነኛል?

      የሚከተሉትን ጥያቄዎች በደንብ አስቢባቸውና መልስ ስጪ፦

      አሁን ካለሽ አመለካከት አንጻር፣ የምታገቢው ሰው ሊኖሩት ይገባል የምትያቸው ባሕርያት የትኞቹ ናቸው? ከታች ከተዘረዘሩት መካከል በጣም አስፈላጊ እንደሆኑ በሚሰሙሽ በአራቱ ላይ ✔ አድርጊ።

      □ ቆንጆ □ መንፈሳዊ

      □ ተግባቢ □ የሚታመን

      □ ተወዳጅ □ ጨዋ

      □ ተጫዋች □ የዓላማ ሰው

      በዕድሜ ለጋ በነበርሽበት ወቅት የወረት ፍቅር ይዞሽ ያውቃል? ከላይ ከተዘረዘሩት መካከል በዚያ ወቅት ግለሰቡን በጣም እንድትወጂው ባደረገሽ ባሕርይ ላይ ✘ አድርጊ።

      ከላይ ከተጠቀሱት ባሕርያት መካከል አንዳቸውም ቢሆኑ መጥፎ አይደሉም። ሁሉም የራሳቸው የሆነ ደስ የሚል ነገር አላቸው። ሆኖም የወረት ፍቅር ይዞሽ በነበረበት ወቅት ይበልጥ ያተኮርሽው በስተግራ በኩል እንደተዘረዘሩት ባሉ ውጫዊ ነገሮች ላይ ነበር ቢባል አትስማሚም?a

      አንድ ሰው በዕድሜ እየበሰለ ሲሄድ ግን በማስተዋል ችሎታው በመጠቀም በስተቀኝ በኩል እንደተጠቀሱት ዓይነት በጣም አስፈላጊ ባሕርያት ያሉት ግለሰብ ለማግኘት ጥረት ማድረግ ይጀምራል። ለምሳሌ ያህል፣ አንድ ወጣት በሰፈሩ ውስጥ በጣም ቆንጆ የምትባለው ልጅ የምትታመን እንዳልሆነች ሊያስተውል ይችላል፤ አሊያም ደግሞ አንዲት ወጣት በክፍሏ ውስጥ በጣም ተወዳጅ የሆነው ልጅ ጨዋ እንዳልሆነ ትገነዘብ ይሆናል። አብዛኛውን ጊዜ ወጣቶች አፍላ የጉርምስና ዕድሜን ካለፉ በኋላ “ይህ ሰው ይሆነኛል?” የሚለውን ጥያቄ ለመመለስ ይበልጥ የሚያተኩሩት ከውጪ በሚታዩ ባሕርያት ላይ ሳይሆን በውስጣዊ ማንነት ላይ ይሆናል።

      በቅድሚያ ራስን ማወቅ ያስፈልጋል

      ለትዳር የሚሆንሽን ሰው ለማግኘት ከመሞከርሽ በፊት ራስሽን በሚገባ ማወቅ ይኖርብሻል። ራስሽን ይበልጥ ለማወቅ እንድትችዪ የሚከተሉትን ጥያቄዎች አስቢባቸው፤ ከዚያም መልስሽን ክፍት ቦታው ላይ አስፍሪ፦

      ምን ጠንካራ ጎኖች አሉኝ? ․․․․․

      ደካማ ጎኖቼስ የትኞቹ ናቸው? ․․․․․

      የማገባው ሰው እንዴት እንዲይዘኝ እፈልጋለሁ? በመንፈሳዊነቴ ረገድስ ምን ደረጃ ላይ መድረስ እፈልጋለሁ? ․․․․․

      ራስሽን ማወቅ ቀላል እንዳልሆነ ባይካድም ከላይ እንደሰፈሩት ባሉ ጥያቄዎች በመጠቀም እንደዚህ ማድረግ ትችያለሽ። ራስሽን ይበልጥ እያወቅሽ በሄድሽ መጠን፣ ከድክመትሽ ይልቅ በጠንካራ ጎንሽ ላይ በማተኮር የተሻልሽ ሰው እንድትሆኚ የሚረዳሽን ሰው ለማግኘት የሚያስችል ብቃት እያዳበርሽ ትሄጃለሽ።b እንዲህ ዓይነት ሰው እንዳገኘሽ የሚሰማሽ ከሆነስ?

      ማንኛውም ሰው ሊሆነኝ ይችላል?

      “ብንጠናና ምን ይመስልሻል?” እንዲህ ያለ ጥያቄ ቢቀርብልሽ በጣም ትጨነቂ አሊያም ደግሞ በደስታ ትፈነድቂ ይሆናል፤ ይህን የሚወስነው የጠየቀሽ ሰው ማንነት ነው። መልስሽ ‘እሺ’ ነው እንበል። ታዲያ በምትጠናኑበት ጊዜ ይህ ሰው ይሆንሽ እንደሆነ ማወቅ የምትችይው እንዴት ነው?

      አዲስ ጫማ ለመግዛት አስበሻል እንበል። አንድ ሱቅ ስትገቢ ዓይንሽ አንድ ጫማ ላይ አረፈ። የሚያናድደው ግን ጫማውን ስትሞክሪው በጣም ጠበበሽ። ምን ታደርጊያለሽ? የፈለገው ይሁን ብለሽ ጫማውን ትገዢዋለሽ? ወይስ ሌላ ጫማ ለማግኘት ትሞክሪያለሽ? የሚያዋጣሽ ጫማውን ወደ ቦታው መልሰሽ ሌላ መፈለግ ነው። የማይሆንሽን ጫማ አድርገሽ መሄድ ሞኝነት ይሆናል!

      የትዳር ጓደኛ ከመምረጥ ጋር በተያያዘም ሁኔታው ተመሳሳይ ነው። ጊዜ እያለፈ ሲሄድ ቀልብሽን የሚስቡ የተለያዩ ወንዶች ያጋጥሙሽ ይሆናል። ያም ቢሆን ግን ማንኛውም ሰው ይሆንሻል ማለት አይደለም። ደግሞስ የምትፈልጊው የሚመችሽ ይኸውም ከባሕርይሽ ጋር የሚጣጣምና እንደ አንቺ ዓይነት ግብ ያለው ሰው አይደለም? (ዘፍጥረት 2:18፤ ማቴዎስ 19:4-6) ታዲያ እንደዚህ ዓይነት ሰው አግኝተሻል? ከሆነ ይህ ሰው እንደሚሆንሽ ማወቅ የምትችይው እንዴት ነው?

      ውጫዊ በሆኑ ነገሮች ላይ ከማተኮር መቆጠብ

      ግለሰቡ ይሆንሽ እንደሆነ በምትገመግሚበት ወቅት ስሜታዊ ላለመሆን ጥንቃቄ አድርጊ! ምክንያቱም ማየት የምትፈልጊውን ብቻ ወደ ማየት ልታዘነብዪ ትችያለሽ። ስለዚህ አትቸኩዪ፤ የግለሰቡን እውነተኛ ባሕርያት ለማወቅ ጥረት አድርጊ። ይህን ለማድረግ ብዙ ልፋት ይጠይቅብሽ ይሆናል። ሆኖም ይህ የሚያስገርም አይደለም። ነጥቡን በምሳሌ ለማስረዳት ያህል፣ አንድ ወጣት መኪና ለመግዛት አሰበ እንበል። መኪናውን ምን ያህል በጥንቃቄ መፈተሽ ያለበት ይመስልሻል? የመኪናውን ውጫዊ መልክ ብቻ ከመመልከት አልፎ ውስጡን መፈተሹ ምናልባትም ሞተሩ ስላለበት ሁኔታ የተቻለውን ያህል ለማወቅ መሞከሩ ተገቢ አይሆንም?

      የትዳር ጓደኛ ማግኘት መኪና ከመምረጥ ይበልጥ በቁም ነገር ሊታይ የሚገባው ጉዳይ ነው። ያም ሆኖ መጠናናት የጀመሩ ብዙ ወጣቶች ከውጫዊ ነገሮች አልፈው አይመለከቱም። ቶሎ የሚታዩዋቸው ከወደዱት ሰው ጋር የሚያመሳስሏቸው ነገሮች ናቸው። ለምሳሌ ‘የሙዚቃ ምርጫችን አንድ ዓይነት ነው፣’ ‘የምንመርጣቸው የጊዜ ማሳለፊያዎች ተመሳሳይ ናቸው፣’ ‘በሁሉም ነገር እንስማማለን!’ ማለት ይቀናቸዋል። አንቺ ግን ቀደም ሲል እንደተጠቀሰው በእርግጥ አፍላ የጉርምስና ዕድሜን አልፈሽ ከሆነ የሚማርኩሽ ውጪያዊ የሆኑ ነገሮች አይሆኑም። ምክንያቱም የግለሰቡን “የተሰወረ የልብ ሰው” ለማወቅ ጥረት ማድረግ አስፈላጊ መሆኑን ትገነዘቢያለሽ።​—1 ጴጥሮስ 3:4፤ ኤፌሶን 3:16

      ለምሳሌ፣ በምትስማሙባቸው ነገሮች ላይ ከማተኮር ይልቅ የማትስማሙባቸው ነገሮች ሲኖሩ ግለሰቡ ምን ዓይነት ባሕርይ እንደሚያሳይ ብታስተውዪ ስለ ውስጣዊ ማንነቱ ይበልጥ ማወቅ ትችያለሽ። በሌላ አባባል፣ ይህ ሰው አለመግባባቶች ሲፈጠሩ ምን ያደርጋል? እኔ ያልኩት ካልሆነ ብሎ ድርቅ ይላል? ምናልባትም “በቁጣ መገንፈል” ወይም ‘መሳደብ’ ይቀናዋል? (ገላትያ 5:19, 20፤ ቆላስይስ 3:8) ወይስ ነገሩ የምርጫ ጉዳይ በሚሆንበት ጊዜ ሰላም ለመፍጠር ሲል የሌላውን ሐሳብ በመቀበል ምክንያታዊ መሆኑን ያሳያል?​—ያዕቆብ 3:17

      ሌላም ልታስቢበት የሚገባ ጉዳይ አለ፦ ይህ ሰው የሚፈልገውን ነገር ለማግኘት ሲል ሊጫንሽ ይሞክራል? በትንሽ በትልቁ ይቀናል? የት ገባሽ የት ወጣሽ ያበዛል? ኒኮል የተባለች አንዲት ወጣት እንዲህ ብላለች፦ “አንዳንድ ጓደኛሞች፣ ‘የት እንዳለሽ ሁልጊዜ ልትነግሪኝ ይገባል’ በሚል እንደሚጨቃጨቁ እሰማለሁ። እንዲህ ያለው ባሕርይ ችግር መኖሩን የሚጠቁም ምልክት እንደሆነ ይሰማኛል።”​—1 ቆሮንቶስ 13:4

      ከላይ እንደተጠቀሱት ያሉት ነጥቦች በጓደኛሽ ባሕርይና ምግባር ላይ ያተኮሩ ናቸው። ሌሎች ስለ ጓደኛሽ ምን አመለካከት እንዳላቸው ማወቅሽም የዚያኑ ያህል አስፈላጊ ነው። ጓደኛሽ በሰዎች ዘንድ ምን ስም አትርፏል? ይህን ለማወቅ ግለሰቡን በደንብ የሚያውቁትን ሰዎች ለምሳሌ በጉባኤ ያሉ የጎለመሱ ክርስቲያኖችን ማነጋገሩ ጠቃሚ ይሆናል። በዚህ መንገድ ጓደኛሽ “በመልካም ምግባሩ የተመሠከረለት” መሆን አለመሆኑን ማወቅ ትችያለሽ።​—የሐዋርያት ሥራ 16:1, 2

      እስካሁን ካየናቸው ነጥቦች አንጻር ጓደኛሽን ስትመዝኚው የተሰማሽን ነገር በጽሑፍ ማስፈርሽ ስለ እሱ ማንነት ሰፋ ያለ ግንዛቤ እንዲኖርሽ ይረዳሻል።

      ባሕርያቱ ․․․․․

      ምግባሩ ․․․․․

      ያተረፈው ስም ․․․․․

      ከዚህም በተጨማሪ በገጽ 39 ላይ ያለውን “ጥሩ ባል ይሆነኛል?” የሚለውን ሣጥን ወይም በገጽ 40 ላይ የሚገኘውን “ጥሩ ሚስት ትሆነኛለች?” የሚለውን ሣጥን መመልከቱም ጠቃሚ ነው። በእነዚህ ሣጥኖች ውስጥ የቀረቡት ጥያቄዎች አንዳችሁ ለሌላው ተስማሚ የትዳር ጓደኛ መሆን ትችሉ እንደሆነ ለመወሰን ይረዷችኋል።

      ጉዳዩን በጥሞና ካሰብሽበት በኋላ ‘ይህ ግለሰብ አይሆነኝም’ የሚል ድምዳሜ ላይ ብትደርሺስ? በዚህ ወቅት ፈተና የሚሆንብሽ የሚከተለውን ጥያቄ መመለስ ይሆናል፦

      ግንኙነታችንን ማቆም ይኖርብን ይሆን?

      መለያየት ጠቃሚ የሚሆንበት ጊዜ አለ። ጂል የተባለች ወጣት ያጋጠማትን ሁኔታ እንመልከት። እንዲህ ብላለች፦ “መጀመሪያ አካባቢ የወንድ ጓደኛዬ የት እንዳለሁ፣ ምን እያደረግሁ እንደሆነ እንዲሁም ከማን ጋር እንደሆንኩ ሁልጊዜ ሲጠይቀኝ እንደሚጨነቅልኝ ስለሚሰማኝ ደስ ይለኝ ነበር። በኋላ ላይ ግን ከእሱ ጋር ብቻ ካልሆነ በቀር ከሌላ ሰው ጋር ለደቂቃ እንኳ ጊዜ ማሳለፍ ችግር ሆነ። ሌላው ቀርቶ ከቤተሰቤ ጋር በተለይ ደግሞ ከአባቴ ጋር ስሆን ይቀና ጀመር። ከእሱ ጋር የነበረኝን ግንኙነት ሳቆም አንዳች ነገር ከላዬ ላይ የወረደልኝ ያህል ቅልል አለኝ!”

      ሣራም ተመሳሳይ ሁኔታ አጋጥሟታል። የወንድ ጓደኛዋ የነበረው ጆን፣ ሥርዓት የጎደለውና ምንም ቢደረግለት የማይደሰት ሰው መሆኑን እያደር አስተዋለች፤ ከዚህም በላይ በአሽሙር ይናገራት ነበር። ሣራ ያጋጠማትን ስታስታውስ እንዲህ ብላለች፦ “በአንድ ወቅት ከቀጠሯችን ሦስት ሰዓት አርፍዶ መጣ! እናቴ በሩን ስትከፍትለት ዝግት አድርጓት ገባ። ከዚያም ‘እንሂዳ፣ አርፍደናልኮ!’ አለኝ። የሚገርመው ‘አርፍጃለሁ’ ከማለት ይልቅ ‘አርፍደናል’ ነበር ያለው። ይቅርታ መጠየቅ ወይም ያረፈደበትን ምክንያት መግለጽ ነበረበት። ከሁሉ በላይ ደግሞ ለእናቴ አክብሮት ሊያሳያት ይገባ ነበር!” እርግጥ ነው፣ ግለሰቡ አንድ ወቅት ላይ መጥፎ ጠባይ ስላሳየ ወይም የሚያበሳጭሽ ነገር ስላደረገ ብቻ ግንኙነታችሁ መቆም አለበት ማለት አይደለም። (መዝሙር 130:3) ሆኖም ሣራ፣ ጓደኛዋ ከላይ የጠቀሰችው ዓይነት ሥርዓት የጎደለው ጠባይ ያሳየው በአጋጣሚ እንዳልሆነና እንዲህ ማድረግ ልማዱ እንደሆነ ስትገነዘብ ግንኙነታቸውን ለማቆም ወሰነች።

      አንቺም እንደ ጂልና እንደ ሣራ የወንድ ጓደኛሽ ተስማሚ የትዳር አጋር እንደማይሆንሽ ብትገነዘቢስ? እንዲህ ከሆነ ውስጥሽ የሚነግርሽን ማዳመጥ አለብሽ! ሁኔታውን አምኖ መቀበል እንደሚከብድሽ ባይካድም ግንኙነቱን ማቆም ከሁሉ የተሻለ ውሳኔ ሊሆን ይችላል። ምሳሌ 22:3 “አስተዋይ ሰው አደጋ ሲያይ መጠጊያ ይሻል” ይላል። ለምሳሌ ያህል፣ አንደኛው ወገን በገጽ 39 እና 40 ላይ ከተጠቀሱት “አደገኛ ምልክቶች” አንዱን እንኳ የሚያሳይ ከሆነ ቢያንስ ችግሩ እስኪስተካከል ድረስ ግንኙነቱን ማቋረጡ ጥበብ ይሆናል። እውነት ነው፣ ግንኙነቱን ማቋረጥ ቀላል ላይሆን ይችላል። ይሁንና ጋብቻ ዘላቂ ጥምረት እንደሆነ አስታውሺ። መለያየታችሁ ለተወሰነ ጊዜ ቢያሳዝንሽም ዕድሜ ልክሽን በጸጸት ስሜት ስትሠቃዪ ከመኖር ይሻልሻል!

      ውሳኔን ማሳወቅ

      ግንኙነታችሁን ማቆም እንደምትፈልጊ ማሳወቅ የሚኖርብሽ እንዴት ነው? በቅድሚያ ለመነጋገር አመቺ የሆነ ሁኔታ መምረጥ አለብሽ። ይህ ሲባል ምን ማለት ነው? አንቺ በእሱ ቦታ ብትሆኚ ኖሮ ጉዳዩ እንዴት እንዲነገርሽ እንደምትፈልጊ አስቢ። (ማቴዎስ 7:12) በሌሎች ፊት ቢነገርሽ ደስ ይልሻል? ደስ እንደማይልሽ የታወቀ ነው። ከሁኔታዎች አንጻር እንዲህ ማድረጉ ጥበብ እንደሆነ ካልተሰማሽ በቀር በስልክ የመልእክት መቀበያ ማሽን ላይ መልእክት በመተው አሊያም በሞባይል ወይም በኢንተርኔት አማካኝነት የጽሑፍ መልእክት በመላክ ውሳኔሽን ማሳወቅም ተገቢ አይደለም። ከዚህ ይልቅ ይህንን ከባድ ጉዳይ ለመወያየት አመቺ የሆነ ጊዜና ቦታ ምረጪ።

      አመቺ የሆነውን ሁኔታ ከመረጥሽ በኋላ ቀጣዩ ነገር ውሳኔሽን የምትናገሪው እንዴት ነው? የሚለው ይሆናል። ሐዋርያው ጳውሎስ፣ እርስ በርሳቸው ‘እውነትን እንዲነጋገሩ’ ክርስቲያኖችን አሳስቧቸዋል። (ኤፌሶን 4:25) ስለዚህ ከሁሉ የተሻለው መንገድ ጥብቅ አቋም እንዳለሽ በሚያሳይ ሆኖም ስሜቱን በማይጎዳ መልኩ ውሳኔሽን ማሳወቅ ነው። ግንኙነታችሁ እንደማያዛልቅ የተሰማሽ ለምን እንደሆነ በግልጽ ንገሪው። ድክመቶቹን መዘክዘክ ወይም የትችት መዓት ማዥጎድጎድ አያስፈልግሽም። “አንተ በፍጹም . . . አታደርግም” ወይም “አንተ መቼም ቢሆን . . . አታውቅም” በማለት ጣትሽን እሱ ላይ ከመቀሰር ይልቅ “እኔ የምፈልገው . . . ሰው ነው” ወይም “ግንኙነታችንን ማቆም እንደሚገባን የሚሰማኝ . . . ምክንያት ነው” እንደሚሉት ባሉ ምን እንደሚሰማሽ ለመግለጽ በሚያስችሉ ቃላት መጠቀም የተሻለ ይሆናል።

      ይህ የምትወላውይበት ጊዜ አይደለም፤ ጓደኛሽ ሐሳብሽን እንዲያስቀይርሽ ልትፈቅጂ አይገባም። ግንኙነታችሁን ለማቆም የወሰንሽው አጥጋቢ ምክንያት ስላለሽ መሆኑን መዘንጋት የለብሽም። በመሆኑም ጓደኛሽ አሳማኝ የሚመስሉ ነጥቦችን በመደርደር ውሳኔሽን እንዳያስቀይርሽ ተጠንቀቂ። ሎሪ የተባለች አንዲት ወጣት እንዲህ ብላለች፦ “ከቀድሞ የወንድ ጓደኛዬ ጋር የነበረኝን ግንኙነት ካቆምኩ በኋላ በተገናኘን ቁጥር በጣም እንደተጎዳ የሚያስመስል ነገር ያደርግ ነበር። እንዲህ የሚያደርገው እንዳዝንለት ብሎ እንደነበረ ይሰማኛል። በእርግጥ አዝኜለት ነበር፤ ሆኖም ይህ ድርጊቱ አቋሜን እንዳላላ አላደረገኝም።” አንቺም እንደ ሎሪ ምን እንደምትፈልጊ ማወቅ ይኖርብሻል። ከአቋምሽ ፍንክች አትበይ። ቃልሽ አይደለም ከሆነ አይደለም ይሁን።​—ያዕቆብ 5:12

      መለያየት የሚያስከትለውን ጉዳት መቋቋም

      ከጓደኛሽ ጋር ከተለያየሽ በኋላ ለተወሰነ ጊዜ በጣም ብትረበሺ ሊገርምሽ አይገባም። ምናልባትም “ዐንገቴን ደፋሁ፤ ጐበጥሁም፤ ቀኑንም ሙሉ በትካዜ ተመላለስሁ” በማለት እንደተናገረው መዝሙራዊ ይሰማሽ ይሆናል። (መዝሙር 38:6) አሳቢ የሆኑ አንዳንድ ጓደኞችሽ ለወንድ ጓደኛሽ ሌላ ዕድል እንድትሰጪው ሊያበረታቱሽ ይሞክሩ ይሆናል። ሆኖም ተጠንቀቂ! ዞሮ ዞሮ መዘዙ የሚተርፈው ለአንቺ እንጂ ለጓደኞችሽ እንዳልሆነ ማወቅ አለብሽ። በተከሰተው ነገር ውስጥሽ ቢያዝንም እንኳ በአቋምሽ ለመጽናት መፍራት የለብሽም።

      በመለያየታችሁ የተጎዳው ስሜትሽ ውሎ አድሮ መጠገኑ አይቀርም። እስከዚያው ድረስ ግን ሁኔታውን ለመቋቋም የሚያስችሉሽን እንደሚከተሉት ያሉ ጠቃሚ እርምጃዎች ለምን አትወስጂም?

      ለምታምኚው ሰው ስሜትሽን አውጥተሽ ተናገሪ።c (ምሳሌ 15:22) ስለ ጉዳዩ ወደ ይሖዋ ጸልዪ። (መዝሙር 55:22) ራስሽን በሥራ አስጠምጂ። (1 ቆሮንቶስ 15:58) ከሌሎች ራስሽን እንዳታገዪ ተጠንቀቂ! (ምሳሌ 18:1 የ1954 ትርጉም) ዛሬ ነገ ሳትዪ ከሚያንጹሽ ሰዎች ጋር ወዳጅነትሽን አጠናክሪ። አእምሮሽ አዎንታዊ በሆኑ ነገሮች ላይ እንዲያተኩር አድርጊ።​—ፊልጵስዩስ 4:8

      አንድ ቀን ሌላ ጓደኛ ማግኘትሽ አይቀርም። በዚህ ጊዜ ከአሁኑ የተሻለ ሚዛናዊ አመለካከት እንደሚኖርሽ ምንም ጥርጥር የለውም። ምናልባት በዚያ ወቅት “ይህ ሰው ይሆነኛል?” ለሚለው ጥያቄ አዎን የሚል መልስ ትሰጪ ይሆናል!

      ተጨማሪ ሐሳብ ለማግኘት የዚህን መጽሐፍ ጥራዝ 1 ምዕራፍ 31 ተመልከት

      በሚቀጥለው ምዕራፍ

      መጠናናት ጀምራችሁ ከሆነ አንዳችሁ ለሌላው ፍቅራችሁን በምትገልጹበት ወቅት እስከምን ድረስ መሄድ እንደምትችሉ መወሰን የምትችሉት እንዴት ነው?

      [የግርጌ ማስታወሻዎች]

      a በዚህ ምዕራፍ ውስጥ የተጠቀሱት ነጥቦች ለሁለቱም ፆታዎች ይሠራሉ።

      b ከዚህም በተጨማሪ ስለ ራስሽ ይበልጥ ለማወቅ በምዕራፍ 1 ላይ “ለማግባት ዝግጁ ነህ?” በሚለው ንዑስ ርዕስ ሥር ከቀረቡት ጥያቄዎች አኳያ ራስሽን መመርመር ትችያለሽ።

      c ወላጆችሽ ወይም ሌሎች የጎለመሱ ሰዎች ለምሳሌ ክርስቲያን ሽማግሌዎች ሊረዱሽ ይችላሉ። ምናልባትም ወጣት በነበሩበት ወቅት ተመሳሳይ ነገር አጋጥሟቸው እንደነበር ይነግሩሽ ይሆናል።

      ቁልፍ ጥቅስ

      “ሕፃን እንኳ ጠባዩ ንጹሕና ቅን መሆኑ፣ ከአድራጎቱ ይታወቃል።”​—ምሳሌ 20:11

      ጠቃሚ ምክር

      አንዳችሁ የሌላውን ባሕርያት ለማወቅ በሚያስችሏችሁ እንቅስቃሴዎች ተካፈሉ፦

      ● የአምላክን ቃል አብራችሁ አጥኑ።

      ● በጉባኤ ስብሰባዎች ተሳትፎ ስታደርጉና አብራችሁ ስታገለግሉ አንዳችሁ የሌላውን ባሕርይ ለማስተዋል ሞክሩ።

      ● በመንግሥት አዳራሽ ጽዳትና ግንባታ ተካፈሉ።

      ይህን ታውቅ ነበር?

      በተደጋጋሚ የተደረጉ ጥናቶች እንደሚያሳዩት የተለያየ ሃይማኖት ያላቸው ሰዎች የሚመሠርቱት ጋብቻ በፍቺ የማክተሙ አጋጣሚ በጣም ሰፊ ነው።

      ላደርጋቸው ያሰብኳቸው ነገሮች

      የማያምን ሰው ወድጄ ከሆነ እንዲህ አደርጋለሁ፦ ․․․․․

      የወንድ ጓደኛዬ ምን ዓይነት ስም እንዳተረፈ ለማወቅ እንዲህ አደርጋለሁ፦ ․․․․․

      ከዚህ ርዕሰ ጉዳይ ጋር በተያያዘ ወላጆቼን ልጠይቃቸው የምፈልገው ነገር ․․․․․

      ምን ይመስልሃል?

      ● በትዳር ውስጥ ሊጠቅሙ የሚችሉ ምን ጥሩ ባሕርያት አሏችሁ?

      ● የትዳር ጓደኛችሁ የሚሆነው ሰው የትኞቹ አስፈላጊ ባሕርያት እንዲኖሩት ትፈልጋላችሁ?

      ● እምነታችሁን የማይጋራ ሰው ብታገቡ ምን ችግሮች ሊያጋጥሟችሁ ይችላሉ?

      ● ስለ ጓደኛችሁ ባሕርይና ምግባር እንዲሁም ስላተረፈው ስም ማወቅ የምትችሉባቸው አንዳንድ መንገዶች የትኞቹ ናቸው?

      [በገጽ 37 ላይ የሚገኝ የተቀነጨበ ሐሳብ]

      የፍቅር ጓደኛችሁ ቤተሰቡን የሚይዝበት መንገድ ወደፊት እናንተን እንዴት እንደሚይዛችሁ ይጠቁማል።”​—ቶኒ

      [በገጽ 34 ላይ የሚገኝ ሣጥን]

      “አቻ ባልሆነ መንገድ አትጠመዱ”

      “ከማያምኑ ጋር አቻ ባልሆነ መንገድ አትጠመዱ።” ወጣቶች በ⁠2 ቆሮንቶስ 6:14 ላይ የሚገኘው ይህ የመጽሐፍ ቅዱስ መመሪያ ጠቃሚ እንደሆነ ይሰማቸው ይሆናል። ያም ቢሆን አንዳንዶች የማያምን ሰው ሊማርካቸው ይችላል። ምክንያቱ ምንድን ነው? አንዳንድ ጊዜ የሚማርካቸው የግለሰቡ መልክ ብቻ ሊሆን ይችላል። ማርክ የተባለ አንድ ወጣት እንዲህ ብሏል፦ “በስፖርት ክፍለ ጊዜ ሁሌ የማያት አንዲት ልጅ ነበረች። ልጅቷ ከእኔ ጋር ለማውራት የማታደርገው ጥረት አልነበረም። በመሆኑም ከእሷ ጋር ጓደኝነት መጀመር በጣም ቀላል ነበር።”

      አንድ ወጣት የራሱን ፍላጎት በሚገባ የሚያውቅና የሚከተላቸው መንፈሳዊ መመሪያዎች ትክክል እንደሆኑ የሚተማመን ከሆነ ብሎም በስሜቱ ከመነዳት ይልቅ በሳል አስተሳሰብ ካዳበረ ምን ዓይነት ውሳኔ ማድረግ እንዳለበት ያውቃል። አንድ የማያምን ሰው የቱንም ያህል ቆንጆና የደስ ደስ ያለው ቢሆን ወይም ምንም ያህል ጨዋ ቢመስል ከአምላክ ጋር ያላችሁን ወዳጅነት ለማጠናከር ሊረዳችሁ እንደማይችል ምንም ጥርጥር የለውም።​—ያዕቆብ 4:4

      እርግጥ ነው፣ ከማያምን ሰው ጋር የፍቅር ጓደኝነት መሥርታችሁ ከሆነ ግንኙነቱን ማቆም ቀላል ላይሆን ይችላል፤ ሲንዲ የተባለች ወጣት እንዲህ ዓይነት ሁኔታ አጋጥሟት ያውቃል። “በየቀኑ አለቅስ ነበር” ብላለች። “በክርስቲያናዊ ስብሰባዎችም ላይ እንኳ ሳይቀር ነጋ ጠባ ስለ ልጁ አስብ ነበር። በጣም እወደው ስለነበር በወቅቱ እሱን ከማጣ ሞቴን እመርጥ ነበር።” ሆኖም ሲንዲ ከማያምን ሰው ጋር የፍቅር ጓደኝነት መጀመሯ ተገቢ እንዳልሆነ እናቷ የሰጠቻት ምክር ጥበብ ያዘለ መሆኑን ለመገንዘብ ብዙ ጊዜ አልወሰደባትም። “ከእሱ ጋር የነበረኝን ግንኙነት ማቆሜ ተገቢ ነበር። ይሖዋ የሚያስፈልገኝን እንደሚያሟላልኝ ምንም አልጠራጠርም” ብላለች።

      እናንተም እንደ ሲንዲ ዓይነት ሁኔታ አጋጥሟችኋል? ከሆነ ሁኔታውን ለማስተካከል ብቻችሁን መታገል አያስፈልጋችሁም! ጉዳዩን ለወላጆቻችሁ ማማከር ትችላላችሁ። ጂም የተባለ ወጣት በትምህርት ቤቱ ካለች አንዲት ልጅ ጋር ፍቅር ይዞት በነበረበት ወቅት እንዲህ አድርጓል። “ወላጆቼ እንዲረዱኝ ጠየቅዃቸው። ለእሷ የነበረኝን የፍቅር ስሜት እንዳሸንፍ የረዳኝ ትልቁ ነገር እነሱን ማማከሬ ነበር” ብሏል። የጉባኤ ሽማግሌዎችም ሊረዷችሁ ይችላሉ። ታዲያ ወደ አንዳቸው ቀርባችሁ ስላጋጠማችሁ ሁኔታ ለምን አትነግሯቸውም?​—ኢሳይያስ 32:1, 2

      [በገጽ 39 ላይ የሚገኝ ሣጥን/​ሥዕል]

      የመልመጃ ሣጥን

      ጥሩ ባል ይሆነኛል?

      ማንነት

      ◻ ያለውን ሥልጣን የሚጠቀምበት እንዴት ነው?​—ማቴዎስ 20:25, 26

      ◻ ምን ግቦች አሉት?​—1 ጢሞቴዎስ 4:15

      ◻ እነዚህ ግቦች ላይ ለመድረስ አሁን ጥረት እያደረገ ነው?​—1 ቆሮንቶስ 9:26, 27

      ◻ ቤተሰቡን የሚይዘው እንዴት ነው?​—ዘፀአት 20:12

      ◻ ጓደኞቹ እነማን ናቸው?​—ምሳሌ 13:20

      ◻ ማውራት የሚቀናው ስለ ምንድን ነው?​—ሉቃስ 6:45

      ◻ ለገንዘብ ምን አመለካከት አለው?​—ዕብራውያን 13:5, 6

      ◻ ምን ዓይነት መዝናኛ ይወዳል?​—መዝሙር 97:10

      ◻ ለይሖዋ ያለውን ፍቅር የሚያሳየው እንዴት ነው?​—1 ዮሐንስ 5:3

      ጠቃሚ ባሕርያት

      ◻ ታታሪ ነው?​—ምሳሌ 6:9-11

      ◻ ገንዘብ አያያዝ ይችላል?​—ሉቃስ 14:28

      ◻ ጥሩ ስም አትርፏል?​—የሐዋርያት ሥራ 16:1, 2

      ◻ ለሌሎች አሳቢ ነው?​—ፊልጵስዩስ 2:4

      አደገኛ ምልክቶች

      ◻ ግልፍተኛ ነው?​—ምሳሌ 22:24

      ◻ የፆታ ብልግና እንድንፈጽም ለማግባባት ይሞክራል?​—ገላትያ 5:19

      ◻ በሌሎች ላይ አካላዊ ጥቃት ይሰነዝራል? ወይም ስሜት የሚያቆስል ነገር የመናገር ልማድ አለው?​—ኤፌሶን 4:31

      ◻ ካልጠጣ በቀር የተዝናና አይመስለውም?​—ምሳሌ 20:1

      ◻ ቀናተኛና ራስ ወዳድ ነው?​—1 ቆሮንቶስ 13:4, 5

      [በገጽ 40 ላይ የሚገኝ ሣጥን/​ሥዕል]

      የመልመጃ ሣጥን

      ጥሩ ሚስት ትሆነኛለች?

      ማንነት

      ◻ በቤተሰብም ሆነ በጉባኤ ውስጥ ለሥልጣን ተገዢ መሆኗን የምታሳየው እንዴት ነው?​—ኤፌሶን 5:21, 22

      ◻ ቤተሰቧን የምትይዘው እንዴት ነው?​—ዘፀአት 20:12

      ◻ ጓደኞቿ እነማን ናቸው?​—ምሳሌ 13:20

      ◻ ማውራት የሚቀናት ስለ ምንድን ነው?​—ሉቃስ 6:45

      ◻ ለገንዘብ ምን አመለካከት አላት?​—1 ዮሐንስ 2:15-17

      ◻ ምን ግቦች አሏት?​—1 ጢሞቴዎስ 4:15

      ◻ እነዚህ ግቦች ላይ ለመድረስ አሁን ጥረት እያደረገች ነው?​—1 ቆሮንቶስ 9:26, 27

      ◻ ምን ዓይነት መዝናኛ ትወዳለች?​—መዝሙር 97:10

      ◻ ለይሖዋ ያላትን ፍቅር የምታሳየው እንዴት ነው?​—1 ዮሐንስ 5:3

      ጠቃሚ ባሕርያት

      ◻ ታታሪ ናት?​—ምሳሌ 31:17, 19, 21, 22, 27

      ◻ ገንዘብ አያያዝ ትችላለች?​—ምሳሌ 31:16, 18

      ◻ ጥሩ ስም አትርፋለች?​—ሩት 3:11

      ◻ ለሌሎች አሳቢ ናት?​—ምሳሌ 31:20

      አደገኛ ምልክቶች

      ◻ ጨቅጫቃ ናት?​—ምሳሌ 21:19

      ◻ የፆታ ብልግና እንድንፈጽም ለማግባባት ትሞክራለች?​—ገላትያ 5:19

      ◻ ስሜት የሚያቆስል ነገር የመናገር ልማድ አላት? ወይም በሌሎች ላይ አካላዊ ጥቃት ትሰነዝራለች?​—ኤፌሶን 4:31

      ◻ ካልጠጣች በቀር የተዝናናች አይመስላትም?​—ምሳሌ 20:1

      ◻ ቀናተኛና ራስ ወዳድ ናት?​—1 ቆሮንቶስ 13:4, 5

      [በገጽ 30 ላይ የሚገኝ ሥዕል]

      ማንኛውም ጫማ ልክሽ እንደማይሆን ሁሉ ጥሩ የትዳር ጓደኛ የሚሆንሽም ማንኛውም ሰው አይደለም

      [በገጽ 31 ላይ የሚገኝ ሥዕል]

      መኪና በምትመርጥበት ጊዜ ውጫዊ መልኩን ብቻ ከመመልከት አልፈህ ውስጡን መፈተሽ አስፈላጊ እንደሆነ ይሰማሃል? የትዳር ጓደኛ መምረጥስ ከዚህ ይበልጥ በቁም ነገር ሊታይ የሚገባው ጉዳይ አይደለም?

  • ገደቡን አለፈ የሚባለው መቼ ነው?
    ወጣቶች የሚጠይቋቸው ጥያቄዎችና ተግባራዊ መሆን የሚችሉ መልሶች፣ ጥራዝ 2
    • ምዕራፍ 4

      ገደቡን አለፈ የሚባለው መቼ ነው?

      እውነት ወይስ ሐሰት?

      መጠናናት የጀመሩ ሁለት ሰዎች በምንም ተአምር መነካካት የለባቸውም።

      □ እውነት

      □ ሐሰት

      አንድ ወንድና አንዲት ሴት የግብረ ሥጋ ግንኙነት ባይፈጽሙም ዝሙት እንደፈጸሙ የሚያስቆጥር ነገር ሊያደርጉ ይችላሉ።

      □ እውነት

      □ ሐሰት

      መጠናናት የጀመሩ ወንድና ሴት በመተቃቀፍ፣ በመደባበስ እና በመሳሳም ፍቅራቸውን ካልገለጹ ይዋደዳሉ ማለት አይቻልም።

      □ እውነት

      □ ሐሰት

      ይህን ጉዳይ ብዙ ጊዜ አስበህበት እንደሚሆን ምንም ጥርጥር የለውም። ከአንዲት ወጣት ጋር እየተጠናናህ ከሆነ ፍቅራችሁን የምትገልጹበት መንገድ ገደቡን አለፈ የሚባለው መቼ እንደሆነ ማወቅ አስቸጋሪ ሊሆንባችሁ ይችላል። እስቲ እውነት ወይም ሐሰት ብለህ እንድትመልስ ከላይ የቀረቡትን ሦስት ጥያቄዎች እንመርምር፤ ከዚያም “ገደቡን አለፈ የሚባለው መቼ ነው?” ለሚለው ጥያቄ መልስ ለማግኘት የአምላክ ቃል እንዴት እንደሚረዳን እንመለከታለን።

      ● መጠናናት የጀመሩ ሁለት ሰዎች በምንም ተአምር መነካካት የለባቸውም።

      ሐሰት። መጽሐፍ ቅዱስ ሥርዓት ባለውና ተገቢ በሆነ መልኩ ፍቅርን መግለጽን አይከለክልም። ለምሳሌ ያህል፣ በጣም ስለሚዋደዱ አንዲት ሱላማጢስ ወጣትና አንድ እረኛ የሚናገር ታሪክ በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ እናገኛለን። እነዚህ ወጣቶች የሚጠናኑት ሥነ ምግባራዊ ንጽሕናቸውን ጠብቀው ነበር። ያም ሆኖ ከመጋባታቸው በፊትም ቢሆን በአንዳንድ መንገዶች አንዳቸው ለሌላው ፍቅራቸውን ይገልጹ እንደነበር ከታሪኩ በግልጽ መመልከት ይቻላል። (ማሕልየ መሓልይ 1:2፤ 2:6፤ 8:5) በዛሬው ጊዜም ለመጋባት የወሰኑ አንድ ወንድና ሴት ንጹሕ በሆነ መንገድ ፍቅራቸውን መግለጻቸው ተገቢ እንደሆነ ይሰማቸው ይሆናል።a

      ይሁንና የሚጠናኑ ሰዎች በዚህ ረገድ ከፍተኛ ጥንቃቄ ማድረግ ይኖርባቸዋል። መሳሳም፣ መተቃቀፍ ወይም የፆታ ስሜትን የሚቀሰቅስ ማንኛውንም ነገር ማድረግ የፆታ ብልግና ወደ መፈጸም ሊያመራ ይችላል። አንድ ወንድና አንዲት ሴት እንዲህ ያሉትን የፍቅር መግለጫዎች የሚያሳዩት በንጹሕ ልቦና ተነሳስተው ቢሆንም እንኳ ስሜታቸውን መቆጣጠር ተስኗቸው በቀላሉ የፆታ ብልግና ሊፈጽሙ ይችላሉ።​—ቆላስይስ 3:5

      ● አንድ ወንድና አንዲት ሴት የግብረ ሥጋ ግንኙነት ባይፈጽሙም ዝሙት እንደፈጸሙ የሚያስቆጥር ነገር ሊያደርጉ ይችላሉ።

      እውነት። በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ “ዝሙት” ተብሎ የተተረጎመው ፖርኒያ የተባለው የግሪክኛ ቃል ሰፊ ትርጉም አለው። ይህ ቃል ባልተጋቡ ሰዎች መካከል የሚፈጸመውን ማንኛውንም ዓይነት የፆታ ግንኙነትና የፆታ ብልቶችን ተገቢ ባልሆነ መንገድ መጠቀምን ያመለክታል። በመሆኑም ዝሙት የሚለው ቃል የሚያመለክተው የግብረ ሥጋ ግንኙነት መፈጸምን ብቻ ሳይሆን በአፍና በፊንጢጣ የፆታ ግንኙነት እንደ መፈጸምና የሌላውን የፆታ ብልት እንደ ማሻሸት የመሳሰሉትን ድርጊቶች ጭምር ነው።

      መጽሐፍ ቅዱስ የሚያወግዘው ዝሙት መፈጸምን ብቻ አይደለም። ሐዋርያው ጳውሎስ እንዲህ ሲል ጽፏል፦ “የሥጋ ሥራዎች የታወቁ ናቸው፤ እነሱም፦ ዝሙት፣ ርኩሰት፣ ብልግና [ናቸው።] . . . እንዲህ ያሉትን ነገሮች የሚፈጽሙ የአምላክን መንግሥት አይወርሱም።”​—ገላትያ 5:19-21

      “ርኩሰት” ምንድን ነው? “ርኩሰት” ተብሎ የተተረጎመው የግሪክኛ ቃል በንግግርም ሆነ በድርጊት የጎደፉ መሆንን ያመለክታል። እጅን የሌላው ሰውነት ውስጥ ማስገባት፣ የሌላውን ልብስ ለማወላለቅ መሞከር ወይም ሊነኩ የማይገባቸውን የሰውነት ክፍሎች ለምሳሌ ጡትን መደባበስ ርኩስ ድርጊት እንደሆነ ምንም ጥርጥር የለውም። መጽሐፍ ቅዱስ፣ ጡትን መደባበስን የሚገልጸው በተጋቡ ሰዎች መካከል ብቻ ከሚፈጸሙ ድርጊቶች እንደ አንዱ አድርጎ ነው።​—ምሳሌ 5:18, 19

      አንዳንድ ወጣቶች ያለምንም እፍረት የአምላክን መሥፈርቶች ይጥሳሉ። ሆን ብለው ገደቡን ያልፋሉ፤ አሊያም ስግብግብ በመሆን ካገኙት ሰው ሁሉ ጋር የፆታ ርኩሰት ለመፈጸም ይፈልጋሉ። እንደዚህ የሚያደርጉ ወጣቶች ሐዋርያው ጳውሎስ “ብልግና” ብሎ የጠራውን ድርጊት ፈጽመዋል ሊባል ይችላል። “ብልግና” ተብሎ የተተረጎመው የግሪክኛ ቃል ‘ጋጠወጥነት፣ ልቅነት፣ ስድነት፣ ገደብ የለሽ የፆታ ፍላጎት’ የሚል ፍቺ አለው። “የሥነ ምግባር ስሜታቸው ስለደነዘዘ በስግብግብነት ማንኛውንም ዓይነት ርኩሰት ለመፈጸም ራሳቸውን ለብልግና አሳልፈው ሰጥተዋል” እንደተባሉት ሰዎች መሆን እንደማትፈልግ ግልጽ ነው።​—ኤፌሶን 4:17-19

      ● መጠናናት የጀመሩ ወንድና ሴት በመተቃቀፍ፣ በመደባበስ እና በመሳሳም ፍቅራቸውን ካልገለጹ ይዋደዳሉ ማለት አይቻልም።

      ሐሰት። አንዳንዶች ከሚያስቡት በተቃራኒ ተገቢ ያልሆኑ የፍቅር መግለጫዎች በአንድ ወንድና በአንዲት ሴት መካከል ያለው ግንኙነት እንዲጠናከር አያደርጉም። ከዚህ ይልቅ በመካከላቸው መከባበርና መተማመን እንዳይኖር ያደርጋሉ። ሎራ የገጠማትን ሁኔታ እንመልከት። እንዲህ ብላለች፦ “አንድ ቀን እናቴ ባልነበረችበት ሰዓት የወንድ ጓደኛዬ ቴሌቪዥን ለማየት በሚል ሰበብ ቤታችን መጣ። መጀመሪያ ላይ እጄን ብቻ ነበር የያዘኝ። ይሁንና ሳላስበው ሰውነቴን ይደባብሰኝ ጀመር። እጁን እንዲሰበስብ ብነግረው ተበሳጭቶ ሊሄድ ይችላል ብዬ ስላሰብኩ ‘ተው’ እንዳልለው ፈራሁ።”

      የሎራ የወንድ ጓደኛ ከልቡ የሚወዳት ይመስልሻል? ወይስ የሚፈልገው የራሱን ስሜት ለማርካት ብቻ ነበር? አንድ ሰው ርኩሰት እንድትፈጽሙ ሊያነሳሳሽ የሚሞክር ከሆነ ከልቡ ይወድሻል ማለት ይቻላል?

      አንድ ወጣት፣ የሴት ጓደኛው ካገኘችው ክርስቲያናዊ ሥልጠና ጋር የሚጋጭና ሕሊናዋን የሚያቆሽሽ ድርጊት እንድትፈጽም የሚገፋፋት ከሆነ የአምላክን ሕግ የሚጥስ ከመሆኑም በላይ ለእሷ ያለው ፍቅር እውነተኛ መሆኑ አጠያያቂ እንዲሆን ያደርጋል። እንዲህ ያለው ድርጊት እንዲፈጸምባት የምትፈቅድ ወጣትም ብትሆን መጠቀሚያ እየሆነች ነው። ከዚህ የከፋው ደግሞ ርኩሰት መፈጸሟ ነው፤ አልፎ ተርፎም ዝሙት ልትፈጽም ትችላለች።b​—1 ቆሮንቶስ 6:9, 10

      ግልጽ የሆኑ ገደቦችን አብጁ

      እየተጠናናችሁ ከሆነ ተገቢ ያልሆኑ የፍቅር መግለጫዎችን ከማሳየት መቆጠብ የምትችሉት እንዴት ነው? ግልጽ የሆኑ ገደቦችን አስቀድሞ ማበጀት የጥበብ እርምጃ ነው። ምሳሌ 13:10 (NW) “እርስ በርስ በሚመካከሩ ሰዎች ዘንድ . . . ጥበብ አለ” ይላል። ተገቢ የሚባለው የፍቅር መግለጫ ምን ዓይነት እንደሆነ አስቀድማችሁ ተነጋገሩ። ስሜታችሁ ከተነሳሳ በኋላ ገደብ ለማበጀት መሞከር ቤታችሁ በእሳት ቢያያዝ እሳቱ ከቁጥጥር ውጭ እስኪሆን ድረስ እርምጃ ሳትወስዱ እንደመቆየት ይሆናል።

      እርግጥ ነው፣ በተለይ መጠናናት እንደጀመራችሁ አካባቢ እንዲህ ያለውን ውይይት ማድረግ ከባድ እንዲያውም የሚያሳፍር ሊሆንባችሁ ይችላል። ሆኖም አስቀድማችሁ ገደብ ማበጀታችሁ በኋላ ላይ ከባድ ችግር ውስጥ እንዳትገቡ ከፍተኛ አስተዋጽኦ ይኖረዋል። ጥበብ የሚንጸባረቅባቸው ገደቦች ማበጀታችሁ እሳት ሊያስነሱ የሚችሉ ሁኔታዎችን አስቀድሞ ከማስወገድ ጋር ሊመሳሰል ይችላል። ከዚህም በተጨማሪ ስለ እነዚህ ጉዳዮች መወያየት መቻላችሁ ግንኙነታችሁ የሚያዛልቅ መሆኑን ይጠቁማል። ደግሞም በጋብቻ ውስጥ በፆታ ግንኙነት ለመደሰት ራስን መግዛትንና ትዕግሥትን ማዳበር እንዲሁም ራስ ወዳድነትን ማስወገድ እጅግ አስፈላጊ ነው።​—1 ቆሮንቶስ 7:3, 4

      ከአምላክ መሥፈርቶች ጋር በሚስማማ መንገድ መኖር ቀላል እንዳልሆነ አይካድም። ያም ቢሆን ይሖዋ በሚሰጥህ ምክር መተማመን ትችላለህ። በኢሳይያስ 48:17 ላይ ይሖዋ “የሚበጅህ ምን እንደ ሆነ የማስተምርህ፣ መሄድ በሚገባህ መንገድ የምመራህ ነኝ” በማለት ስለ ራሱ ተናግሯል። ይሖዋ ከሁሉ የተሻለውን ነገር እንድታገኝ ይመኝልሃል!

      ተጨማሪ ሐሳብ ለማግኘት የዚህን መጽሐፍ ጥራዝ 1 ምዕራፍ 24 ተመልከት

      በሚቀጥለው ምዕራፍ

      አንዲት ወጣት ድንግልናዋን ጠብቃ ስለቆየች ችግር አለባት ማለት አይደለም። እንዲያውም እንዲህ ማድረጓ የጥበብ አካሄድ ነው። እንዲህ የምንልበትን ምክንያት እስቲ እንመልከት።

      [የግርጌ ማስታወሻዎች]

      a በአንዳንድ የዓለም ክፍሎች ያልተጋቡ ወንድና ሴት በሰዎች ፊት ፍቅራቸውን መግለጻቸው ሌሎችን ቅር የሚያሰኝ ከመሆኑም ሌላ እንደ ነውር ይቆጠራል። ክርስቲያኖች ሌሎችን የሚያሰናክል ነገር ላለማድረግ መጠንቀቅ አለባቸው።​—2 ቆሮንቶስ 6:3

      b በዚህ አንቀጽ ላይ የተጠቀሱት ነጥቦች ለሁለቱም ፆታዎች እንደሚሠሩ ግልጽ ነው።

      ቁልፍ ጥቅስ

      “ፍቅር . . . ተገቢ ያልሆነ ምግባር አያሳይም።”​—1 ቆሮንቶስ 13:4, 5

      ጠቃሚ ምክር

      ከፍቅር ጓደኛችሁ ጋር ለመጠናናት ስትገናኙ ሌሎችም እንዲኖሩ አድርጉ፤ አሊያም ቢያንስ አንድ ሰው አብሯችሁ መሆን ይኖርበታል። ችግር ውስጥ እንድትገቡ የሚያደርጉ ሁኔታዎችን አስወግዱ፤ ለምሳሌ የቆመ መኪና ወይም ቤት ውስጥ ብቻችሁን አትሁኑ።

      ይህን ታውቅ ነበር?

      ተጫጭታችሁ ከሆነ ከፆታ ግንኙነት ጋር የተያያዙ አንዳንድ ጉዳዮችን በግልጽ መነጋገር ያስፈልጋችኋል። ይሁን እንጂ በስልክ ስታወሩም ሆነ የጽሑፍ መልእክት ስትላላኩ የፆታ ስሜትን ለመቀስቀስ የታሰቡ ቃላትን መጠቀም ርኩሰት ነው።

      ላደርጋቸው ያሰብኳቸው ነገሮች

      የሥነ ምግባር ብልግና ወደ መፈጸም ሊመሩ የሚችሉ ሁኔታዎችን ለማስወገድ እንዲህ አደርጋለሁ፦ ․․․․․

      የፍቅር ጓደኛዬ ተገቢ ያልሆነ ድርጊት እንድንፈጽም ሊገፋፋኝ ቢሞክር እንዲህ አደርጋለሁ፦ ․․․․․

      ከዚህ ርዕሰ ጉዳይ ጋር በተያያዘ ወላጆቼን ልጠይቃቸው የምፈልገው ነገር ․․․․․

      ምን ይመስልሃል?

      ● ከፍቅር ጓደኛችሁ ጋር አብራችሁ ስትሆኑ በመካከላችሁ በሚኖረው አካላዊ ቅርበት ረገድ ምን ዓይነት ገደብ ታበጃላችሁ?

      ● በዝሙት፣ በርኩሰትና፣ በብልግና መካከል ያለውን ልዩነት አብራራ።

      [በገጽ 46 ላይ የሚገኝ የተቀነጨበ ሐሳብ]

      “እኔና እጮኛዬ ሥነ ምግባራዊ ንጽሕናችንን ጠብቀን ስለመቆየት የሚገልጹ በመጽሐፍ ቅዱስ ላይ የተመሠረቱ ጽሑፎችን አብረን አንብበናል። እነዚህ ጽሑፎች ንጹሕ ሕሊና እንድንይዝ እንደረዱን ይሰማናል።”​—ለቲሺያ

      [በገጽ 44 ላይ የሚገኝ ሣጥን]

      ገደቡን አልፋችሁ ብትሄዱስ?

      ተገቢ ያልሆነ ነገር ከፈጸማችሁ ምን ማድረግ አለባችሁ? ችግሩን በራሳችሁ እንደምታስተካክሉት በማሰብ ራሳችሁን አታታልሉ። አንዲት ወጣት እንዲህ ብላለች፦ “‘ሁለተኛ እንዲህ እንዳናደርግ እርዳን’ ብዬ እጸልይ ነበር። ገደቡን ሳናልፍ በመመላለስ ረገድ አንዳንድ ጊዜ ቢሳካልንም የተሳሳትንባቸው ወቅቶችም ነበሩ።” ስለዚህ ጉዳዩን ለወላጆቻችሁ መንገር ያስፈልጋችኋል። መጽሐፍ ቅዱስም ‘የጉባኤ ሽማግሌዎችን እንድትጠሩ’ የሚያበረታታ ጠቃሚ ምክር ይሰጣል። (ያዕቆብ 5:14) እነዚህ ክርስቲያን እረኞች ከአምላክ ጋር ያላችሁን ግንኙነት ለማስተካከል የሚረዳችሁ ምክር፣ ተግሣጽና ወቀሳ ይሰጧችኋል።

      [በገጽ 47 ላይ የሚገኝ ሥዕል]

      ቤታችሁ በእሳት ቢያያዝ እርምጃ ለመውሰድ እሳቱ ከቁጥጥር ውጭ እስኪሆን ትጠብቃላችሁ? በፍቅር መግለጫዎች ረገድ ገደብ ለማበጀትም ስሜታችሁ እስኪነሳሳ መጠበቅ የለባችሁም

  • ድንግልናዬን መጠበቅ ያለብኝ ለምንድን ነው?
    ወጣቶች የሚጠይቋቸው ጥያቄዎችና ተግባራዊ መሆን የሚችሉ መልሶች፣ ጥራዝ 2
    • ምዕራፍ 5

      ድንግልናዬን መጠበቅ ያለብኝ ለምንድን ነው?

      “ከየአቅጣጫው የሚመጣው ተጽዕኖ ‘የፆታ ግንኙነት ምን እንደሚመስል ሞክሬ ባየው’ ብዬ እንዳስብ ያደርገኛል።”​—ኬሊ

      “የፆታ ግንኙነት ሳልፈጽም እስካሁን መቆየቴ ያሳፍረኛል።”​—ጆርደን

      “ዘንድሮም ድንግል ነሽ?”a እንዲህ ያለው ጥያቄ ሽምቅቅ እንድትዪ ያደርግሽ ይሆናል። በብዙ ቦታዎች አንዲት ወጣት ድንግል ከሆነች ችግር እንዳለባት ተደርጋ ትታያለች። ከዚህ አንጻር በርካታ ወጣቶች ገና በአሥራዎቹ ዕድሜ ውስጥ እያሉ የፆታ ግንኙነት የሚፈጽሙ መሆኑ ምንም አያስገርምም!

      ፍላጎታችሁና እኩዮቻችሁ የሚያሳድሩባችሁ ተጽዕኖ

      ክርስቲያን ከሆንሽ መጽሐፍ ቅዱስ ‘ከዝሙት እንድትርቂ’ የሚሰጠውን ማሳሰቢያ ታውቂያለሽ። (1 ተሰሎንቄ 4:3) ያም ሆኖ የፆታ ስሜትሽን መቆጣጠር አስቸጋሪ ሊሆንብሽ ይችላል። ፖል የተባለ ወጣት እንዲህ ሲል በግልጽ ተናግሯል፦ “አንዳንድ ጊዜ ከፆታ ግንኙነት ጋር የተያያዙ ሐሳቦች ያለ ምንም ምክንያት ወይም ሳልፈልግ ወደ አእምሮዬ ይመጣሉ።” አብዛኛውን ጊዜ እንዲህ ያለው ስሜት በተፈጥሮ ያለ ነገር ነው።

      ይሁንና ድንግል በመሆንሽ ጓደኞችሽ ነጋ ጠባ የሚያሾፉብሽና የሚነዘንዙሽ ከሆነ ሁኔታው ከባድ ነው። ለምሳሌ፣ አንድን ወጣት እኩዮቹ ‘የፆታ ግንኙነት የማትፈጽም ከሆነማ ወንድ ነኝ አትበል’ የሚሉት ቢሆንስ? አሊያም ደግሞ አንዲትን ወጣት ጓደኞቿ ‘የፆታ ግንኙነት ካልፈጸምሽ ምኑን ሴት ሆንሽው’ ቢሏትስ? ሔለን እንዲህ ብላለች፦ “እኩዮቻችሁ የፆታ ግንኙነት መፈጸም የሚያስደስትና ሁሉም ሰው የሚያደርገው ነገር እንደሆነ ይናገራሉ። ከዚህም ከዚያም ጋር ካልተኛችሁ ከሰው የተለያችሁ እንደሆናችሁ አድርገው ይቆጥሯችኋል።”

      ይሁንና ከጋብቻ በፊት የፆታ ግንኙነት ከመፈጸም ጋር በተያያዘ እኩዮችሽ የሚደብቁሽ ነገር አለ። ለምሳሌ ያህል፣ ከወንድ ጓደኛዋ ጋር የፆታ ግንኙነት የፈጸመች ማሪያ የተባለች አንዲት ወጣት እንዲህ በማለት ታስታውሳለች፦ “ድርጊቱን ከፈጸምኩ በኋላ በኀፍረትና በጥፋተኝነት ስሜት ተዋጥኩ። ራሴን ጠላሁት፤ የወንድ ጓደኛዬንም ጨርሶ ላየው አልፈለግኩም።” አብዛኞቹ ወጣቶች ባያውቁትም እንዲህ ዓይነቱ ሁኔታ ብዙ ጊዜ የሚያጋጥም ነው። እንደ እውነቱ ከሆነ ከጋብቻ በፊት የፆታ ግንኙነት መፈጸም ብዙውን ጊዜ የስሜት ሥቃይ የሚያስከትል ከመሆኑም ሌላ አስከፊ መዘዞች አሉት!

      ያም ሆኖ ሻንዳ የተባለች ወጣት “አምላክ በጋብቻ ውስጥ ካልሆነ በቀር የፆታ ግንኙነት መፈጸም እንደሌለባቸው እያወቀ ወጣቶች እንዲህ ዓይነት ፍላጎት እንዲኖራቸው ለምን አደረገ?” የሚል ጥያቄ አንስታለች። ይህ ጥሩ ጥያቄ ነው። እስቲ የሚከተሉትን ነጥቦች እንመልከት፦

      ከፆታ ፍላጎት ሌላ ኃይለኛ ስሜት አድሮብሽ አያውቅም? እንደሚያውቅ ምንም ጥርጥር የለውም። ይሖዋ አምላክ የፈጠረሽ የተለያየ ዓይነት ፍላጎትና ስሜት እንዲኖርሽ አድርጎ ነው።

      እንዲህ ያሉ ስሜቶች በውስጥሽ በተቀሰቀሱ ቁጥር ልታስተናግጃቸው ይገባል ማለት ነው? በፍጹም። ምክንያቱም አምላክ ሲፈጥርሽ ስሜትሽን የመቆጣጠር ችሎታም ሰጥቶሻል።

      ታዲያ ነጥቡ ምንድን ነው? አንዳንድ ስሜቶች በውስጥሽ እንዳይቀሰቀሱ ማድረግ አትችዪ ይሆናል፤ ሆኖም እነዚህን ፍላጎቶችሽን ከመፈጸም ራስሽን መግታት ትችያለሽ። እውነቱን ለመናገር፣ የፆታ ስሜትሽ በተቀሰቀሰ ቁጥር ፍላጎትሽን ለማርካት መነሳት አንድ ሰው ባናደደሽ ቁጥር ከመማታት ባልተናነሰ ስህተትና ቂልነት ነው።

      አምላክ የመራቢያ አካላችንን የሰጠን አላግባብ እንድንጠቀምበት አይደለም። መጽሐፍ ቅዱስ “ከእናንተ እያንዳንዱ የገዛ ራሱን ዕቃ እንዴት በቅድስናና በክብር መያዝ እንዳለበት [ሊያውቅ ይገባል]” ይላል። (1 ተሰሎንቄ 4:4) መጽሐፍ ቅዱስ “ለመውደድ ጊዜ አለው፤ ለመጥላትም ጊዜ አለው” ይላል። በተመሳሳይም የፆታ ፍላጎትን ለማርካትም ሆነ ይህን ከማድረግ ለመቆጠብ ጊዜ አለው። (መክብብ 3:1-8) በዚያም ሆነ በዚህ ስሜትሽን መቆጣጠር የምትችይው አንቺ ነሽ!

      ይሁን እንጂ አንዲት ወጣት በፌዝ መልክ “አሁንም ድንግል ነኝ እንዳትይኝ ብቻ” ብትልሽ ምን ማድረግ ትችያለሽ? በዚህ ጊዜ መደናገጥ የለብሽም። ዓላማዋ በአንቺ ላይ ማሾፍ ከሆነ “አዎ፣ አሁንም ድንግል ነኝ። ደግሞም ድንግል በመሆኔ ቅንጣት ታክል አላፍርም!” ብለሽ ልትመልሺላት ትችያለሽ። አሊያም “ይህ የግል ጉዳዬ ስለሆነ አንቺን አይመለከትሽም” ማለት ትችያለሽ።b (ምሳሌ 26:4፤ ቆላስይስ 4:6) በሌላ በኩል ግን እንዲህ ላለችሽ ወጣት ስለ አቋምሽ የበለጠ ልታስረጃት እንደሚገባ ይሰማሽ ይሆናል። ከሆነ በመጽሐፍ ቅዱስ ላይ የተመሠረተውን አቋምሽን በተመለከተ አንዳንድ ነገሮች ልትነግሪያት ትችያለሽ።

      አንዲት ወጣት በፌዝ መልክ “አሁንም ድንግል ነኝ እንዳትይኝ ብቻ” ብትልሽ ሌላስ ምን ልትያት ትችያለሽ? መልስሽን ከታች አስፍሪው።

      ․․․․․

      ውድ ስጦታ

      ሰዎች ከጋብቻ በፊት የፆታ ግንኙነት ቢፈጽሙ አምላክ ምን ይሰማዋል? ለአንድ ጓደኛሽ ስጦታ ገዝተሻል እንበል። ይሁንና ጓደኛሽ ስጦታውን ገና ሳትሰጫት ለማየት ጓጉታ ብትከፍተው ምን ይሰማሻል? በሁኔታው አትበሳጪም? አንቺም ከጋብቻ በፊት የፆታ ግንኙነት ብትፈጽሚ አምላክ ምን እንደሚሰማው ልትገምቺ ትችያለሽ። አምላክ ከሰጠሽ ስጦታ ማለትም ከፆታ ግንኙነት ደስታ ለማግኘት እስክታገቢ ድረስ እንድትቆዪ ይፈልጋል።​—ዘፍጥረት 1:28

      ‘ታዲያ የፆታ ስሜቴ እንዳያስቸግረኝ ምን ባደርግ ይሻለኛል?’ ብለሽ ታስቢ ይሆናል። በአጭር አነጋገር፣ ስሜትሽን መቆጣጠር መማር ይኖርብሻል። ደግሞም እንዲህ ለማድረግ የሚያስችል ብቃት አለሽ! ይሖዋ እንዲረዳሽ ጸልዪ። የአምላክ መንፈስ ራስን የመግዛት ባሕርይ ይበልጥ እንድታዳብሪ ሊረዳሽ ይችላል። (ገላትያ 5:22, 23) ይሖዋ “በቅንነት የሚሄዱትን፣ መልካም ነገር አይነፍጋቸውም” የሚለውን ጥቅስ አስታውሺ። (መዝሙር 84:11) ጎርደን የተባለ አንድ ወጣት እንዲህ ብሏል፦ “ከጋብቻ በፊት የፆታ ግንኙነት መፈጸም ያን ያህል መጥፎ እንዳልሆነ ማሰብ ከጀመርኩ እንዲህ ያለው ድርጊት በመንፈሳዊነቴ ላይ ስለሚያስከትለው ጉዳት አሰላስላለሁ፤ ይህም ኃጢአት በመፈጸም የማገኘው ደስታ የፈለገ ቢሆን ከይሖዋ ጋር ካለኝ ዝምድና ሊበልጥብኝ እንደማይችል እንድገነዘብ ያደርገኛል።”

      ድንግል መሆንሽ ችግር እንዳለብሽ የሚያሳይ አይደለም። ከዚህ በተቃራኒ ክብርን ዝቅ የሚያደርገውና የሚያሳፍረው ብሎም ጎጂ የሚሆነው የፆታ ብልግና መፈጸም ነው። በመሆኑም ዓለም የሚያናፍሰው ፕሮፓጋንዳ፣ ከመጽሐፍ ቅዱስ መሥፈርቶች ጋር በሚስማማ መንገድ መኖርሽ ስህተት እንደሆነ እንዲሰማሽ አያድርግሽ። ድንግልናሽን ጠብቀሽ መቆየትሽ ስሜታዊ ጉዳት እንዳይደርስብሽ የሚረዳሽ ከመሆኑም ሌላ ጤንነትሽን ለመጠበቅ ያስችልሻል። ከሁሉ በላይ ደግሞ ከአምላክ ጋር ያለሽ ዝምድና እንዳይበላሽ ይረዳሻል።

      ተጨማሪ ሐሳብ ለማግኘት የዚህን መጽሐፍ ጥራዝ 1 ምዕራፍ 24 ተመልከት

      [የግርጌ ማስታወሻዎች]

      a በዚህ ምዕራፍ ውስጥ የተጠቀሱት ነጥቦች ለሁለቱም ፆታዎች ይሠራሉ።

      b ኢየሱስ በአንድ ወቅት ሄሮድስ ጥያቄ ሲያቀርብለት ዝምታን እንደመረጠ መገለጹ ትኩረት የሚስብ ነው። (ሉቃስ 23:8, 9) ተገቢ ያልሆኑ ጥያቄዎች ሲቀርቡልን ብዙውን ጊዜ የተሻለው ነገር መልስ አለመስጠት ነው።

      ቁልፍ ጥቅስ

      “[አንድ ሰው] ድንግልናውን ጠብቆ ለመኖር በልቡ ከወሰነ . . . መልካም ያደርጋል።”​—1 ቆሮንቶስ 7:37

      ጠቃሚ ምክር

      አንዳንድ ወጣቶች እንደ አንቺ ዓይነት እምነት እንዳላቸው ቢናገሩም እንኳ ጠንካራ የሥነ ምግባር አቋም ከሌላቸው ከእነሱ ጋር ጓደኝነት ላለመመሥረት ተጠንቀቂ።

      ይህን ታውቅ ነበር?

      ልቅ የሆነ የፆታ ግንኙነት የመፈጸም ልማድ ያላቸው ሰዎች አብዛኛውን ጊዜ ካገቡም በኋላ ይህ አመላቸው አይለቃቸውም። በሌላ በኩል ደግሞ ከማግባታቸው በፊት ለአምላክ የሥነ ምግባር መሥፈርቶች ታማኝ የነበሩ ሰዎች ካገቡም በኋላ ለትዳር ጓደኛቸው ታማኝ የመሆናቸው አጋጣሚ ሰፊ ነው።

      ላደርጋቸው ያሰብኳቸው ነገሮች

      እስከማገባ ድረስ ድንግልናዬን ጠብቄ ለመቆየት እንድችል እንዲህ ማድረግ ያስፈልገኛል፦ ․․․․․

      ጓደኞቼ በአቋሜ እንዳልጸና የሚያስቸግሩኝ ከሆነ እንዲህ አደርጋለሁ፦ ․․․․․

      ከዚህ ርዕሰ ጉዳይ ጋር በተያያዘ ወላጆቼን ልጠይቃቸው የምፈልገው ነገር ․․․․․

      ምን ይመስልሃል?

      ● አንዳንዶች፣ ድንግል የሆኑ ወጣቶች ላይ የሚያሾፉባቸው ለምንድን ነው?

      ● ድንግልናን ጠብቆ መቆየት አስቸጋሪ ሊሆን የሚችለው ለምንድን ነው?

      ● እስኪያገቡ ድረስ ድንግል ሆኖ መቆየት ምን ጥቅሞች አሉት?

      ● ድንግልናን ጠብቆ መቆየት ያለውን ጥቅም ለታናናሾቻችሁ ማስረዳት የምትችሉት እንዴት ነው?

      [በገጽ 51 ላይ የሚገኝ የተቀነጨበ ሐሳብ]

      ‘ሴሰኛ ወይም ርኩስ የሆነ ማንኛውም ሰው በአምላክ መንግሥት ምንም ውርሻ እንደሌለው’ ሁልጊዜ ማስታወሴ የፆታ ብልግና እንድፈጽም የሚያጋጥመኝን ፈተና ለመቋቋም አስችሎኛል።” (ኤፌሶን 5:5)​—ሊዲያ

      [በገጽ 49 ላይ የሚገኝ ሣጥን]

      የመልመጃ ሣጥን

      በእርግጥ ከዚያ በኋላ ምን ይሆናል?

      አብዛኛውን ጊዜ እኩዮችሽም ሆኑ በብዙኃኑ ዘንድ ተወዳጅ የሆኑ የመዝናኛ ፕሮግራሞች ከጋብቻ በፊት የፆታ ግንኙነት መፈጸም የሚያስከትለውን መዘዝ አድበስብሰው ያልፉታል። እስቲ የሚከተሉትን ሦስት ሁኔታዎች እንመልከት። እነዚህ ወጣቶች በእርግጥ ምን ያጋጠማቸው ይመስልሻል?

      ● አብሮሽ የሚማር አንድ ወጣት ከበርካታ ሴቶች ጋር የፆታ ግንኙነት እንደፈጸመ በጉራ ይናገራል። ሁኔታው በጣም አስደሳች እንደሆነና ማናቸውም ምንም ችግር እንዳላጋጠማቸው ይገልጻል። ይሁንና እሱም ሆነ ሴቶቹ ድርጊቱን ከፈጸሙ በኋላ ያጋጠማቸው ነገር በእርግጥ እንደጠበቁት የሚሆን ይመስልሻል? ․․․․․

      ● አንድ ፊልም እየተመለከትሽ ነው እንበል፤ ፊልሙ የሚደመደመው ሁለት የሚዋደዱ ወጣቶች ገና ሳይጋቡ የፆታ ግንኙነት ሲፈጽሙ በማሳየት ነው። በገሃዱ ዓለም ቢሆን ኖሮ ከዚያ በኋላ ምን የሚያጋጥማቸው ይመስልሻል? ․․․․․

      ● አንድ ቆንጆ ወጣት የፆታ ግንኙነት እንድትፈጽሙ ጠየቀሽ። ድርጊቱን ብትፈጽሙ ማንም እንደማያውቅባችሁ ነግሮሻል። ከልጁ ጋር የፆታ ግንኙነት ብትፈጽሚና ሁኔታውን ለመደበቅ ብትሞክሪ ከዚያ በኋላ የሚያጋጥምሽ ነገር በእርግጥ እንደጠበቅሽው የሚሆን ይመስልሻል? ․․․․․

      [በገጽ 54 ላይ የሚገኝ ሥዕል]

      ከጋብቻ በፊት የፆታ ግንኙነት መፈጸም አንድ ስጦታ ሳይሰጥህ አስቀድመህ እንደመክፈት ነው

አማርኛ ጽሑፎች (1991-2025)
ውጣ
ግባ
  • አማርኛ
  • አጋራ
  • የግል ምርጫዎች
  • Copyright © 2025 Watch Tower Bible and Tract Society of Pennsylvania
  • የአጠቃቀም ውል
  • ሚስጥር የመጠበቅ ፖሊሲ
  • ሚስጥር የመጠበቅ ማስተካከያ
  • JW.ORG
  • ግባ
አጋራ