የመጠበቂያ ግንብ የኢንተርኔት ቤተ መጻሕፍት
መጠበቂያ ግንብ
የኢንተርኔት ቤተ መጻሕፍት
አማርኛ
፦
  • ፡
  • መጽሐፍ ቅዱስ
  • የሕትመት ውጤቶች
  • ስብሰባዎች
  • ሳንሄድሪን ፊት ቀረበ፤ ከዚያም ወደ ጲላጦስ ተወሰደ
    እስከ ዛሬ ከኖሩት ሁሉ የሚበልጠው ታላቅ ሰው
    • ምዕራፍ 121

      ሳንሄድሪን ፊት ቀረበ፤ ከዚያም ወደ ጲላጦስ ተወሰደ

      ሌሊቱ እየተገባደደ ነው። ጴጥሮስ ኢየሱስን ለሦስተኛ ጊዜ የካደው ሲሆን የሳንሄድሪን አባላት ሲያካሄዱት የቆዩትን የፌዝ ችሎት አጠናቀው ተበትነዋል። ይሁን እንጂ ዓርብ እንደነጋ እንደገና ተሰበሰቡ፤ አሁን የተሰበሰቡት በሳንሄድሪን ሸንጎ መሰብሰቢያ አዳራሻቸው ውስጥ ነው። የተሰበሰቡበት ዓላማ ሌሊት ያካሄዱት ችሎት ሕጋዊ መልክ እንዲኖረው ለማድረግ ሳይሆን አይቀርም። ኢየሱስ ፊታቸው ሲቀርብ ሌሊት እንዳደረጉት ሁሉ አሁንም “ክርስቶስ አንተ ነህን? ንገረን” አሉት።

      ኢየሱስ “ብነግራችሁ አታምኑም” ሲል መለሰላቸው። “ብጠይቅም አትመልሱልኝም።” ይሁን እንጂ ኢየሱስ “ከአሁን ጀምሮ የሰው ልጅ በእግዚአብሔር ኃይል ቀኝ ይቀመጣል” በማለት በድፍረት ማንነቱን ገለጸላቸው።

      ሁሉም “እንግዲያስ አንተ የእግዚአብሔር ልጅ ነህን?” ብለው ጠየቁት።

      ኢየሱስ “እኔ እንደ ሆንሁ እናንተ ትላላችሁ” ሲል መለሰላቸው።

      እነዚህ ሰዎች ዓላማቸው እሱን ለመግደል ስለሆነ ይህ መልስ ለእነርሱ በቂ ነበር። ልክ አምላክን እንደ ሰደበ አድርገው ቆጠሩት። “ራሳችን ከአፉ ሰምተናልና ከእንግዲህ ወዲህ ምን ምስክር ያስፈልገናል?” አሉ። ስለዚህ ኢየሱስን አስረው ወሰዱትና ለሮማዊው ገዥ ለጴንጤናዊው ጲላጦስ አሳልፈው ሰጡት።

      ኢየሱስን አሳልፎ የሰጠው ይሁዳ ሲከናወን የነበረውን ነገር ይከታተል ነበር። ኢየሱስ እንደተፈረደበት ሲያውቅ ተጸጸተ። ስለዚህ ሠላሳውን ብር ለመመለስ ወደ ካህናት አለቆቹና ወደ ሕዝቡ ሽማግሌዎች ሄዶ “ንጹሕ ደም አሳልፌ በመስጠቴ በድያለሁ” አላቸው።

      “ታዲያ እኛ ምን ቸገረን! የራስህ ጉዳይ ነው!” በማለት ደንታ ቢስነታቸውን በሚያሳይ መንገድ መለሱለት። (የ1980 ትርጉም) ስለዚህ ይሁዳ ብሩን ቤተ መቅደሱ ውስጥ በትኖ ሄደና ራሱን ለመስቀል ሞከረ። ይሁን እንጂ ይሁዳ ገመዱን አስሮበት የነበረው ቅርንጫፍ ሳይሰበር አይቀርም፤ ሲወድቅ ሰውነቱ ከታች ከነበሩት አለቶች ጋር በመላተሙ ተሰንጥቆ ሞተ።

      የካህናት አለቆቹ ብሩን ምን እንደሚያደርጉበት ግራ ገባቸው። “የደም ዋጋ ነውና ወደ መባ ልንጨምረው አልተፈቀደም” አሉ። ስለዚህ አንድ ላይ ሆነው ከተማከሩ በኋላ ለእንግዶች መቃብር እንዲሆን የሸክላ ሠሪውን መሬት ገዙበት። ስለዚህ መሬቱ “የደም መሬት” ተባለ።

      ኢየሱስ ወደ ገዥው ቤተ መንግሥት ሲወሰድ አሁንም ጊዜው ገና ማለዳ ነበር። ሆኖም ከኢየሱስ ጋር የመጡት አይሁዶች ከአሕዛብ ጋር እንዲህ ዓይነት የቅርብ ግንኙነት ማድረግ ያረክሰናል ብለው ስለሚያምኑ ለመግባት ፈቃደኞች አልሆኑም። ስለዚህ ጲላጦስ እነርሱን ለመርዳት ሲል ወደ ውጪ ወጣ። “ይህን ሰው ስለ ምን ትከሱታላችሁ?” ሲል ጠየቃቸው።

      እነርሱም “ይህስ ክፉ አድራጊ ባይሆን ወደ አንተ አሳልፈን ባልሰጠነውም ነበር” ሲሉ መለሱለት።

      ጲላጦስ በዚህ ጉዳይ እጁን ማስገባት ስላልፈለገ “እናንተ ወስዳችሁ እንደ ሕጋችሁ ፍረዱበት” አላቸው።

      አይሁዶቹ እርሱን ለመግደል ያላቸውን ፍላጎት በመግለጽ “ለእኛስ ማንንም ልንገድል አልተፈቀደልንም” አሉት። በእርግጥም ኢየሱስን በማለፍ በዓል ላይ ቢገድሉት ኖሮ ብዙ ሰዎች ኢየሱስን ከፍ አድርገው ይመለከቱት ስለነበረ የሕዝብ ዓመፅ ሊቀሰቀስ ይችል ነበር። ሆኖም ሮማውያን በፖለቲካ ክስ እንዲገድሉት ማድረግ ከቻሉ እነርሱ በሕዝቡ ዘንድ ከተጠያቂነት ነፃ ሊሆኑ ይችላሉ።

      ስለዚህ የሃይማኖት መሪዎቹ አምላክን ሰድቦአል ብለው ኢየሱስን የወነጀሉበትን ችሎት ሳይጠቅሱ አሁን የተለያዩ ክሶች ፈጠሩ። ሦስት ክፍሎችን የያዘ ክስ መሠረቱ:- “ይህ [1] ሕዝባችንን ሲያጣምም [2] ለቄሣርም ግብር እንዳይሰጥ ሲከለክል ደግሞም:- [3] እኔ ክርስቶስ ንጉሥ ነኝ ሲል አገኘነው።”

      ጲላጦስን ይበልጥ ያሳሰበው ኢየሱስ እኔ ንጉሥ ነኝ ብሏል የሚለው ክስ ነበር። ስለዚህ እንደገና ወደ ቤተ መንግሥቱ ገብቶ ኢየሱስን አስጠራውና “የአይሁድ ንጉሥ አንተ ነህን?” ሲል ጠየቀው። በሌላ አነጋገር፣ ቄሣርን በመቃወም እኔ ንጉሥ ነኝ ብለህ ሕጉን ተላልፈሃልን? ማለቱ ነበር።

      ኢየሱስ ጲላጦስ ስለ እርሱ ምን ያህል እንደሰማ ማወቅ ስለፈለገ “አንተ ይህን የምትለው ከራስህ ነውን ወይስ ሌሎች ስለ እኔ ነገሩህን?” ሲል ጠየቀው።

      ጲላጦስ ስለ እርሱ የሚያውቀው ነገር እንደሌለና እውነታውን ማወቅ እንደሚፈልግ ገለጸ። “እኔ አይሁዳዊ ነኝን? ወገኖችህና የካህናት አለቆች ለእኔ አሳልፈው ሰጡህ፤ ምን አድርገሃል?” አለው።

      ኢየሱስ ንግሥናን በተመለከተ የተነሣውን ጉዳይ እንዲሁ አድበስብሶ ለማለፍ አልሞከረም። ኢየሱስ ቀጥሎ የሰጠው መልስ ጲላጦስን እንዳስገረመው ምንም አያጠራጥርም። ሉቃስ 22:​66 እስከ 23:​3፤ ማቴዎስ 27:​1-11፤ ማርቆስ 15:​1፤ ዮሐንስ 18:​28-35፤ ሥራ 1:​16-20

      ▪ የሳንሄድሪን ሸንጎ እንደገና ጠዋት የተሰበሰበው ለምን ዓላማ ነው?

      ▪ ይሁዳ የሞተው እንዴት ነው? በ30ው ብርስ ምን ተደረገበት?

      ▪ አይሁዶች ኢየሱስን ራሳቸው ከመግደል ይልቅ ሮማውያን እንዲገድሉት ለማድረግ የፈለጉት ለምንድን ነው?

      ▪ አይሁዶች በኢየሱስ ላይ ምን ክሶች መሠረቱ?

  • ከጲላጦስ ወደ ሄሮድስ ከዚያም እንደገና ወደ ጲላጦስ ተወሰደ
    እስከ ዛሬ ከኖሩት ሁሉ የሚበልጠው ታላቅ ሰው
    • ምዕራፍ 122

      ከጲላጦስ ወደ ሄሮድስ ከዚያም እንደገና ወደ ጲላጦስ ተወሰደ

      ኢየሱስ ንጉሥ መሆኑን ከጲላጦስ ለመደበቅ አንዳችም ሙከራ ያላደረገ ቢሆንም መንግሥቱ በሮም መንግሥት ላይ ምንም የሚፈጥረው ስጋት እንደሌለ ገለጸ። ኢየሱስ “መንግሥቴ ከዚህ ዓለም አይደለችም” አለው። “መንግሥቴስ ከዚህ ዓለም ብትሆን፣ ወደ አይሁድ እንዳልሰጥ ሎሌዎቼ ይዋጉልኝ ነበር፤ አሁን ግን መንግሥቴ ከዚህ አይደለችም።” በዚህ መንገድ ኢየሱስ ምንም እንኳ መንግሥቱ ምድራዊ ባይሆንም መንግሥት እንዳለው ሦስት ጊዜ ገልጿል።

      ሆኖም ጲላጦስ “እንግዲያ ንጉሥ ነህን?” ሲል አጥብቆ ጠየቀው። መንግሥትህ ከዚህ ዓለም ባይሆንም እንኳ ንጉሥ ነህን? ማለቱ ነበር።

      ኢየሱስ የሚከተለውን መልስ በመስጠት ጲላጦስ ትክክለኛ መደምደሚያ ላይ እንደደረሰ እንዲገነዘብ አደረገው:- “እኔ ንጉሥ እንደ ሆንሁ አንተ ትላለህ። እኔ ለእውነት ልመሰክር ስለዚህ ተወልጃለሁ ስለዚህም ወደ ዓለም መጥቻለሁ፤ ከእውነት የሆነ ሁሉ ድምፄን ይሰማል።”

      አዎን፣ ኢየሱስ ወደ ምድር የመጣው “ለእውነት” ለመመስከር፣ በተለይም ስለ መንግሥቱ የሚገልጸውን እውነት ለመመስከር ነው። ኢየሱስ ሕይወቱን የሚያሳጣው ቢሆን እንኳ ለዚህ እውነት ታማኝ ሆኖ ለመገኘት ዝግጁ ነው። ጲላጦስ “እውነት ምንድር ነው?” ብሎ የጠየቀው ቢሆንም እንኳ ተጨማሪ ማብራሪያ ለማግኘት አልፈለገም። ፍርድ ለመስጠት የሚያስችል በቂ ነገር አግኝቷል።

      ጲላጦስ ከቤተ መንግሥቱ ውጪ ሆኖ ወደሚጠባበቀው ሕዝብ ተመለሰ። ከሁኔታው መረዳት እንደሚቻለው ኢየሱስን ጎኑ አቁሞ የካህናት አለቆቹንና አብረዋቸው ያሉትን ሰዎች “በዚህ ሰው አንድ በደል ስንኳ አላገኘሁበትም” አላቸው።

      ሕዝቡ በውሳኔ ተበሳጭተው ግትር አቋም በመያዝ “ከገሊላ ጀምሮ እስከዚህ ድረስ በይሁዳ ሁሉ እያስተማረ ሕዝቡን ያውካል” አሉ።

      የአይሁዶቹ ጭፍን የሆነ ግትር አቋም ጲላጦስን ሳያስገርመው አይቀርም። ስለዚህ የካህናት አለቆቹና የሕዝቡ ሽማግሌዎች መጮኻቸውን ሲቀጥሉ ጲላጦስ ወደ ኢየሱስ ዞር አለና “ስንት ያህል እንዲመሰክሩብህ አትሰማምን?” ሲል ጠየቀው። ሆኖም ኢየሱስ ምንም መልስ አልሰጠም። ኢየሱስ ይህን ሁሉ መሠረተ ቢስ የሆነ ክስ ሲሰነዝሩበት ዝም ማለቱ ጲላጦስን አስደነቀው።

      ጲላጦስ ኢየሱስ የገሊላ ሰው መሆኑን ሲያውቅ ራሱን ከኃላፊነት ነፃ የሚያደርግበት መንገድ አገኘ። የገሊላ ገዥ የሆነው ሄሮድስ አንቲጳስ (የታላቁ ሄሮድስ ልጅ) የማለፍ በዓሉን ለማክበር ወደ ኢየሩሳሌም መጥቶ ነበር፤ ስለዚህ ጲላጦስ ኢየሱስን ወደ እርሱ ሰደደው። ቀደም ሲል ሄሮድስ አንቲጳስ የአጥማቂው ዮሐንስ ራስ እንዲቆረጥ አድርጓል። ከዚያም ሄሮድስ ኢየሱስ እየፈጸማቸው ስለነበሩት ተአምራት ሲሰማ ዮሐንስ ከሞት እንደተነሳና ኢየሱስ የተባለው እሱ እንደሆነ አድርጎ በማሰብ ፈርቶ ነበር።

      አሁን ሄሮድስ ኢየሱስን የሚያይበት አጋጣሚ በማግኘቱ በጣም ተደሰተ። ሄሮድስ የተደሰተው ስለ ኢየሱስ ደህንነት አስቦ ወይም ደግሞ በኢየሱስ ላይ የተነሱት ክሶች እውነተኛ መሆን አለመሆናቸውን በሚገባ ለማጣራት ፈልጎ አይደለም። ከዚህ ይልቅ ኢየሱስ የሆነ ተአምር ሲፈጽም ለማየት ይመኝና ተስፋ ያደርግ ስለነበረ ብቻ ነው።

      ይሁን እንጂ ኢየሱስ ሄሮድስ የጓጓለትን ነገር ለመፈጸም ፈቃደኛ አልሆነም። እንዲያውም ሄሮድስ ሲጠይቀው አንድም ቃል አልተነፈሰም። ሄሮድስና ዘብ ጠባቂዎቹ ኢየሱስን እንደጠበቁት ሆኖ ሳላላገኙት ተሳለቁበት። የሚያብረቀርቅ ልብስ አልብሰው አሾፉበት። ከዚያም ወደ ጲላጦስ መልሰው ላኩት። በዚህም ምክንያት ቀደም ሲል ጠላቶች የነበሩት ሄሮድስና ጲላጦስ አሁን ጥሩ ወዳጆች ሆኑ።

      ኢየሱስ ተመልሶ ሲመጣ ጲላጦስ የካህናት አለቆችን፣ የአይሁድ መሪዎችንና ሕዝቡን አንድ ላይ ጠርቶ እንዲህ አላቸው:- “ሕዝቡን ያጣምማል ብላችሁ ይህን ሰው ወደ እኔ አመጣችሁት፤ እነሆም፣ በፊታችሁ መርምሬ ከምትከሱበት ነገር አንድ በደል ስንኳ በዚህ ሰው አላገኘሁበትም። ሄሮድስም ደግሞ ምንም አላገኘም፤ ወደ እኛ መልሶታልና፤ እነሆም፣ ለሞት የሚያደርሰው ምንም አላደረገም፤ እንግዲያስ ቀጥቼ እፈታዋለሁ።”

      በዚህ መንገድ ጲላጦስ ኢየሱስ ንጹሕ እንደሆነ ሁለት ጊዜ ተናግሯል። ካህናቱ አሳልፈው የሰጡት ስለ ቀኑበት ብቻ እንደሆነ ስለተገነዘበ ሊፈታው ፈልጓል። ጲላጦስ ኢየሱስን ለመፍታት ጥረት ማድረጉን በቀጠለ ጊዜ ይህንኑ ጥረቱን ከበፊቱ የበለጠ እንዲገፋበት የሚያደርግ ነገር አጋጠመው። በፍርድ ወንበሩ ላይ ተቀምጦ ሳለ ሚስቱ መልእክት በመላክ እንዲህ ስትል አጥብቃ አሳሰበችው:- “ስለ እርሱ ዛሬ በሕልም [ከመለኮታዊ ኃይል የመጣ እንደሆነ ግልጽ ነው] እጅግ መከራ ተቀብያለሁና በዚያ ጻድቅ ሰው ምንም አታድርግ።”

      ሆኖም ጲላጦስ ይህን ንጹሕ ሰው መፍታት እንዳለበት ቢያውቅም እንኳ እንዴት ሊፈታው ይችላል? ዮሐንስ 18:​36-38፤ ሉቃስ 23:​4-16፤ ማቴዎስ 27:​12-14, 18, 19፤ 14:​1, 2፤ ማርቆስ 15:​2-5

      ▪ ኢየሱስ ስለ ንግሥናው የቀረበለትን ጥያቄ የመለሰው እንዴት ነው?

      ▪ ኢየሱስ በምድራዊ ሕይወቱ ወቅት የመሰከረለት “እውነት” ምንድን ነው?

      ▪ ጲላጦስ ምን ፍርድ ሰጠ? ሰዎቹ ምን ምላሽ አሳዩ? ጲላጦስ ኢየሱስን ምን አደረገው?

      ▪ ሄሮድስ አንቲጳስ ማን ነው? ኢየሱስን ማየቱ በጣም ያስደሰተው ለምንድን ነው? በእርሱስ ላይ ምን አደረገበት?

      ▪ ጲላጦስ ኢየሱስን ለመፍታት ከፍተኛ ፍላጎት ያደረበት ለምንድን ነው?

  • “እነሆ ሰውዬው!”
    እስከ ዛሬ ከኖሩት ሁሉ የሚበልጠው ታላቅ ሰው
    • ምዕራፍ 123

      “እነሆ ሰውዬው!”

      ጲላጦስ፣ ኢየሱስ ያሳየው ጠባይ ስለማረከውና ንጹሕ መሆኑን ስለተገነዘበ እሱን ለመፍታት ሌላ መንገድ መፈለግ ጀመረ። ሕዝቡን “በፋሲካ [“በማለፍ በዓል፣” NW] አንድ ልፈታላችሁ ልማድ አላችሁ” አላቸው።

      በርባን የሚባል አንድ የታወቀ ነፍሰ ገዳይም ታስሮ ነበር፤ ስለዚህ ጲላጦስ “በርባንን ወይስ ክርስቶስ የተባለውን ኢየሱስን ማንኛውን ልፈታላችሁ ትወዳላችሁ?” ሲል ጠየቃቸው።

      ሕዝቡ ከሥር ሆነው የሚቆሰቁሷቸው የካህናት አለቆች ስላግባቧቸው በርባን እንዲፈታና ኢየሱስ እንዲገደል ጠየቁ። ጲላጦስ አሁንም ተስፋ ባለመቁረጥ “ከሁለቱ ማንኛውን ልፈታላችሁ ትወዳላችሁ?” ሲል በድጋሚ ጠየቃቸው።

      “በርባንን” ብለው ጮኹ።

      ጲላጦስ በጣም በመጨነቅ “ክርስቶስ የተባለውን ኢየሱስን እንግዲህ ምን ላድርገው?” ብሎ ጠየቃቸው።

      ጆሮ በሚያደነቁር ድምፅ “ይሰቀል” “ስቀለው ስቀለው” እያሉ ጮኹ።

      ጲላጦስ አንድ ንጹሕ ሰው እንዲገደል እየጠየቁ መሆኑን ስለተረዳ የሚከተለውን የተቃውሞ ሐሳብ አቀረበ:- “ምን ነው? ያደረገውስ ክፋት ምንድር ነው? ለሞት የሚያደርሰው በደል አላገኘሁበትም፤ ስለዚህ ቀጥቼ እፈታዋለሁ።”

      ጲላጦስ የተለያዩ ሙከራዎች ቢያደርግም ክፉኛ የተቆጣው ሕዝብ በሃይማኖት መሪዎቹ ግፊት “ይሰቀል” እያለ መጮኹን ቀጠለ። በካህናቱ ቆስቋሽነት ያበደው ሕዝብ ደም ተጠምቶ ነበር። ከሕዝቡ መካከል አንዳንዶቹ ከአምስት ቀናት በፊት ኢየሱስ ንጉሥ ሆኖ ወደ ኢየሩሳሌም ሲገባ ጥሩ አቀባበል አድርገውለት የነበሩት ሰዎች ሳይሆኑ አይቀሩም! በዚህ መካከል የኢየሱስ ደቀ መዛሙርት በቦታው ከነበሩ ድምፃቸውን አጥፍተው ተደብቀዋል።

      ጲላጦስ ሕዝቡን ለማግባባት ያደረገው ጥረት እንዳልተሳካና ሁከት እየተቀሰቀሰ መሆኑን ሲረዳ ውኃ አመጣና እጆቹን በሕዝቡ ፊት ታጥቦ “እኔ ከዚህ ጻድቅ ሰው ደም ንጹሕ ነኝ፤ እናንተ ተጠንቀቁ” አላቸው። በዚህ ጊዜ ሕዝቡ መልሰው “ደሙ በእኛና በልጆቻችን ላይ ይሁን” አሉ።

      ስለዚህ ጲላጦስ ካቀረቡት ጥያቄ ጋር በመስማማትና ትክክል እንደሆነ የሚያውቀውን ነገር ከማድረግ ይልቅ የሕዝቡን ፍላጎት ለማሟላት በመፈለግ በርባንን ፈታላቸው። ኢየሱስን ወሰደውና ልብሱን አስወልቆ አስገረፈው። ይህ ተራ ግርፋት አይደለም። ዘ ጆርናል ኦቭ ዚ አሜሪካን ሜዲካል አሶሲየሽን ሮማውያን ለመግረፍ ይጠቀሙበት የነበረውን ልማድ እንዲህ ሲል ገልጾታል:-

      “ለመግረፍ ይጠቀሙበት የነበረው የተለመደው መሣሪያ የተለያየ ርዝመት ያላቸው ነጠላ የሆኑ ወይም ደግሞ የተገመዱ የቆዳ ጠፍሮች ያሉትና በጠፍሮቹ ላይ አለፍ አለፍ ብለው የተሰኩ ትንንሽ የብረት እንክብሎች ወይም ስለት ያላቸው የበግ አጥንት ቁርጥራጮች ያሉት አጠር ያለ ጅራፍ (ፍላግረም ወይም ፍላጀለም) ነው። . . . ሮማውያን ወታደሮቹ የሰውዬውን ጀርባ ባለ በሌለ ኃይላቸው ደጋግመው ሲገርፉት የብረት እንክብሎቹ ትልልቅ ሰንበር ያወጣሉ። የቆዳ ጠፍሮቹና የበግ አጥንት ቁርጥራጮቹ ደግሞ ቆዳውንና ከቆዳው ሥር ያሉትን ሕብረ ሕዋሳት ይቆራርጧቸዋል። ከዚያም ግርፋቱ ሲቀጥል የቆዳው ስንጥቅ እየጠለቀ ይሄድና ከሥር ያሉት ጡንቻዎች ድረስ ይደርሳል፤ ይህም ሥጋው እንዲተለተልና ደም ቋጥሮ እንዲነዝረው ያደርገዋል።”

      ኢየሱስ በዚህ መንገድ በጣም በሚያሠቃይ ሁኔታ ከተገረፈ በኋላ ወደ ገዥው ቤተ መንግሥት ተወሰደና ወታደሮቹ በሙሉ እንዲሰበሰቡ ተደረገ። እዚያም ወታደሮቹ የእሾህ አክሊል ራሱ ላይ በማጥለቅና ወደ ታች በመጫን ሌላ አረመኔያዊ ድርጊት ፈጸሙበት። በቀኝ እጁ መቃ አስያዙት፤ ንጉሣውያን ቤተሰቦች የሚለብሱትን ዓይነት ሐምራዊ ልብስ አለበሱት። ከዚያም “የአይሁድ ንጉሥ ሆይ፣ ሰላም ለአንተ ይሁን” እያሉ ዘበቱበት። ምራቃቸውን ተፉበት፤ በጥፊም መቱት። ጠንካራውን መቃ ከእጁ ወስደው ጭንቅላቱን ሲመቱት ራሱ ላይ ባጠለቀው የሚያዋርድ “አክሊል” ላይ ያሉት ሹል እሾኾች ይበልጥ ጭንቅላቱ ውስጥ ተሰኩ።

      ኢየሱስ ይህን ሁሉ ቁም ስቅል ተቋቁሞ ያሳየው አስደናቂ ግርማ ሞገስና ጥንካሬ ጲላጦስን በጣም ስላስደነቀው ኢየሱስን ለማስለቀቅ ሌላ ሙከራ ለማድረግ ተገፋፋ። ሕዝቡን “እነሆ፣ አንዲት በደል ስንኳ እንዳላገኘሁበት ታውቁ ዘንድ እርሱን ወደ ውጭ አወጣላችኋለሁ” አላቸው። ምናልባትም በኢየሱስ ላይ የደረሰውን ሥቃይ ሲመለከቱ ልባቸው ይራራ ይሆናል ብሎ አስቦ ይሆናል። ኢየሱስ የእሾኹን አክሊል አጥልቆና ከላይ የሚደረበውን ሐምራዊ ልብስ አድርጎ እየደማ ያለው ፊቱ እየጠዘጠዘው በዚያ ጨካኝ ሕዝብ ፊት ሲቆም ጲላጦስ “እነሆ ሰውዬው!” ሲል ተናገረ።

      ምንም እንኳ የተደበደበና የቆሳሰለ ቢሆንም በታሪክ ዘመናት ሁሉ ተወዳዳሪ ያልተገኘለት ታላቅ ሰው ፊታቸው ቆሟል፤ በእርግጥም እስከ ዛሬ ከኖሩት ሁሉ የሚበልጥ ታላቅ ሰው! አዎን፣ ኢየሱስ፣ ጲላጦስ እንኳን ሳይቀር አምኖ የተቀበለውን ታላቅነቱን የሚመሰክር ግርማና እርጋታ አሳይቷል፤ ምክንያቱም ጲላጦስ የተናገራቸው ቃላት አክብሮትና ሐዘን የተቀላቀለባቸው ይመስላሉ። ዮሐንስ 18:​39 እስከ 19:​5፤ ማቴዎስ 27:​15-17, 20-30፤ ማርቆስ 15:​6-19፤ ሉቃስ 23:​18-25

      ▪ ጲላጦስ ኢየሱስን ለማስለቀቅ የሞከረው በምን መንገድ ነው?

      ▪ ጲላጦስ ራሱን ከኃላፊነት ነፃ ለማድረግ የሞከረው እንዴት ነው?

      ▪ መገረፍ ሲባል ምን ነገሮችን ይጨምራል?

      ▪ ኢየሱስን ከገረፉት በኋላ የዘበቱበት እንዴት ነው?

      ▪ ጲላጦስ ኢየሱስን ለማስለቀቅ ምን ተጨማሪ ሙከራ አድርጓል?

  • አልፎ መሰጠትና መወሰድ
    እስከ ዛሬ ከኖሩት ሁሉ የሚበልጠው ታላቅ ሰው
    • ምዕራፍ 124

      አልፎ መሰጠትና መወሰድ

      ጲላጦስ፣ ኢየሱስ ብዙ ሥቃይ ቢደርስበትም እንኳ ያሳየው ግርማ ሞገስ ስሜቱን በጣም ስለነካው እሱን ለማስለቀቅ እንደገና ሙከራ ሲያደርግ የካህናት አለቆቹ ከበፊቱ ይበልጥ ተቆጡ። የክፋት ዓላማቸውን ምንም ነገር እንዳያስተጓጉልባቸው ለመከላከል ቆርጠዋል። ስለዚህ እንደገና “ስቀለው ስቀለው” እያሉ መጮኽ ጀመሩ።

      ጲላጦስ “እናንተ ወስዳችሁ ስቀሉት” ሲል መለሰላቸው። (አይሁዶች ቀደም ሲል ከተናገሩት ሐሳብ በተቃራኒ፣ ለሞት የሚያበቃ አንድ ዓይነት ሃይማኖታዊ ጥፋት የፈጸሙ ወንጀለኞችን የማስገደል ሥልጣን ሊኖራቸው ይችላል።) ከዚያም ጲላጦስ ቢያንስ ለአምስተኛ ጊዜ ኢየሱስ ንጹሕ መሆኑን በመግለጽ “እኔስ አንዲት በደል ስንኳ አላገኘሁበትም” አላቸው።

      አይሁዶቹ የሰነዘሯቸው የፖለቲካ ክሶች ምንም ውጤት እንዳላስገኙ በመገንዘብ ከተወሰኑ ሰዓታት በፊት ኢየሱስ በሳንሄድሪን ችሎት ፊት ቀርቦ በነበረ ጊዜ ተጠቅመውበት የነበረውን አምላክን ተሳድቧል የሚለውን ሃይማኖታዊ ክሳቸውን እንደገና አነሱ። “እኛ ሕግ አለን፣ እንደ ሕጋችንም ሊሞት ይገባዋል፣ ራሱን የእግዚአብሔር ልጅ አድርጎአልና” አሉ።

      ይህ ክስ ለጲላጦስ አዲስ ከመሆኑም በላይ ይበልጥ እንዲፈራ አደረገው። ጲላጦስ አሁን ኢየሱስ ተራ ሰው አለመሆኑን ተገነዘበ፤ የሚስቱ ሕልምና ኢየሱስ ያሳየው አስደናቂ የመንፈስ ጥንካሬም ይህን የሚያመለክት ነበር። ግን እንዴት “የእግዚአብሔር ልጅ” ሊሆን ይችላል? ጲላጦስ ኢየሱስ የገሊላ ሰው መሆኑን ያውቃል። ሆኖም ምናልባት ከዚያ በፊት በሕይወት ይኖር የነበረ ሰው ይሆን? ጲላጦስ እንደገና ወደ ቤተ መንግሥቱ ይዞት ገባና “አንተ ከወዴት ነህ?” ሲል ጠየቀው።

      ኢየሱስ መልስ አልሰጠም። ኢየሱስ ንጉሥ እንደሆነ፣ ሆኖም መንግሥቱ ከዚህ ዓለም እንዳልሆነ ቀደም ሲል ለጲላጦስ ነግሮታል። አሁን ሌላ ተጨማሪ ማብራሪያ መስጠቱ ምንም ፋይዳ የለውም። ይሁን እንጂ ጲላጦስ ኢየሱስ መልስ አለመስጠቱ ክብሩን ዝቅ እንዳደረገበት ሆኖ ስለተሰማው ድንገት ግንፍል ብሎ “አትነግረኝምን? ልሰቅልህ ሥልጣን እንዳለኝ ወይም ልፈታህ ሥልጣን እንዳለኝ አታውቅምን?” አለው።

      ኢየሱስ “ከላይ ካልተሰጠህ በቀር በእኔ ላይ ምንም ሥልጣን ባልነበረህም” በማለት በአክብሮት መለሰለት። ኢየሱስ ምድራዊ ጉዳዮችን እንዲያስተዳድሩ አምላክ ለሰብዓዊ ገዥዎች የሰጠውን ሥልጣን መጥቀሱ ነበር። ኢየሱስ “ስለዚህ ለአንተ አሳልፎ የሰጠኝ ኃጢአቱ የባሰ ነው” ሲል አክሎ ተናገረ። በእርግጥም ሊቀ ካህናቱ ቀያፋና ግብረ አበሮቹ እንዲሁም የአስቆሮቱ ይሁዳ በኢየሱስ ላይ ለደረሰው ኢሰብዓዊ ድርጊት ከጲላጦስ የበለጠ ከባድ ኃላፊነት አለባቸው።

      ጲላጦስ ከበፊቱ ይበልጥ በኢየሱስ በመደነቅና መለኮታዊ አመጣጥ ሊኖረው ይችላል ብሎ በመስጋት እሱን ለማስለቀቅ እንደገና ጥረት ማድረግ ጀመረ። ይሁን እንጂ አይሁዶቹ ጲላጦስን አልተቀበሉትም። የፖለቲካ ክሳቸውን በድጋሚ በማንሳት እንዲህ ሲሉ በተንኮል አስፈራሩት:- “ይህንስ ብትፈታው የቄሣር ወዳጅ አይደለህም፤ ራሱን ንጉሥ የሚያደርግ ሁሉ የቄሣር ተቃዋሚ ነው።”

      ምንም እንኳ ሁኔታው መጥፎ ትርጉም ሊያሰጥ የሚችል ቢሆንም ጲላጦስ ዳግመኛ ኢየሱስን ወደ ውጪ አወጣው። “እነሆ ንጉሣችሁ” በማለት አሁንም ሕዝቡን ለማግባባት ሞከረ።

      “አስወግደው፣ አስወግደው፣ ስቀለው” አሉ።

      ጲላጦስ ተስፋ በመቁረጥ “ንጉሣችሁን ልስቀለውን?” ሲል ጠየቃቸው።

      አይሁዶች የሮማውያን አገዛዝ አስመርሯቸዋል። እንዲያውም የሮምን አገዛዝ በጣም ጠልተውታል! ሆኖም የካህናት አለቆቹ በግብዝነት “ከቄሣር በቀር ሌላ ንጉሥ የለንም” አሉ።

      ጲላጦስ ለፖለቲካ ሥልጣኑና ለስሙ በመስጋት በመጨረሻ አይሁዶች ያለማቋረጥ ያሰሙት ለነበረው ጥያቄ ተንበረከከ። ኢየሱስን አሳልፎ ሰጣቸው። ወታደሮቹ ሐምራዊውን ጨርቅ ከኢየሱስ ላይ አወለቁና የራሱን ልብስ አለበሱት። ኢየሱስ ሊሰቀል ሲወሰድ የራሱን የመከራ እንጨት እንዲሸከም ተደረገ።

      አሁን ዕለቱ ዓርብ ኒሳን 14 ሲሆን የጠዋቱ ክፍለ ጊዜ ተጋምሷል፤ ምናልባትም ወደ እኩለ ቀን እየተቃረበ ሳይሆን አይቀርም። ኢየሱስ ከሐሙስ ማለዳ ጀምሮ አልተኛም፤ በተጨማሪም ሥቃይ ሲፈራረቅበት ቆይቷል። ስለዚህ የተሸከመው እንጨት ከጥቂት ጊዜ በኋላ ኃይሉን ሁሉ እንደሚያሟጥጠው ግልጽ ነው። ስለዚህ በአፍሪካ ውስጥ ከምትገኘው ከቀሬና የመጣ አንድ ስምዖን የተባለ መንገደኛ በዚያ ሲያልፍ እንጨቱን እንዲሸከምለት አስገደዱት። ጉዞአቸውን ሲቀጥሉ ለኢየሱስ ዋይ ዋይ የሚሉና ሙሾ የሚያወጡ ሴቶችን ጨምሮ ብዙ ሰዎች ተከተሏቸው።

      ኢየሱስ ወደ ሴቶቹ ዞረና እንዲህ አላቸው:- “እናንተ የኢየሩሳሌም ልጆች፣ ለእኔስ አታልቅሱልኝ፤ ዳሩ ግን:- መካኖችና ያልወለዱ ማኅፀኖች ያላጠቡ ጡቶችም ብፁዓን [“ደስተኞች፣” NW] ናቸው የሚሉበት ጊዜ እነሆ ይመጣልና ለራሳችሁና ለልጆቻችሁ አልቅሱ። . . . በእርጥብ እንጨት እንዲህ የሚያደርጉ ከሆኑ፣ በደረቀውስ እንዴት ይሆን?”

      ኢየሱስ እሱ እዚያ በመገኘቱና በእሱ የሚያምኑ ጥቂት ቀሪዎች በመኖራቸው የተነሳ ትንሽ የሕይወት እርጥበት ሊኖረው ስለቻለው የአይሁድን ሕዝብ ስለሚያመለክተው ዛፍ መናገሩ ነበር። ሆኖም እነዚህ ሰዎች ከሕዝቡ መካከል በሚወጡበት ጊዜ በመንፈሳዊ የሞተ ዛፍ ማለትም የደረቀ ብሔራዊ ኅብረተሰብ ብቻ ይቀራል። የሮማ ሠራዊት የአምላክ ፍርድ አስፈጻሚ ሆኖ የአይሁድን ሕዝብ በሚያጠፋበት ጊዜ እንዴት ያለ ሐዘን ይሆናል! ዮሐንስ 19:​6-17፤ 18:​31፤ ሉቃስ 23:​24-31፤ ማቴዎስ 27:​31, 32፤ ማርቆስ 15:​20, 21

      ▪ የሃይማኖት መሪዎቹ በኢየሱስ ላይ ያነሷቸው ፖለቲካዊ ክሶች ምንም ውጤት ሳያስገኙ ሲቀሩ ምን ክስ አቀረቡ?

      ▪ ጲላጦስ ከበፊቱ የበለጠ ፍርሃት ያደረበት ለምንድን ነው?

      ▪ በኢየሱስ ላይ ለደረሰው ነገር ይበልጥ ኃጢአቱን የሚሸከመው ማን ነው?

      ▪ ካህናቱ በመጨረሻ ጲላጦስ ኢየሱስን ለሞት አሳልፎ እንዲሰጥ ያደረጉት እንዴት ነው?

      ▪ ኢየሱስ ያለቀሱለትን ሴቶች ምን አላቸው? ስለ ዛፉ “እርጥብ” መሆን ከዚያም ‘መድረቅ’ ሲናገር ምን ማመልከቱ ነበር?

  • በእንጨት ላይ ተሰቅሎ ያሳለፈው ሥቃይ
    እስከ ዛሬ ከኖሩት ሁሉ የሚበልጠው ታላቅ ሰው
    • ምዕራፍ 125

      በእንጨት ላይ ተሰቅሎ ያሳለፈው ሥቃይ

      ከኢየሱስ ጋር የሚሰቀሉ ሁለት ዘራፊዎች አብረውት ተወስደው ነበር። ከከተማው ብዙም ሳይርቁ ጎልጎታ ወይም የራስ ቅል ስፍራ ተብሎ ወደሚጠራው ቦታ ሲደርሱ ጉዞው አበቃ።

      እስረኞቹ ልብሳቸውን እንዲያወልቁ ተደረገ። ከዚያም ከርቤ የተቀላቀለበት ወይን ጠጅ አቀረቡላቸው። መጠጡ የተዘጋጀው በኢየሩሳሌም ሴቶች ሳይሆን አይቀርም፤ ሮማውያን ይህ የሚያደነዝዝ መድኃኒት ለሚሰቀሉት ሰዎች እንዲሰጥ ይፈቅዱ ነበር። ይሁን እንጂ ኢየሱስ ከቀመሰው በኋላ አልጠጣም አለ። አልጠጣም ያለው ለምንድን ነው? እምነቱ በሚታይበት በዚህ ታላቅ ፈተና ወቅት አእምሮውን ለማደንዘዝ እንዳልፈለገ ግልጽ ነው።

      አሁን ኢየሱስ እጆቹን ከራሱ በላይ ዘርግቶ በእንጨቱ ላይ ተጋደመ። ከዚያም ወታደሮቹ ትልልቅ ምስማሮች በእጆቹና በእግሮቹ ላይ ቸነከሩ። ምስማሮቹ ሥጋውንና ጅማቶቹን በስተው ሲገቡ በሥቃይ ይቃትት ነበር። እንጨቱ ቀጥ ብሎ እንዲቆም ሲደረግ የሰውነቱ ክብደት ምስማሮቹ በገቡባቸው ቁስሎች ላይ ስለሚያርፍ ሥቃዩ በጣም ይበረታል። ሆኖም ኢየሱስ በሮማ ወታደሮቹ ላይ አልዛተባቸውም፤ ከዚህ ይልቅ “አባት ሆይ፣ የሚያደርጉትን አያውቁምና ይቅር በላቸው” ሲል ጸለየላቸው።

      ጲላጦስ “የአይሁድ ንጉሥ የናዝሬቱ ኢየሱስ” የሚል ጽሑፍ የተጻፈበት ምልክት በእንጨቱ ላይ እንዲለጠፍ አደረገ። ይህን ጽሑፍ የጻፈው ለኢየሱስ አክብሮት ስለነበረው ብቻ ሳይሆን የአይሁድ ካህናት በኢየሱስ ላይ የሞት ፍርድ እንዲፈርድ በእሱ ላይ ከፍተኛ ተጽዕኖ በማሳደራቸው በእነርሱ ላይ ባደረበት ጥላቻ ጭምር ይመስላል። ጲላጦስ ሰዎች ሁሉ ሊያነቡት እንዲችሉ በሦስት ቋንቋዎች ማለትም በዕብራይስጥ፣ በኦፊሴላዊው የላቲን ቋንቋና ቀለል ባለ ግሪክኛ እንዲጻፍ አደረገ።

      ቀያፋንና ሐናን ጨምሮ የካህናት አለቆቹ ተበሳጩ። ይህ አዎንታዊ ማስታወቂያ በተቀዳጁት ድል ያገኙትን ደስታ አጨለመባቸው። ስለዚህ “እርሱ:- የአይሁድ ንጉሥ ነኝ እንዳለ እንጂ የአይሁድ ንጉሥ ብለህ አትጻፍ” ብለው ተቃወሙት። ጲላጦስ ካህናቱ እሱን መሣሪያ አድርገው መጠቀማቸው አናዶት ስለነበር “የጻፍሁትን ጽፌአለሁ” በማለት በንቀት የማያዳግም መልስ ሰጣቸው።

      አሁን ካህናቱ ከብዙ ሕዝብ ጋር ሆነው የሞት ፍርዱ በሚፈጸምበት ቦታ ተሰበሰቡ፤ ከዚያም ካህናቱ ማስታወቂያው ላይ የተጻፈውን ቃል ማስተባበል ጀመሩ። ቀደም ሲል በሳንሄድሪን ፊት በተካሄዱት ችሎቶች ላይ ቀርቦ የነበረውን የሐሰት ምሥክርነት ደግመው ተናገሩ። ስለዚህ በዚያ የሚያልፉ ሰዎች በፌዝ መልክ ራሳቸውን እየነቀነቁ “ቤተ መቅደስን የምታፈርስ በሦስት ቀንም የምትሠራው፣ ራስህን አድን፤ የእግዚአብሔር ልጅስ ከሆንህ ከመስቀል [“ከመከራው እንጨት፣” NW] ውረድ” በማለት መሳደብ መጀመራቸው አያስደንቅም።

      የካህናት አለቆቹና ሃይማኖታዊ ግብረ አበሮቻቸውም በመቀጠል እንዲህ አሉ:- “ሌሎችን አዳነ፣ ራሱን ሊያድን አይችልም፤ የእስራኤል ንጉሥ ከሆነ፣ አሁን ከመስቀል [“ከመከራው እንጨት፣” NW] ይውረድ እኛም እናምንበታለን። በእግዚአብሔር ታምኖአል፤ የእግዚአብሔር ልጅ ነኝ ብሎአልና ከወደደውስ አሁን ያድነው።”

      ወታደሮቹም እነርሱን ተከትለው በኢየሱስ መቀለድ ጀመሩ። ሆምጣጤ አመጡና የደረቁት ከንፈሮቹ ላይ አስጠግተው በመያዝ ሳይሆን አይቀርም፣ አሾፉበት። “አንተስ የአይሁድ ንጉሥ ከሆንህ፣ ራስህን አድን” እያሉ ዘበቱበት። በኢየሱስ ቀኝና ግራ የተሰቀሉት ዘራፊዎች እንኳን ሳይቀሩ አሾፉበት። እስቲ አስበው! እስከ ዛሬ ከኖሩት ሁሉ የሚበልጠው ታላቅ ሰው፣ አዎን፣ ከይሖዋ አምላክ ጋር ሆኖ ሁሉንም ነገሮች የፈጠረው ይህ ሰው ይህን ሁሉ ኢሰብዓዊ ድርጊት በጽናት ተቋቁሟል!

      ወታደሮቹ ኢየሱስ ከላይ ይደርበው የነበረውን ልብስ ወስደው አራት ቦታ ከፋፈሉት። ከዚያም ልብሱን ለመከፋፈል ዕጣ ተጣጣሉ። እጀ ጠባቡ ግን ስፌት የሌለው ከላይ ጀምሮ ወጥ የሆነ ከፍተኛ ጥራት ያለው ልብስ ነበር። ስለዚህ ወታደሮቹ “ለማን እንዲሆን በእርሱ ዕጣ እንጣጣልበት እንጂ አንቅደደው” ተባባሉ። በዚህ መንገድ ሳያውቁት “ልብሴን እርስ በርሳቸው ተከፋፈሉ በእጀ ጠባቤም ዕጣ ተጣጣሉበት” የሚለው ጥቅስ እንዲፈጸም አድርገዋል።

      ከጊዜ በኋላ ከዘራፊዎቹ አንዱ ኢየሱስ በእርግጥም ንጉሥ እንደሆነ ተገነዘበ። ስለዚህ ጓደኛውን እንዲህ ሲል ገሠጸው:- “አንተ እንደዚህ ባለ ፍርድ ሳለህ እግዚአብሔርን ከቶ አትፈራውምን? ስለ አደረግነውም የሚገባንን እንቀበላለንና በእኛስ እውነተኛ ፍርድ ነው፤ ይህ ግን ምንም ክፋት አላደረገም።” ከዚያም ኢየሱስን “በመንግሥትህ በመጣህ ጊዜ አስበኝ” ሲል ለመነው።

      ኢየሱስ “እውነት እልሃለሁ ዛሬ፣ ከእኔ ጋር በገነት ትሆናለህ” ሲል መለሰለት። (NW) ኢየሱስ በሰማይ ንጉሥ ሆኖ በሚገዛበት ጊዜ ከአርማጌዶን የተረፉት ሰዎችና ጓደኞቻቸው በሚያለሟት ገነት በምትሆነው ምድር ላይ እንዲኖር ይህን ንስሐ የገባ ክፉ አድራጊ ከሞት ሲያስነሳው ይህ ተስፋ ፍጻሜውን ያገኛል። ማቴዎስ 27:​33-44፤ ማርቆስ 15:​22-32፤ ሉቃስ 23:​27, 32-43፤ ዮሐንስ 19:​17-24

      ▪ ኢየሱስ ከርቤ የተቀላቀለበትን ወይን ጠጅ መጠጣት ያልፈለገው ለምንድን ነው?

      ▪ ኢየሱስ በተሰቀለበት እንጨት ላይ ማስታወቂያ የተለጠፈው ለምን ሳይሆን አይቀርም? ይህስ በጲላጦስና በካህናት አለቆቹ መካከል ምን የሐሳብ ልውውጥ እንዲደረግ ምክንያት ሆኗል?

      ▪ ኢየሱስ በእንጨቱ ላይ ተሰቅሎ እያለ ምን ተጨማሪ በደል ተፈጽሞበታል? ከሁኔታው ለመረዳት እንደሚቻለው ለዚህ ምክንያት የሆነውስ ነገር ምንድን ነው?

      ▪ በኢየሱስ ልብሶች ላይ በተፈጸመው ነገር አንድ ትንቢት ፍጻሜውን ያገኘው እንዴት ነው?

      ▪ ከሌቦቹ አንዱ ምን ለውጥ አደረገ? ኢየሱስ ጥያቄውን የሚያሟላለትስ እንዴት ነው?

  • “ይህ በእውነት የእግዚአብሔር ልጅ ነበረ”
    እስከ ዛሬ ከኖሩት ሁሉ የሚበልጠው ታላቅ ሰው
    • ምዕራፍ 126

      “ይህ በእውነት የእግዚአብሔር ልጅ ነበረ”

      ኢየሱስ እንጨቱ ላይ ተሰቅሎ ብዙም ሳይቆይ እኩለ ቀን ላይ ለሦስት ሰዓት የቆየ እንግዳ የሆነ ጨለማ ተከሰተ። ይህ የሆነው በፀሐይ ግርዶሽ ሳቢያ አይደለም። ምክንያቱም የፀሐይ ግርዶሽ የሚፈጠረው አዲስ ጨረቃ በምትኖርበት ጊዜ ብቻ ነው፤ በማለፍ በዓል ጊዜ ደግሞ ጨረቃ ሙሉ ነች። ከዚህም በላይ የፀሐይ ግርዶሽ የሚቆየው ለጥቂት ደቂቃዎች ብቻ ነው። ስለዚህ ጨለማው በመለኮታዊ ኃይል የተፈጸመ ነበር! በኢየሱስ ላይ ሲያላግጡ የነበሩት ሰዎች ጋብ እንዲሉና አልፎ ተርፎም ፌዛቸውን እንዲያቆሙ ሳያደርጋቸው አልቀረም።

      ይህ ያልተለመደ ሁኔታ የተከሰተው አንደኛው ክፉ አድራጊ ጓደኛውን ከመገሠጹና ኢየሱስን እንዲያስታውሰው ከመጠየቁ በፊት ከሆነ ይህ ሁኔታ ንስሐ እንዲገባ አስተዋጽኦ አድርጎለት ሊሆን ይችላል። አራት ሴቶች ማለትም የኢየሱስ እናትና እህቷ ሰሎሜ እንዲሁም መግደላዊት ማርያምና የታናሹ ያዕቆብ እናት የሆነችው ማርያም ወደ መከራው እንጨት የቀረቡት በጨለማው ወቅት ሊሆን ይችላል። ኢየሱስ የሚወደው ሐዋርያ ዮሐንስ ከእነርሱ ጋር ነበር።

      የኢየሱስ እናት አጥብታና ተንከባክባ ያሳደገችው ልጅ እዚያ ላይ ተሰቅሎ ሲሠቃይ ስታይ ልቧ ምንኛ ‘በሐዘን ጦር ተወግቶ’ ይሆን! ሆኖም ኢየሱስ ስለ ራሱ ሥቃይ ብቻ ሳይሆን ስለ እናቱም ደህንነት አስቧል። እንደምንም ተጣጥሮ በጭንቅላቱ ወደ ዮሐንስ በማመልከት እናቱን “አንቺ ሴት፣ እነሆ ልጅሽ” አላት። ከዚያም በጭንቅላቱ ወደ ማርያም በማመልከት ዮሐንስን “እናትህ እነኋት” አለው።

      ከሁኔታው መረዳት እንደሚቻለው በዚህ ወቅት መበለት የሆነችውን እናቱን እንዲንከባከባት ኢየሱስ ይበልጥ ለሚወደው ሐዋርያ በአደራ ሰጣት። ይህን ያደረገው የማርያም ሌሎች ልጆች ገና በእሱ ያላመኑ በመሆኑ ነው። በዚህ መንገድ ለእናቱ የሚያስፈልጉትን ሥጋዊ ነገሮችን ብቻ ሳይሆን መንፈሳዊ ነገሮችንም በማዘጋጀት ጥሩ ምሳሌ ትቷል።

      ከቀትር በኋላ ዘጠኝ ሰዓት ገደማ ላይ ኢየሱስ “ተጠማሁ” አለ። ኢየሱስ የአቋም ጽናቱ እስከ መጨረሻ ድረስ እንዲፈተን አባቱ ጥበቃውን ከእሱ ላይ እንዳነሳ ሆኖ የተሰማው ይመስላል። ስለዚህ “አምላኬ፣ አምላኬ፣ ለምን ተውኸኝ?” ሲል በታላቅ ድምፅ ጮኸ። በአቅራቢያው የነበሩ አንዳንዶች ይህን ሲሰሙ “እነሆ፣ ኤልያስን ይጠራል” አሉ። ወዲያውኑ ከመካከላቸው አንዱ ሮጦ ሄደና ሆምጣጤ ውስጥ የተነከረ ሰፍነግ በሂሶፕ አገዳ ጫፍ ላይ አድርጎ አጠጣው። ሌሎቹ ግን “ተዉ፤ ኤልያስ ሊያወርደው ይመጣ እንደ ሆነ እንይ” አሉ።

      ኢየሱስ ሆምጣጤውን ከሰጡት በኋላ “ተፈጸመ” ብሎ ጮኸ። አዎን፣ አባቱ ወደ ምድር ሲልከው እንዲያከናውነው የሰጠውን ሥራ ሁሉ ፈጽሟል። በመጨረሻ “አባት ሆይ፣ ነፍሴን [“መንፈሴን፣” NW] በእጅህ አደራ እሰጣለሁ” አለ። በዚህ መንገድ ኢየሱስ አምላክ እንደገና መልሶ እንደሚሰጠው በመተማመን የሕይወት ኃይሉን ለአምላክ በአደራ ሰጠ። ከዚያም ራሱን አዘንብሎ ሞተ።

      ኢየሱስ የመጨረሻዋን ትንፋሽ እንደተነፈሰ ኃይለኛ የምድር ነውጥ ተከሰተና ዓለቶች ተሰነጠቁ። ነውጡ በጣም ኃይለኛ ስለነበረ ከኢየሩሳሌም ውጪ ያሉት መቃብሮች ተከፈቱና አስከሬኖቹ ወደ ውጪ ወጡ። የወጡትን አስከሬኖች የተመለከቱ መንገደኞች ወደ ከተማይቱ ገቡና የሆነውን ነገር አወሩ።

      በተጨማሪም ኢየሱስ ሲሞት በአምላክ ቤተ መቅደስ ውስጥ ቅድስቱን ከቅድስተ ቅዱሳኑ የሚለየው ትልቅ መጋረጃ ከላይ እስከ ታች ለሁለት ተቀደደ። ይህ እጅግ ያጌጠ መጋረጃ 18 ሜትር ገደማ ከፍታ ያለውና በጣም ከባድ የነበረ ይመስላል! ይህ አስደናቂ ተአምር አምላክ በልጁ ገዳዮች ላይ የተሰማውን ቁጣ ከመግለጹም በላይ ወደ ቅድስተ ቅዱሳኑ ማለትም ወደ ሰማይ የሚያስገባው መንገድ በኢየሱስ ሞት አማካኝነት እንደተከፈተ ያመለክታል።

      ሰዎች የምድር ነውጡንና የተፈጸሙትን ነገሮች ሲመለከቱ ከፍተኛ ፍርሃት አደረባቸው። ግድያውን እንዲያስፈጽም ኃላፊነት የተሰጠው መቶ አለቃ አምላክን አከበረ። “ይህ በእውነት የእግዚአብሔር ልጅ ነበረ” አለ። በጲላጦስ ፊት በተካሄደው ችሎት ላይ ኢየሱስ የአምላክ ልጅ ነኝ ብሏል በሚለው ክስ ላይ ውይይት ሲደረግ መቶ አለቃው በቦታው የነበረ ይመስላል። እናም አሁን ኢየሱስ የአምላክ ልጅ እንደሆነ፣ አዎን፣ በእርግጥም እስከ ዛሬ ከኖሩት ሁሉ የሚበልጥ ታላቅ ሰው መሆኑን አምኗል።

      ሌሎች ሰዎችም በእነዚህ ተአምራዊ ክንውኖች በጣም ተነክተው የተሰማቸውን ጥልቅ ሐዘንና ኀፍረት ለመግለጽ ደረታቸውን እየደቁ ወደ ቤታቸው ተመለሱ። በእነዚህ ታላላቅ ክንውኖች ስሜታቸው በጥልቅ የተነካ ብዙ የኢየሱስ ሴት ደቀ መዛሙርት በርቀት ሆነው ይህን አስገራሚ ትዕይንት እየተመለከቱ ነበር። ሐዋርያው ዮሐንስም በቦታው ነበር። ማቴዎስ 27:​45-56፤ ማርቆስ 15:​33-41፤ ሉቃስ 23:​44-49፤ 2:​34, 35፤ ዮሐንስ 19:​25-30

      ▪ ለሦስት ሰዓት ያህል የጨለመው በፀሐይ ግርዶሽ ምክንያት ሊሆን የማይችለው ለምንድን ነው?

      ▪ ኢየሱስ ከመሞቱ ከጥቂት ጊዜ በፊት በዕድሜ የገፉ ወላጆች ላሏቸው ሰዎች ምን ጥሩ ምሳሌ ትቷል?

      ▪ ኢየሱስ ከመሞቱ በፊት የተናገራቸው አራት የመጨረሻ ዐረፍተ ነገሮች የትኞቹ ናቸው?

      ▪ የምድር ነውጡ ምን ነገር አስከትሏል? የቤተ መቅደሱ መጋረጃ ለሁለት መቀደዱ ምን ትርጉም አለው?

      ▪ ግድያውን ያስፈጸመው መቶ አለቃ ተአምራቱን ሲመለከት ምን ተሰማው?

  • ዓርብ ተቀበረ፤ እሁድ መቃብሩ ባዶ ሆኖ ተገኘ
    እስከ ዛሬ ከኖሩት ሁሉ የሚበልጠው ታላቅ ሰው
    • ምዕራፍ 127

      ዓርብ ተቀበረ፤ እሁድ መቃብሩ ባዶ ሆኖ ተገኘ

      ጊዜው ዓርብ አመሻሹ ላይ ነው፤ ኒሳን 15 ላይ የሚውለው ሰንበት ደግሞ ልክ ፀሐይ ስትጠልቅ ይጀምራል። የኢየሱስ አስከሬን ዝልፍልፍ ብሎ እንጨቱ ላይ ተንጠልጥሏል፤ በጎኑ የተሰቀሉት ሁለቱ ዘራፊዎች ግን አሁንም በሕይወት አሉ። ዓርብ ከሰዓት በኋላ የማዘጋጀት ቀን ተብሎ ይጠራ ነበር፤ ምክንያቱም ሰዎች ምግብ የሚያዘጋጁትና ሰንበት እስኪያልፍ ድረስ ሊቆዩ የማይችሉትን ሌሎች አጣዳፊ ሥራዎች የሚያጠናቅቁበት ጊዜ ስለነበረ ነው።

      ከጥቂት ጊዜ በኋላ የሚጀምረው ሰንበት መደበኛ ሰንበት (የሳምንቱ ሰባተኛ ቀን) ብቻ አልነበረም፤ ከዚህ ይልቅ ድርብ ወይም “ታላቅ” ሰንበትም ነበር። ይህን መጠሪያ ሊያገኝ የቻለው ለሰባት ቀን የሚከበረው ያልቦካ ቂጣ በዓል የመጀመሪያ ቀን የሆነው ኒሳን 15 (ይህ ዕለት በየትኛውም የሳምንቱ ቀን ላይ ቢውል ምንጊዜም ሰንበት ነው) መደበኛው ሰንበት በሚከበርበት ቀን ላይ ስለዋለ ነው።

      በአምላክ ሕግ መሠረት አስከሬኖች በእንጨት ላይ ተሰቅለው ማደር የለባቸውም። ስለዚህ አይሁዶች ጲላጦስ ፊት ቀረቡና የተሰቀሉት ሰዎች ጭናቸው ተሰብሮ ሞታቸው እንዲፋጠን ይደረግ ዘንድ ጠየቁት። ስለዚህ ወታደሮቹ የሁለቱን ዘራፊዎች ጭን ሰበሩ። ሆኖም ኢየሱስ ሞቶ ስለነበረ የሱን ጭን አልሰበሩም። ይህ “ከእርሱ አጥንት አይሰበርም” የሚለው ጥቅስ ፍጻሜውን እንዲያገኝ አድርጓል።

      ይሁን እንጂ ኢየሱስ እንደሞተ ሙሉ በሙሉ እርግጠኛ ለመሆን ከወታደሮቹ አንዱ ጎኑን በጦር ወጋው። ጦሩ ልቡ አካባቢ በስቶ ገባና ወዲያውኑ ደምና ውኃ ወጣ። የዓይን ምሥክር የነበረው ሐዋርያው ዮሐንስ ይህ ድርጊት “የወጉትን ያዩታል” የሚለው ሌላ ጥቅስ እንዲፈጸም ያደረገ መሆኑን ገልጿል።

      የተከበረ የሳንሄድሪን አባል የነበረው የአርማትያሱ ዮሴፍም ግድያው በተፈጸመበት ቦታ ነበር። ከፍተኛው ፍርድ ቤት በኢየሱስ ላይ የወሰደውን ፍትሃዊ ያልሆነ ድርጊት ደግፎ ድምፅ ለመስጠት ፈቃደኛ አልሆነም። ዮሴፍ ምንም እንኳ ባደረበት ፍርሃት ምክንያት ማንነቱን በግልጽ ባያሳውቅም የኢየሱስ ደቀ መዝሙር ነበር። አሁን ግን ድፍረት በማሳየት የኢየሱስን አስከሬን እንዲሰጠው ጲላጦስን ጠየቀው። ጲላጦስ ግድያውን እንዲያስፈጽም ኃላፊነት ተሰጥቶት የነበረውን መቶ አለቃ አስጠርቶ ኢየሱስ መሞቱን ካረጋገጠ በኋላ አስከሬኑን አሳልፎ ሰጠው።

      ዮሴፍ አስከሬኑን ወሰደና በንጹሕ ጨርቅ ከፈነው። የሳንሄድሪን አባል የሆነው ኒቆዲሞስም ረድቶታል። ኒቆዲሞስም ሥልጣኑን እንዳያጣ ስለሰጋ በኢየሱስ ላይ ያለውን እምነት አልገለጠም ነበር። አሁን ግን 33 ኪሎ ግራም የሚመዝን የከርቤና በጣም ውድ የሆነ እሬት ቅልቅል አመጣ። የኢየሱስን አስከሬን እነዚህን ቅመሞች በያዙ ጨርቆች በመጠቅለል በአይሁዳውያን የአገናነዝ ልማድ ገነዙት።

      ከዚያም አስከሬኑ በአቅራቢያው በሚገኝ የአትክልት ሥፍራ ዮሴፍ ባዘጋጀው ከዓለት ተወቅሮ በተሠራ አዲስ መቃብር ውስጥ ተቀበረ። በመጨረሻም አንድ ትልቅ ድንጋይ አንከባለው መቃብሩን ዘጉት። አስከሬኑን ከሰንበት ቀን በፊት ለመቅበር ሲባል ዝግጅቱ የተከናወነው በጥድፊያ ነበር። ስለዚህ መግደላዊት ማርያምና የታናሹ ያዕቆብ እናት የሆነችው ማርያም ተጨማሪ ቅመሞችና ሽቶ ለማዘጋጀት በፍጥነት ወደ ቤት ሄዱ። እነዚህ ሴቶች አስከሬኑን ለመቅበር ዝግጅት ሲደረግ አስተዋጽኦ ሳያበረክቱ አይቀሩም። የኢየሱስ አስከሬን ረዘም ላለ ጊዜ ተጠብቆ መቆየት እንዲችል ከሰንበት ቀን በኋላ ተጨማሪ ሽቶና ቅባት ለመቀባት አቅደው ነበር።

አማርኛ ጽሑፎች (1991-2025)
ውጣ
ግባ
  • አማርኛ
  • አጋራ
  • የግል ምርጫዎች
  • Copyright © 2025 Watch Tower Bible and Tract Society of Pennsylvania
  • የአጠቃቀም ውል
  • ሚስጥር የመጠበቅ ፖሊሲ
  • ሚስጥር የመጠበቅ ማስተካከያ
  • JW.ORG
  • ግባ
አጋራ