የመጠበቂያ ግንብ የኢንተርኔት ቤተ መጻሕፍት
መጠበቂያ ግንብ
የኢንተርኔት ቤተ መጻሕፍት
አማርኛ
፦
  • ፡
  • መጽሐፍ ቅዱስ
  • የሕትመት ውጤቶች
  • ስብሰባዎች
  • የፆታ ግንኙነት መፈጸም ይበልጥ ያቀራርበን ይሆን?
    ወጣቶች የሚጠይቋቸው ጥያቄዎችና ተግባራዊ መሆን የሚችሉ መልሶች፣ ጥራዝ 1
    • ምዕራፍ 24

      የፆታ ግንኙነት መፈጸም ይበልጥ ያቀራርበን ይሆን?

      ሣራ ከናታን ጋር የፍቅር ጓደኝነት ከጀመረች ገና ሁለት ወሯ ቢሆንም ዕድሜዋን ሁሉ እንደምታውቀው ሆኖ ይሰማታል። አዘውትረው በሞባይል መልእክት ይለዋወጣሉ፣ አንዳንድ ጊዜ ደግሞ በስልክ ለሰዓታት ያወራሉ፣ እንዲሁም እርስ በርስ ይናበባሉ! ዛሬም በጨረቃ በደመቀው ምሽት መኪናቸውን አቁመው እያወሩ ነው፤ ናታን ግን ከወሬ ያለፈ ነገር እንዲያደርጉ ፈልጓል።

      ባለፉት ሁለት ወራት ናታንና ሣራ እጅ ለእጅ ከመያያዝና ለሰላምታ ያህል ከንፈር ለከንፈር ከመሳሳም ያለፈ ምንም ነገር አድርገው አያውቁም። ሣራ ከዚህ እንዲያልፉ አትፈልግም። በሌላ በኩል ደግሞ ናታንን እንዳታጣው ፈርታለች። ናታን በጣም ቆንጆና ልዩ እንደሆነች እንዲሰማት ያደርጋታል። ‘ደግሞም እኔና ናታን እስከተዋደድን ድረስ ምን ችግር አለው?’ በማለት ከራሷ ጋር ትሟገታለች።

      ሣራና ናታን ወዴት እያመሩ እንደሆነ መገመት አያቅትሽ ይሆናል። ይሁን እንጂ እነዚህ ወጣቶች የፆታ ግንኙነት መፈጸማቸው በሕይወታቸው ላይ ምን ያህል መጥፎ ተጽዕኖ እንደሚያሳድር ላትገነዘቢ ትችያለሽ። እስቲ የሚከተለውን አስቢ፦

      እንደ ስበት ሕግ ያሉ የተፈጥሮ ሕጎችን ብትጥሺ እንዲህ ማድረግ ከሚያስከትለው መዘዝ ማምለጥ አትችዪም። ‘ከዝሙት ራቁ’ እንደሚለው ያለውን የሥነ ምግባር ሕግ ብትጥሺም ውጤቱ ተመሳሳይ ነው። (1 ተሰሎንቄ 4:3) ይህን ትእዛዝ መጣስ ምን መዘዝ ያስከትላል? መጽሐፍ ቅዱስ ‘ዝሙት የሚፈጽም ሰው በራሱ አካል ላይ ኃጢአት እየሠራ ነው’ ይላል። (1 ቆሮንቶስ 6:18) ይህ የሚሆነው እንዴት ነው? እስቲ ከጋብቻ በፊት የፆታ ግንኙነት መፈጸም የሚያስከትላቸውን ሦስት ጉዳቶች ቀጥሎ ባሉት ክፍት ቦታዎች ላይ ለመጻፍ ሞክሪ።

      1 ․․․․․

      2 ․․․․․

      3 ․․․․․

      የጻፍሽውን ነገር መለስ ብለሽ ተመልከቺው። ከጻፍሻቸው ነገሮች መካከል የአባለ ዘር በሽታዎች፣ ያልተፈለገ እርግዝና ወይም የአምላክን ሞገስ ማጣት የሚሉት ይገኙበታል? አምላክ ዝሙትን አስመልክቶ የሰጠውን የሥነ ምግባር ሕግ የሚጥሱ ሰዎች እንደ እነዚህ ያሉ አስከፊ መዘዞች እንደሚያጋጥሟቸው የታወቀ ነው።

      ያም ሆኖ የፆታ ግንኙነት ለመፈጸም ትፈተኚ ይሆናል። ‘እንዲህ ባደርግ ምንም አልሆንም’ ብለሽ ታስቢ ይሆናል። ደግሞስ ሁሉም ሰው የፆታ ግንኙነት ይፈጽም የለ? በትምህርት ቤት ያሉት እኩዮችሽ የፆታ ግንኙነት መፈጸማቸውን እንደ ጀብዱ አድርገው ያወሩታል፤ ደግሞም ይህን በማድረጋቸው እነሱ ምንም ዓይነት ጉዳት የደረሰባቸው አይመስሉም። ምናልባትም በዚህ ርዕስ መግቢያ ላይ እንደተጠቀሰችው እንደ ሣራ የፆታ ግንኙነት መፈጸም ከፍቅር ጓደኛሽ ጋር ይበልጥ እንደሚያቀራርባችሁ ይሰማሽ ይሆናል። በዚያ ላይ ደግሞ ድንግል በመሆንሽ እንዲቀለድብሽ አትፈልጊም። ታዲያ ከዚህ ሁሉ የፆታ ግንኙነት እንድትፈጽሚ የሚቀርብልሽን ጥያቄ ብትቀበዪ አይሻልም?

      እስቲ ቆም ብለሽ ለማሰብ ሞክሪ! ከሁሉ በፊት ማወቅ ያለብሽ ነገር ቢኖር የፆታ ግንኙነት የሚፈጽመው ሁሉም ሰው አለመሆኑን ነው። እውነት ነው፣ በርካታ ወጣቶች የፆታ ግንኙነት እንደሚፈጽሙ የሚገልጽ አኃዛዊ መረጃ ተመልክተሽ ይሆናል። ለምሳሌ ያህል፣ በዩናይትድ ስቴትስ የተደረገ አንድ ጥናት እንደሚያሳየው በአገሪቱ ከሚኖሩ 3 ወጣቶች መካከል 2ቱ የሁለተኛ ደረጃ ትምህርታቸውን ከመጨረሳቸው በፊት የፆታ ግንኙነት መፈጸም ይጀምራሉ። ይሁን እንጂ ይኸው አኃዝ እንደሚያመለክተው ከ3 ወጣቶች 1ዱ የፆታ ግንኙነት እንደማይፈጽም ልብ ማለት ያስፈልጋል፤ ይህ ደግሞ ቀላል የሚባል ቁጥር አይደለም። ይሁንና የፆታ ግንኙነት ስለሚፈጽሙት ወጣቶችስ ምን ማለት ይቻላል? ተመራማሪዎች እንደገለጹት ከእነዚህ ወጣቶች አብዛኞቹ ከታች እንደተዘረዘሩት ያሉ ያልጠበቋቸው ሁኔታዎች ወይም ዱብ ዕዳዎች አጋጥመዋቸዋል።

      ዱብ ዕዳ 1 ጸጸት። ከጋብቻ በፊት የፆታ ግንኙነት የፈጸሙ አብዛኞቹ ወጣቶች በኋላ ላይ በድርጊታቸው እንደተቆጩ ተናግረዋል።

      ዱብ ዕዳ 2 አለመተማመን። ወጣቶቹ የፆታ ግንኙነት ከፈጸሙ በኋላ ‘ከእኔ ሌላ ከማን ጋር የፆታ ግንኙነት ፈጽማ/ፈጽሞ ይሆን?’ እያሉ ማሰብ ይጀምራሉ።

      ዱብ ዕዳ 3 ግራ መጋባት። ማንም ሴት ብትሆን የወንድ ጓደኛዋ ከጉዳት እንዲጠብቃት እንጂ መጠቀሚያ እንዲያደርጋት አትፈልግም። ብዙዎቹ ወንዶች ደግሞ ከአንዲት ሴት የፈለጉትን ካገኙ በኋላ ያቺ ሴት ያን ያህል አትማርካቸውም።

      ከላይ ከተገለጸው በተጨማሪ ብዙ ወጣት ወንዶች ከአንዲት ሴት ጋር የፆታ ግንኙነት ከፈጸሙ በኋላ ከእሷ ጋር ትዳር መመሥረት እንደማይፈልጉ ተናግረዋል። ለምን? ንጽሕናዋን የጠበቀች ወጣት ማግባት ስለሚመርጡ ነው!

      ይህ ያስገርምሽ አልፎ ተርፎም ያናድድሽ ይሆናል። ከሆነ ልታስታውሺው የሚገባ አንድ ሐቅ አለ፦ ከጋብቻ በፊት የፆታ ግንኙነት ከመፈጸም ጋር በተያያዘ እውነታው በፊልምና በቴሌቪዥን ላይ ከሚቀርበው በጣም የተለየ ነው። የመዝናኛው ኢንዱስትሪ በአሥራዎቹ ዕድሜ የሚገኙ ወጣቶች የፆታ ግንኙነት መፈጸማቸው በጣም አስደሳችና ምንም ጉዳት የሌለው ነገር እንደሆነ አልፎ ተርፎም እነዚህ ወጣቶች ከልባቸው እንደሚዋደዱ የሚያሳይ እንደሆነ አድርጎ ያቀርበዋል። ይሁን እንጂ በዚህ አትሞኚ! ከጋብቻ በፊት የፆታ ግንኙነት እንድትፈጽሚ የሚያባብሉሽ ሁሉ ይህን የሚያደርጉት የራሳቸውን ፍላጎት ለማርካት ነው። (1 ቆሮንቶስ 13:4, 5) አንድ ሰው እውነት የሚወድሽ ከሆነ አካላዊና ስሜታዊ ጉዳት የሚያስከትልብሽ ነገር እንድታደርጊ ይገፋፋሻል? (ምሳሌ 5:3, 4) ደግሞስ ከልቡ የሚያስብልሽ ሰው ከአምላክ ጋር ያለሽን ዝምድና የሚያበላሽ ድርጊት እንድትፈጽሚ ይጠይቅሻል?—ዕብራውያን 13:4

      ወደ ወንዶች ስንመጣ ደግሞ፣ ከአንዲት ወጣት ጋር የፍቅር ጓደኝነት ጀምረህ ከሆነ በዚህ ምዕራፍ ውስጥ የተጠቀሱት ነጥቦች ስለ ግንኙነታችሁ በቁም ነገር እንድታስብ ሊያደርጉህ ይገባል። ‘ለሴት ጓደኛዬ ከልቤ አስብላታለሁ?’ ብለህ ራስህን ጠይቅ። መልስህ ‘አዎ’ ከሆነ ይህን ማሳየት የምትችለው እንዴት ነው? የአምላክን ሕጎች ለማክበር የሚያስችል ጥንካሬ እና ወደ ፈተና ሊያስገቡ ከሚችሉ ሁኔታዎች ለመራቅ የሚረዳ ጥበብ እንዳለህ በማሳየት ነው፤ ከዚህም በተጨማሪ ለሴት ጓደኛህ በማሰብ ለእሷ ፍቅር እንዳለህ አሳይ። እንዲህ የምታደርግ ከሆነ የሴት ጓደኛህ “ውዴ የእኔ ነው፤ እኔም የእርሱ ነኝ” በማለት እንደተናገረችው ጥሩ ሥነ ምግባር ያላት ሱላማጢስ ልጃገረድ ዓይነት ስሜት ይኖራታል። (ማሕልየ መሓልይ 2:16) በአጭሩ፣ ከልቧ ታደንቅሃለች!

      ወንዶችም ሆኑ ሴቶች ከጋብቻ በፊት የፆታ ግንኙነት ሲፈጽሙ በጣም ውድ የሆነ ነገርን አውጥተው የጣሉ ያህል ነው፤ እንዲህ ሲያደርጉ ራሳቸውን ያዋርዳሉ። (ሮም 1:24) ብዙዎች የፆታ ግንኙነት ከፈጸሙ በኋላ በጣም ውድ የሆነ ነገር የተነጠቁ ያህል የባዶነትና የዋጋ ቢስነት ስሜት የሚሰማቸው መሆኑ ምንም አያስደንቅም! ይህ ሁኔታ በአንቺ ላይ እንዲደርስ አትፍቀጂ! አንድ ሰው “ብትወጂኝ ኖሮ እሺ ትዪኝ ነበር” እያለ የፆታ ግንኙነት እንድትፈጽሚ ሊያባብልሽ ከሞከረ ፈርጠም ብለሽ “አንተም ብትወደኝ ኖሮ እንዲህ ያለ ነገር አትጠይቀኝም ነበር!” በማለት መልሺለት።

      ሰውነትሽን እንደ ውድ ነገር ልትመለከቺው ይገባል፤ እንደማይረባ ነገር አታቃልዪው። አምላክ ከዝሙት እንድንርቅ የሰጠውን ትእዛዝ ለመጠበቅ የሚያስችል ጥንካሬ እንዳለሽ በተግባር አሳዪ። ደግሞም የፆታ ግንኙነት መፈጸሙን ስታገቢ ትደርሺበታለሽ። ከጋብቻ በፊት የፆታ ግንኙነት መፈጸም ከሚያስከትለው ጭንቀትና ጸጸት ነፃ ሆነሽ በፆታ ግንኙነት የሚገኘውን ደስታ ሙሉ በሙሉ ማጣጣም የምትችዪው ካገባሽ በኋላ ነው።—ምሳሌ 7:22, 23፤ 1 ቆሮንቶስ 7:3

      ተጨማሪ ሐሳብ ለማግኘት የዚህን መጽሐፍ ጥራዝ 2 ምዕራፍ 4 እና 5 ተመልከት

      በሚቀጥለው ምዕራፍ

      ማስተርቤሽን ያን ያህል ስህተት ነው?

      ቁልፍ ጥቅስ

      ‘ከዝሙት ሽሹ። ዝሙት የሚፈጽም ሰው በራሱ አካል ላይ ኃጢአት እየሠራ ነው።’—1 ቆሮንቶስ 6:18

      ጠቃሚ ምክር

      ከተቃራኒ ፆታ ጋር በተያያዘ የሚከተለው ሐሳብ ጥሩ መመሪያ ይሆንሻል፦ ወላጆችሽ ቢኖሩ ኖሮ የማታደርጊውን ነገር በሌላ ጊዜም ልታደርጊው አይገባም።

      ይህን ታውቅ ነበር?

      አብዛኛውን ጊዜ ወንዶች ከአንዲት ሴት ጋር የፆታ ግንኙነት ከፈጸሙ በኋላ እሷን ትተው ከሌላ ሴት ጋር የፍቅር ጓደኝነት መመሥረት ይፈልጋሉ።

      ላደርጋቸው ያሰብኳቸው ነገሮች

      ከተቃራኒ ፆታ ጋር በምሆንበት ጊዜ ከሚከተሉት ሁኔታዎች መራቅ ይኖርብኛል፦ ․․․․․

      አንድ ወጣት ጭር ባለ አካባቢ እንድንገናኝ ቢጠይቀኝ እንዲህ እለዋለሁ፦ ․․․․․

      ከዚህ ርዕሰ ጉዳይ ጋር በተያያዘ ወላጆቼን ልጠይቃቸው የምፈልገው ነገር ․․․․․

      ምን ይመስልሃል?

      ● ከጋብቻ በፊት የፆታ ግንኙነት መፈጸም አስደሳች ቢመስልም ይህን ማድረግ ትክክል ያልሆነው ለምንድን ነው?

      ● አንድ ሰው የፆታ ግንኙነት እንድትፈጽሙ ቢጠይቅሽ ምን ታደርጊያለሽ?

      [በገጽ 176 ላይ የሚገኝ የተቀነጨበ ሐሳብ]

      “ክርስቲያን በመሆናችን በሌሎች ዘንድ ተወዳጅ እንድንሆን የሚያደርጉን ባሕርያት አሉን። ስለዚህ ሥነ ምግባር የጎደለው ድርጊት እንድንፈጽም ስንጠየቅ ንቁ መሆንና ጥያቄውን መቃወም ይኖርብናል። ላሉን መልካም ባሕርያት ትልቅ ቦታ ልንሰጥ ይገባል። በማይረባ ነገር አንለውጣቸው!”—ጆሽዋ

      [በገጽ 176 እና 177 ላይ የሚገኝ ሥዕል]

      ከጋብቻ በፊት የፆታ ግንኙነት መፈጸም አንድን ውብ ሥዕል የበር ምንጣፍ እንደ ማድረግ ነው

  • የማስተርቤሽን ልማድን ማሸነፍ የምችለው እንዴት ነው?
    ወጣቶች የሚጠይቋቸው ጥያቄዎችና ተግባራዊ መሆን የሚችሉ መልሶች፣ ጥራዝ 1
    • ምዕራፍ 25

      የማስተርቤሽን ልማድን ማሸነፍ የምችለው እንዴት ነው?

      “ማስተርቤሽን መፈጸም የጀመርኩት በስምንት ዓመቴ ነው። ከጊዜ በኋላ አምላክ ስለዚህ ጉዳይ ያለውን አመለካከት አወቅሁ። በዚህ ልማድ በተሸነፍኩ ቁጥር በራሴ በጣም አዝናለሁ። ‘አምላክ እንደ እኔ ያለውን ሰው እንዴት ሊወደው ይችላል?’ ብዬ አስባለሁ።”—ሉዊዝ

      የጉርምስና ዕድሜ የፆታ ስሜት በጣም የሚያይልበት ወቅት ነው። በዚህ የተነሳ አንዳንዶች ማስተርቤሽን መፈጸም ይጀምሩ ይሆናል።a ብዙ ሰዎች ይህ ልማድ ምንም ችግር እንደሌለው ይናገራሉ። “እንዲህ ብታደርግ ማንንም አትጎዳም” ይሉ ይሆናል። ይሁንና ከእንዲህ ዓይነቱ ልማድ ለመራቅ የሚያነሳሳ አጥጋቢ ምክንያት አለ። ሐዋርያው ጳውሎስ “በምድራዊ የአካል ክፍሎቻችሁ ውስጥ ያሉትን ዝንባሌዎች ግደሉ” ብሏል፤ ጳውሎስ ይህን ሲል ከጠቀሳቸው ነገሮች መካከል “የፆታ ምኞት” ይገኝበታል። (ቆላስይስ 3:5) ማስተርቤሽን የፆታ ምኞትን ከመግደል ይልቅ ጭራሹኑ ያባብሰዋል። ቀጥሎ የቀረቡትን ነጥቦችም ልብ በል፦

      ● ማስተርቤሽን አንድ ሰው የራስ ወዳድነት ዝንባሌ እንዲያድርበት ያደርጋል። ለምሳሌ፣ አንድ ሰው ይህን ድርጊት ሲፈጽም የራሱን ሥጋዊ ፍላጎት በማርካት ላይ ያተኩራል።

      ● የማስተርቤሽን ልማድ የተጠናወተው ግለሰብ፣ ተቃራኒ ፆታ ያላቸውን ሰዎች የእሱን የፆታ ፍላጎት ለማርካት እንደተፈጠሩ አድርጎ መመልከት ሊጀምር ይችላል።

      ● የማስተርቤሽን ልማድ የሚያስከትለው የራስ ወዳድነት አስተሳሰብ የትዳር ጓደኛሞች በፆታ ግንኙነት መርካት አስቸጋሪ እንዲሆንባቸው ሊያደርግ ይችላል።

      በውስጥህ የሚታገልህን የፆታ ስሜት ለማርካት ማስተርቤሽን ከመፈጸም ይልቅ ራስን የመግዛት ባሕርይ ለማዳበር ጥረት አድርግ። (1 ተሰሎንቄ 4:4, 5) መጀመሪያውኑ የፆታ ስሜትህ እንዲቀሰቀስ ከሚያደርጉ ሁኔታዎች መራቅህ በዚህ ረገድ እንደሚረዳህ መጽሐፍ ቅዱስ ይናገራል። (ምሳሌ 5:8, 9) ይሁንና ማስተርቤሽን የመፈጸም ልማድ ተጠናውቶህ ከሆነስ? ይህን ልማድ ለማሸነፍ ብትጥርም አልተሳካልህ ይሆናል። በመሆኑም ‘ለውጥ ማድረግና ከአምላክ የጽድቅ መሥፈርቶች ጋር ተስማምቼ መኖር አልችልም’ ብለህ ትደመድም ይሆናል። ፔድሮ የተባለ ወጣት እንደዚህ ይሰማው ነበር። እንዲህ ብሏል፦ “ይህ ልማድ ሲያገረሽብኝ በራሴ በጣም አዝናለሁ። ለሠራሁት ስህተት ፈጽሞ ይቅርታ ሊደረግልኝ እንደማይችል ይሰማኝ እንዲሁም መጸለይ እንኳ ይከብደኝ ነበር።”

      አንተም እንዲህ የሚሰማህ ከሆነ አይዞህ! ጨርሶ ልትለወጥ እንደማትችል አታስብ። በርካታ ወጣቶችም ሆኑ አዋቂዎች ይህን ልማድ ማሸነፍ ችለዋል። አንተም ልታሸንፈው ትችላለህ!

      የጥፋተኝነት ስሜትን ማሸነፍ

      ከላይ እንዳየነው ማስተርቤሽን የመፈጸም ልማድ ያላቸው ሰዎች ብዙውን ጊዜ በጥፋተኝነት ስሜት ይዋጣሉ። እርግጥ ነው፣ “አምላካዊ በሆነ መንገድ ማዘን” ይህን ልማድ ለማሸነፍ ኃይል ይሰጥሃል። (2 ቆሮንቶስ 7:11) በሌላ በኩል ግን ከልክ ያለፈ የጥፋተኝነት ስሜት ከጥቅሙ ጉዳቱ ሊያመዝን ይችላል። እንዲህ ያለው ስሜት በጣም ተስፋ ስለሚያስቆርጥህ ይህን ልማድ ለማሸነፍ የምታደርገውን ጥረት እርግፍ አድርገህ ልትተወው ትችላለህ።—ምሳሌ 24:10 NW

      ስለዚህ ስለ ጉዳዩ ሚዛናዊ አመለካከት ሊኖርህ ይገባል። ማስተርቤሽን ርኩስ ከሆኑ ድርጊቶች የሚፈረጅ ነው። “ለተለያየ ምኞትና ሥጋዊ ደስታ [እንድትገዛ]” እንዲሁም ጤናማ ያልሆነ ዝንባሌ እንዲኖርህ ያደርጋል። (ቲቶ 3:3) በሌላ በኩል ግን ማስተርቤሽን እንደ ዝሙት ያለ ከባድ የፆታ ብልግና አይደለም። (ይሁዳ 7 የ1954 ትርጉም) በመሆኑም ይህ ችግር ካለብህ ‘ይቅር የማይባል ኃጢአት ሠርቻለሁ’ ብለህ አትደምድም። ዋናው ነገር ይህን ድርጊት እንድትፈጽም የሚገፋፋህን ኃይለኛ ስሜት መቋቋምህና ጥረት ማድረግህን ፈጽሞ አለማቆምህ ነው!

      ልማዱ በሚያገረሽብህ ወቅት በቀላሉ ተስፋ ትቆርጥ ይሆናል። በዚህ ጊዜ በምሳሌ 24:16 ላይ የሚገኘውን “ጻድቅ ሰባት ጊዜ እንኳ ቢወድቅ ይነሣልና፤ ክፉዎች ግን በጥፋት ይወድቃሉ” የሚለውን ጥቅስ አስታውስ። ይህ ልማድ አንዳንድ ጊዜ ቢያገረሽብህ ክፉ ሰው ነህ ማለት አይደለም። በመሆኑም ተስፋ አትቁረጥ። ከዚህ ይልቅ ይህ ልማድ እንዲያገረሽብህ ያደረገውን ነገር ለማወቅና ያንን ደግመህ ላለመፈጸም ጥረት አድርግ።

      ጊዜ ወስደህ በይሖዋ ፍቅርና ምሕረት ላይ አሰላስል። በድክመቱ ተሸንፎ የነበረው መዝሙራዊው ዳዊት እንዲህ በማለት ጽፏል:- “አባት ለልጆቹ እንደሚራራ፣ እግዚአብሔር ለሚፈሩት እንዲሁ ይራራል። እርሱ አፈጣጠራችንን ያውቃልና፤ ትቢያ መሆናችንንም ያስባል።” (መዝሙር 103:13, 14) አዎን፣ ይሖዋ ፍጹማን አለመሆናችንን ግምት ውስጥ የሚያስገባ ከመሆኑም ሌላ “ይቅር ባይ” ነው። (መዝሙር 86:5) በሌላ በኩል ግን ለመሻሻል ጥረት እንድናደርግም ይፈልጋል። ታዲያ የማስተርቤሽን ልማድን ለማሸነፍ ምን እርምጃዎች መውሰድ ትችላለህ?

      መዝናኛህን ገምግም። የፆታ ስሜት እንዲቀሰቀስ የሚያደርጉ ፊልሞችን ወይም የቴሌቪዥን ፕሮግራሞችን ትመለከታለህ? አሊያም እንዲህ ዓይነት ድረ ገጾችን ትቃኛለህ? መዝሙራዊው “ከንቱ ነገር ከማየት ዐይኖቼን መልስ” በማለት ጥበብ የሚንጸባረቅበት ጸሎት አቅርቧል።b—መዝሙር 119:37

      አእምሮህ በሌሎች ነገሮች ላይ እንዲያተኩር አድርግ። ዊልያም የተባለ ክርስቲያን እንዲህ የሚል ምክር ሰጥቷል፦ “ከመተኛታችሁ በፊት መንፈሳዊ ነገሮችን አንብቡ። ስለ መንፈሳዊ ነገሮች እያሰባችሁ መተኛታችሁ በጣም ጠቃሚ ነው።”—ፊልጵስዩስ 4:8

      የሌሎችን እርዳታ ጠይቅ። ነገሩ ስለሚያሳፍርህ ለምትቀርበው ሰው መናገር ይከብድህ ይሆናል። ይሁንና ይህን ማድረግህ የማስተርቤሽን ልማድን ለማሸነፍ ሊረዳህ ይችላል! ዴቪድ የተባለ ክርስቲያን ይህ እውነት መሆኑን ከራሱ ተሞክሮ ተመልክቷል። እንዲህ ብሏል፦ “ከአባቴ ጋር ብቻችንን ሆነን ስለ ጉዳዩ ነገርኩት። አባቴ ምን እንዳለኝ መቼም አልረሳውም። እንድረጋጋ በሚያደርግ መንገድ ፈገግ ብሎ፣ ጉዳዩን ስለነገርኩት ደስ እንዳለው ገለጸልኝ። ያለብኝን ችግር ለእሱ ለመናገር ምን ያህል እንደተጨነቅሁ ተረድቶልኝ ነበር። በወቅቱ የሚያስፈልገኝ እንዲህ ዓይነት ማበረታቻ ነበር።

      “አባቴ፣ አንዳንድ ጥቅሶችን አውጥቶ ካነበበልኝ በኋላ ይህን ድርጊት በመፈጸሜ መጥፎ ሰው እንዳልሆንኩ አረጋገጠልኝ፤ ከዚያም ድርጊቱን አቅልዬ እንዳልመለከተው ደግሞ ሌሎች ጥቅሶችን አሳየኝ። በዚህ ልማድ ሳልሸነፍ የተወሰነ ጊዜ ለመቆየት ጥረት እንዳደርግ ያበረታታኝ ሲሆን በጉዳዩ ላይ ሌላ ጊዜ ለመነጋገር ተስማማን። በመሃል ቢያገረሽብኝ እንኳ ተስፋ እንዳልቆርጥ ከዚህ ይልቅ በልማዱ ሳልሸነፍ ረዘም ላለ ጊዜ ለመቆየት ጥረት እንዳደርግ አበረታታኝ።” ታዲያ ዴቪድ ምን ተሰምቶት ይሆን? “ችግሬን የሚያውቅና እርዳታ የሚሰጠኝ ሰው መኖሩ ከምንም በላይ ጠቅሞኛል” ብሏል።c

      በሚቀጥለው ምዕራፍ

      “አብሮ መውጣት” ችግር አለው?

      [የግርጌ ማስታወሻዎች]

      a ማስተርቤሽን የፆታ ስሜትን ለማነሳሳትና ለማርካት ብሎ የራስን የፆታ አካል የማሻሸት ልማድ ነው፤ በመሆኑም አንድ ሰው ሳያስበው ከሚያጋጥመው የፆታ ስሜት መነሳሳት ጋር ሊምታታ አይገባም። ለምሳሌ አንድ ልጅ እንቅልፍ ላይ እያለ ዘሩ ሊፈስ ወይም የፆታ ስሜቱ በመነሳሳቱ ከእንቅልፉ ሊነቃ ይችላል። በተመሳሳይም አንዳንድ ሴቶች ልክ የወር አበባ ዑደት ከመጀመሩ በፊት ወይም እንዳበቃ ሳያስቡት የፆታ ስሜታቸው ሊነሳሳ ይችላል። ከዚህ በተቃራኒ ማስተርቤሽን የሚያመለክተው ሆን ብሎ የፆታ ስሜትን ማነሳሳትን ነው።

      b ተጨማሪ ሐሳብ ለማግኘት የዚህን መጽሐፍ ጥራዝ 2 ምዕራፍ 33 ተመልከት።

      c ተጨማሪ ሐሳብ ለማግኘት የዚህን መጽሐፍ ጥራዝ 2 ከገጽ 239-241 ተመልከት።

      ቁልፍ ጥቅስ

      “ከወጣትነት ዕድሜ ጋር ተያይዘው ከሚመጡ ምኞቶች ሽሽ፤ ከዚህ ይልቅ በንጹሕ ልብ ጌታን ከሚጠሩት ጋር ጽድቅን፣ እምነትን፣ ፍቅርንና ሰላምን ለማግኘት ተጣጣር።”—2 ጢሞቴዎስ 2:22

      ጠቃሚ ምክር

      የፆታ ስሜትህ እያየለ ከመሄዱ በፊት ጸልይ። ፈተናውን ለመቋቋም የሚያስችልህ ‘ከሰብዓዊ ኃይል በላይ የሆነ ኃይል’ እንዲሰጥህ ይሖዋ አምላክን ጠይቀው።—2 ቆሮንቶስ 4:7

      ይህን ታውቅ ነበር?

      ለፆታ ስሜት በቀላሉ መሸነፍ የድክመት ምልክት ነው። በሌላ በኩል ግን አንድ ሰው ብቻውን እያለም እንኳ ራሱን መቆጣጠር መቻሉ ውስጣዊ ጥንካሬ እንዳለው ያሳያል።

      ላደርጋቸው ያሰብኳቸው ነገሮች

      አእምሮዬ ንጹሕ በሆኑ ነገሮች ላይ እንዲያተኩር እንዲህ አደርጋለሁ፦ ․․․․․

      ለስሜቴ ከመሸነፍ ይልቅ እንዲህ አደርጋለሁ፦ ․․․․․

      ከዚህ ርዕሰ ጉዳይ ጋር በተያያዘ ወላጆቼን ልጠይቃቸው የምፈልገው ነገር ․․․․․

      ምን ይመስልሃል?

      ● ይሖዋ “ይቅር ባይ” እንደሆነ ማስታወስ ጠቃሚ የሆነው ለምንድን ነው?—መዝሙር 86:5

      ● የፆታ ፍላጎትን የፈጠረው አምላክ ራሱ ሆኖ ሳለ ራስን የመግዛት ባሕርይን እንድታዳብር ትእዛዝ መስጠቱ በአንተ ላይ ምን እምነት እንዳለው ያሳያል?

      [በገጽ 182 ላይ የሚገኝ የተቀነጨበ ሐሳብ]

      “ችግሩን ማሸነፌ በይሖዋ ፊት ንጹሕ ሕሊና እንዲኖረኝ ረድቶኛል፤ ይህን ደግሞ በምንም ነገር ልለውጠው አልፈልግም!”—ሣራ

      [በገጽ 180 ላይ የሚገኝ ሥዕል]

      እየሮጥክ እያለ ብትወድቅ እንደገና ወደ ኋላ እንደማትመለስ ሁሉ የማስተርቤሽን ልማድ ቢያገረሽብህም እስካሁን ያደረግኸው ጥረት መና ይቀራል ማለት አይደለም

  • አንድ ሰው “አብሬው እንድወጣ” ቢጠይቀኝስ?
    ወጣቶች የሚጠይቋቸው ጥያቄዎችና ተግባራዊ መሆን የሚችሉ መልሶች፣ ጥራዝ 1
    • ምዕራፍ 26

      አንድ ሰው “አብሬው እንድወጣ” ቢጠይቀኝስ?

      “አንዳንድ ወጣቶች የፆታ ግንኙነት እስከ መፈጸም ይደርሱ እንደሆነ ለማየትና ከምን ያህል ሰዎች ጋር የፆታ ግንኙነት መፈጸም እንደሚችሉ ለማወቅ ሲሉ ብቻ ካገኙት ሰው ጋር ይወጣሉ።”—ፔኒ

      “ልጆቹ ስለዚህ ጉዳይ ሲያወሩ ትንሽ እንኳ አያፍሩም። የሴት ጓደኛ ብትኖራቸውም ከሌሎች ብዙ ሴቶች ጋር የፆታ ግንኙነት እንደፈጸሙ በጉራ ያወራሉ።”—ኤድዋርድ

      በዛሬው ጊዜ ብዙ ወጣቶች የፍቅር ስሜት ወይም ግንኙነት ሳይኖራቸው ካገኙት ሰው ጋር የፆታ ግንኙነት ይፈጽማሉ፤ እንዲያውም ስለዚህ ጉዳይ በኩራት ይናገራሉ። አንዳንዶች ደግሞ ፍቅረኛ መያዝ የሚያስከትለውን ኃላፊነት መሸከም ሳያስፈልጋቸው የፆታ ግንኙነት ለመፈጸም ሲሉ ብቻ የሚቀርቧቸው ሰዎች ይኖሯቸዋል።

      አንቺም እንዲህ ዓይነት ጥያቄ ሲቀርብልሽ ለመቀበል ትፈተኚ ይሆናል።a (ኤርምያስ 17:9) ቀደም ሲል የተጠቀሰው ኤድዋርድ እንዲህ ብሏል፦ “ብዙ ወጣት ሴቶች የፆታ ግንኙነት እንድንፈጽም ይጠይቁኛል፤ በክርስትና ሕይወቴ ውስጥ በጣም የከበደኝ ፈተና ይህ ነው። አልፈልግም ማለት ቀላል አይደለም!” አንድ ሰው እንዲህ ያለ ጥያቄ ቢያቀርብልሽ ልታስቢባቸው የሚገቡ አንዳንድ የመጽሐፍ ቅዱስ መመሪያዎች የትኞቹ ናቸው?

      ስህተት የሆነበትን ምክንያት ማወቅ

      ዝሙት ከባድ ኃጢአት ነው፤ እንዲያውም ይህን ድርጊት የሚፈጽሙ ሰዎች “የአምላክን መንግሥት አይወርሱም።” (1 ቆሮንቶስ 6:9, 10) ይህን ድርጊት የሚፈጽሙት ሰዎች “እንዋደዳለን” ይሉ ይሆናል፤ አሊያም ደግሞ በመካከላቸው የፍቅር ስሜት ላይኖር ይችላል፤ ያም ሆነ ይህ ከጋብቻ በፊት የፆታ ግንኙነት መፈጸማቸው ከባድ ኃጢአት ነው። በዚህ ረገድ የሚያጋጥምሽን ፈተና ለመቋቋም እንድትችዪ ዝሙትን በተመለከተ የይሖዋ ዓይነት አመለካከት ማዳበር ይኖርብሻል።

      “ይሖዋ የሚሰጠን መመሪያ ከሁሉ የተሻለ እንደሆነ እርግጠኛ ነኝ።”—ካረን፣ ካናዳ

      “በፈተናው ብትሸነፉ ወላጆቻችሁ፣ ጓደኞቻችሁና የጉባኤያችሁ አባላት ምን ያህል እንደሚያዝኑ አስቡ።”—ፒተር፣ ብሪታንያ

      ፍጹም ባለመሆንሽ ድርጊቱ አስደሳች እንደሆነ ይሰማሽ ይሆናል፤ ይሁንና ዝሙትን በተመለከተ ይሖዋ ያለው ዓይነት አመለካከት በማዳበር ‘ክፋትን መጥላት’ ትችያለሽ።—መዝሙር 97:10

      በተጨማሪም፦ ዘፍጥረት 39:7-9⁠ን አንብቢ። ዮሴፍ ከፆታ ብልግና ጋር በተያያዘ ያጋጠመውን ፈተና በመቋቋም ያሳየውን ድፍረትና ይህን ለማድረግ ያስቻለው ምን እንደሆነ ልብ በዪ።

      በምታምኚበት ነገር ኩሪ

      አብዛኛውን ጊዜ ወጣቶች ስለሚያምኑበት ነገር በኩራት ይናገራሉ። አንቺም የአምላክን መሥፈርቶች ከፍ አድርገሽ እንደምትመለከቺ በምግባርሽ የማሳየት ልዩ አጋጣሚ አለሽ። ከጋብቻ በፊት የፆታ ግንኙነት መፈጸም ትክክል እንዳልሆነ የምታምኚ መሆኑ ሊያሳፍርሽ አይገባም።

      “የምትመሩበት የሥነ ምግባር መሥፈርት እንዳላችሁ ገና ከጅምሩ በግልጽ ተናገሩ።”—አለን፣ ጀርመን

      “በሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤት አብረውኝ የሚማሩት ወንዶች አቋሜን ስለሚያውቁ እኔን ለማግባባት መሞከር ከንቱ ድካም መሆኑን ተገንዝበው ነበር።”—ቪኪ፣ ዩናይትድ ስቴትስ

      ለምታምኚበት ነገር ጠንካራ አቋም መያዝሽ ጎልማሳ ክርስቲያን መሆንሽን ይጠቁማል።—1 ቆሮንቶስ 14:20

      በተጨማሪም፦ ምሳሌ 27:11⁠ን አንብቢ። ትክክለኛውን ነገር ማድረግሽ የይሖዋን ልብ ምን ያህል እንደሚያስደስተው አስቢ!

      ቆራጥ ሁኚ!

      የሚቀርቡልሽን ጥያቄዎች ለመቀበል ፈቃደኛ እንዳልሆንሽ ብትናገሪም አንዳንዶች እየተግደረደርሽ እንደሆነ ሊሰማቸው ይችላል።

      “ሁሉ ነገራችሁ ማለትም አለባበሳችሁ፣ አነጋገራችሁ፣ የምትቀራረቧቸው ሰዎች እንዲሁም ሌሎችን የምትቀርቡበት መንገድ እንዲህ ያለውን ድርጊት ለመፈጸም ፈቃደኛ እንዳልሆናችሁ የሚያሳይ መሆን አለበት።”—ጆይ፣ ናይጄሪያ

      “ጥያቄያቸውን እንደማትቀበሉ መቼም ቢሆን ግልጽ ልታደርጉላቸው ይገባል። እንዲሁም ሌላ ዓላማ ያላቸው ወንዶች የሚሰጧችሁን ስጦታ ፈጽሞ አትቀበሉ። ምክንያቱም በምላሹ አንድ ነገር እንድታደርጉላቸው ሊጠብቁባችሁ ይችላሉ።”—ላራ፣ ብሪታንያ

      በአቋምሽ የምትጸኚ ከሆነ ይሖዋ ይረዳሻል። መዝሙራዊው ዳዊት ከግል ተሞክሮው በመነሳት ስለ ይሖዋ ሲናገር “ከታማኙ ጋር ታማኝ ትሆናለህ” ብሏል።—መዝሙር 18:25

      በተጨማሪም፦ 2 ዜና መዋዕል 16:9⁠ን አንብቢ። ይሖዋ ትክክል የሆነውን ነገር ለማድረግ የሚጥሩ ሰዎችን ለመርዳት ምን ያህል ዝግጁ እንደሆነ ልብ በዪ።

      አስተዋይ ሁኚ

      መጽሐፍ ቅዱስ “አስተዋይ ሰው አደጋ ሲያይ መጠጊያ ይሻል” ይላል። (ምሳሌ 22:3) ይህን ምክር እንዴት በተግባር ማዋል ትችያለሽ? የማስተዋል ችሎታሽን በመጠቀም ነው!

      “ስለ እንደዚህ ዓይነት ነገር ከሚያወሩ ሰዎች በተቻላችሁ መጠን ራቁ።”—ኔኦሚ፣ ጃፓን

      “አድራሻችሁን ወይም ስልክ ቁጥራችሁን የመሳሰሉ የግል መረጃዎችን አትስጡ።”—ዳያና፣ ብሪታንያ

      ስለ አነጋገርሽ፣ ስለ ምግባርሽ፣ ስለ ጓደኞችሽ እንዲሁም አዘውትረሽ ስለምትሄጂባቸው ቦታዎች ቆም ብለሽ አስቢ። ከዚያም ‘ሰዎች የፆታ ግንኙነት ለመፈጸም እንዲጠይቁኝ የሚጋብዙ ነገሮችን ሳይታወቀኝ እያደረግሁ ይሆን?’ ብለሽ ራስሽን ጠይቂ።

      በተጨማሪም፦ ዘፍጥረት 34:1, 2⁠ን አንብቢ። ዲና የተባለች አንዲት ወጣት ለፈተና ወደሚያጋልጥ ቦታ መሄዷ ምን መዘዝ እንዳስከተለባት ለማሰብ ሞክሪ።

      “አብሮ መውጣት” በይሖዋ ፊት እንደ ቀላል የሚታይ ነገር እንዳልሆነ አስተውዪ፤ አንቺም ይህን ድርጊት አቅልለሽ ልትመለከቺው አይገባም። ትክክል ለሆነው ነገር አቋም ከወሰድሽ ንጹሕ ሕሊና እንዲሁም ለራስሽ አክብሮት ይኖርሻል። ካርሊ የተባለች አንዲት ወጣት እንዲህ ብላለች፦ “የማንም ጊዜያዊ ስሜት ማርኪያ ለምን ትሆናላችሁ? በይሖዋ ፊት ያላችሁን ንጹሕ አቋም ለመጠበቅ ብዙ ጥረት አድርጋችኋል፤ ይህን አቋማችሁን እንዳታጡ ተጠንቀቁ!”

      በሚቀጥለው ምዕራፍ

      ወንዶች የሚወዱት ምን ዓይነት ሴቶችን ነው? ወንዶቹ ምን እንደሚሉ ስታነብቢ ትገረሚ ይሆናል!

      ቁልፍ ጥቅስ]

      “[በአምላክ] ፊት ቆሻሻና እድፍ ሳይኖርባችሁ በሰላም እንድትገኙ የተቻላችሁን ጥረት አድርጉ።”—2 ጴጥሮስ 3:14

      ጠቃሚ ምክር

      መልካም ባሕርያትን ለማፍራት ጥረት አድርጊ። (1 ጴጥሮስ 3:3, 4) እንዲህ ካደረግሽ የሚቀርቡሽም እንደ አንቺው ጥሩ ባሕርያት ያላቸው ሰዎች ይሆናሉ።

      ይህን ታውቅ ነበር?

      የፆታ ግንኙነት ይሖዋ በጋብቻ ውስጥ ደስታ እንድናገኝበት አስቦ ያደረገው ዝግጅት ነው፤ የተጋቡ ሰዎች፣ ዝሙት መፈጸም ከሚያስከትለው ጭንቀትና ጸጸት ነፃ ሆነው በፆታ ግንኙነት የሚገኘውን ደስታ ማጣጣም ይችላሉ።

      ላደርጋቸው ያሰብኳቸው ነገሮች

      ንጹሕ ሥነ ምግባር ይዞ በመኖር ረገድ እንደ ዮሴፍ ቆራጥ ለመሆን እንዲህ አደርጋለሁ፦ ․․․․․

      ዲና የሠራችውን ዓይነት ስህተት ላለመሥራት እንዲህ አደርጋለሁ፦ ․․․․․

      ከዚህ ርዕሰ ጉዳይ ጋር በተያያዘ ወላጆቼን ልጠይቃቸው የምፈልገው ነገር ․․․․․

      ምን ይመስልሃል?

      ● ከጋብቻ በፊት የፆታ ግንኙነት መፈጸም አስደሳች ቢመስልም ይህን ማድረግ ትክክል ያልሆነው ለምንድን ነው?

      ● አንድ ሰው የፆታ ግንኙነት እንድትፈጽሙ ቢጠይቅሽ ምን ታደርጊያለሽ?

      [በገጽ 185 ላይ የሚገኝ የተቀነጨበ ሐሳብ]

      “ቆራጥ መሆን ያስፈልጋል! አንድ ወጣት ሥነ ምግባር የጎደለው ነገር እንዳደርግ ሊያባብለኝ ሲሞክር ‘እጅህን ሰብስብ!’ ካልኩት በኋላ ኮስተር ብዬ ጥዬው ሄድኩ።”—ኤለን

      [በገጽ 187 ላይ የሚገኝ ሥዕል]

      ካገኙት ሰው ጋር የፆታ ግንኙነት መፈጸም ራስን ማራከስ ነው

      [የግርጌ ማስታወሻ]

      a በዚህ ምዕራፍ ውስጥ የተጠቀሱት ነጥቦች ለሁለቱም ፆታዎች ይሠራሉ።

አማርኛ ጽሑፎች (1991-2025)
ውጣ
ግባ
  • አማርኛ
  • አጋራ
  • የግል ምርጫዎች
  • Copyright © 2025 Watch Tower Bible and Tract Society of Pennsylvania
  • የአጠቃቀም ውል
  • ሚስጥር የመጠበቅ ፖሊሲ
  • ሚስጥር የመጠበቅ ማስተካከያ
  • JW.ORG
  • ግባ
አጋራ