የመጠበቂያ ግንብ የኢንተርኔት ቤተ መጻሕፍት
መጠበቂያ ግንብ
የኢንተርኔት ቤተ መጻሕፍት
አማርኛ
፦
  • ፡
  • መጽሐፍ ቅዱስ
  • የሕትመት ውጤቶች
  • ስብሰባዎች
  • የሕይወታችን ዓላማ
    ትምህርት ቤትና የይሖዋ ምሥክሮች
    • የሕይወታችን ዓላማ

      በመጀመሪያ የይሖዋ ምሥክሮችን ማንነትና የሕይወታችንን ዓላማ በአጭሩ መግለጽ ጠቃሚ ይሆናል። እኛ በመላው ዓለም በ231 አገሮች የምንገኝ ዓለም አቀፍ ክርስቲያናዊ ቡድን ነን። አምላክን የምናመልክበት መንገድ ጠቅላላውን የሕይወት አመለካከታችንንና አኗኗራችንን ይነካል።

      አምላክ በተወሰነ ቦታ የሚኖር ሕያው አካል መሆኑን ስለምናምን ከሱ ጋር የአባትና የልጅነት መቀራረብና ዝምድና እንዲኖረን ማድረግ አስፈላጊ ነገር እንደሆነ እናምናለን። (ማቴዎስ 6:9) ይህን ዝምድና ለማግኘት ከሚያስችሉን ነገሮች አንዱ እሱን በግል ስሙ ማወቅ ነው። መጽሐፍ ቅዱስ በመዝሙር 83:18 ላይ እንዲህ ይላል:- “ስምህ ይሖዋ የሆንከው አንተ ብቻ በምድር ላይ የሁሉ የበላይ እንደሆንህ አሕዛብ ይወቁ።”—አዓት

      ክርስቲያኖች እንደመሆናችን መጠን በሕይወታችን በሙሉ የአምላክ ልጅ ኢየሱስ ክርስቶስ የተወልንን አርዓያ ለመከተል እንፈልጋለን። ኢየሱስ ከፍተኛ ትምህርት የነበረው ሰው መሆኑን ያስተማራቸው ትምህርቶች ጥበብ የተሞላባቸው ከመሆናቸው ለመገንዘብ እንችላለን። ይሁን እንጂ ኢየሱስ እውቀቱን የተጠቀመበት ሌሎችን ለመጥቀም እንጂ ከፍተኛ ሀብት ወይም ትልቅ ማዕረግ ለማግኘት አልነበረም። በሕይወቱ የመጀመሪያውን ትልቅ ቦታ የሰጠው ለአምላክ አገልግሎት ነበር። “የእኔስ ምግብ የላከኝን ፈቃድ አደርግ ዘንድ ሥራውንም እፈጽም ዘንድ ነው” ብሏል።—ዮሐንስ 4:34

      እኛም ልክ እንደ ኢየሱስ ይሰማናል። በመላው ዓለም የሚኖሩ ምሥክሮች ይህን ፍላጎታቸውን ለመፈጸም ስለሚያስችላቸው ለትምህርት ከፍተኛ ግምት ይሰጣሉ። ወጣቶቻችን ስለ አካባቢያቸውና ስለ ሕይወታቸው እንዲሁም ስለ ሕይወት ምንነት ግንዛቤና እውቀት አግኝተው የእውቀት አድማሳቸውን እንዲያሰፉ እናበረታታለን። በዚህም ምክንያት ብዙ የሰብዓዊ እውቀት መስኮችን የሚዳስሰውን ንቁ! የተባለውን መጽሔታችንን አዘውትረው ያነባሉ። ለትምህርት ቤት ሥራቸውም ይጠቀሙበታል። አንዳንድ መምህራንም የሚሰጡትን ትምህርት ሲያዘጋጁ በዚህ መጽሔት ይጠቀማሉ።

      ልጆቻችን የሚያገኙት የትምህርት ማሠልጠኛ አብዛኞቻቸው የፈጠራ ችሎታቸውን እንዲያዳብሩ ረድቷቸዋል። ዘ ጆርናል ኦቭ ፐርሰናሊቲ የተሰኘው መጽሔት በ12 ዓመት ልጆች የ“ፈጠራ ችሎታ” ላይ በአውስትራሊያ ስለተደረገ ጥናት ሲዘግብ እንዲህ ብሏል:- “በተለይ ከሌሎች ጋር ሲነፃፀር ብዛት ያላቸው የይሖዋ ምሥክሮች የሆኑ ልጆች ከፍተኛ የፈጠራ ችሎታ እንዳላቸው መገንዘብ ተችሏል።” ይህ ሊሆን የቻለው የምሥክሮቹ ሃይማኖት የማሰብ ችሎታቸውን እንዲጠቀሙ ስለሚያበረታታ ነው።

      ወጣት ምሥክሮች ጥሩ ትምህርት ለማግኘት ፍላጎት ያላቸው ቢሆንም ትምህርት የሚከታተሉት ክብር ወይም ታዋቂነት ለማግኘት በማሰብ አይደለም። የሕይወታቸው ዋና ግብ ለአምላክ በሚያቀርቡት አገልግሎት ውጤታማና ፍሬያማ መሆን ነው። ለዚህም ከትምህርት ቤት የሚያገኙት ሥልጠና ከፍተኛ እገዛ እንደሚያደርግላቸው ይገነዘባሉ። ስለዚህ አብዛኛውን ጊዜ የሚመርጡት በዘመናዊው ዓለም ራሳቸውን ለመቻል የሚያበቋቸውን የትምህርት ዓይነቶች ነው። በዚህ የተነሣ አብዛኞቹ ሙያ ነክ ትምህርቶችን ሊወስዱ ወይም በሙያ ትምህርት ቤቶች ገብተው ሊማሩ ይችላሉ። ትምህርት ሲጨርሱም ዋነኛ ሥራቸው በሆነው በክርስቲያናዊ አገልግሎታቸው ላይ ለማተኮር የሚያስችላቸው ዓይነት ሥራ ለማግኘት ይፈልጋሉ።

      ለመጽሐፍ ቅዱስ ያላቸው አመለካከት

      ከላይ ከተባለው ለመረዳት እንደምትችሉት የይሖዋ ምሥክሮች ከሌሎች ብዙ ሃይማኖተኞች ይበልጥ መጽሐፍ ቅዱስን እንደ ሕይወታቸው መመሪያ አድርገው ይመለከቱታል። “ቅዱስ ጽሑፉ ሁሉ በአምላክ መንፈስ አነሳሽነት የተጻፈ” መሆኑን ያምናሉ።—2 ጢሞቴዎስ 3:16 አዓት

      ከእነዚያ ቃላት ጋር በመስማማትም በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ የተመዘገበው ነገር ሁሉ ትክክል እንደሆነና አንድን ክርስቲያን በሕይወቱ ሊመራው እንደሚገባ እናምናለን። በመሆኑም አንድ ወጣት ምሥክር ለአንዳንድ የትምህርት ቤት እንቅስቃሴዎች ያለው አመለካከት ለመጽሐፍ ቅዱስ ትምህርቶች ግድየለሽ የሆነ ተማሪ ካለው አመለካከት በጣም የተለየ ሊሆን ይችላል። ይህ ብሮሹር እነዚህን እንቅስቃሴዎችና የይሖዋ ምሥክሮች በእነዚህ እንቅስቃሴዎች ረገድ ያላቸውን አቋም ለምን እንደወሰዱ እንድትገነዘቡ ሊረዳችሁ ይሞክራል።

      እንደምታውቁት መጽሐፍ ቅዱስ ተወዳዳሪ የሌለው የትንቢት መጽሐፍ ስለሆነ ምሥክሮቹ በእነዚህ ትንቢቶች ማመናቸው ለትምህርት ቤት ባላቸው አመለካከት ላይ የሚያስከትለውን ውጤት ከግምት ውስጥ እንድታስገቡት ልንጠይቃችሁ እንወዳለን።

  • ስለ መጪው ጊዜ ያለን አመለካከት
    ትምህርት ቤትና የይሖዋ ምሥክሮች
    • ስለ መጪው ጊዜ ያለን አመለካከት

      ለሕይወት ያለንን አመለካከት በጥልቅ የሚነካ የመጽሐፍ ቅዱስ ትንቢት በራእይ 21:3, 4 ላይ ይገኛል። እንዲህ ይነበባል:- “እግዚአብሔር እሱ ራሱ ከእነርሱ [ከሰዎች] ጋር ሆኖ አምላካቸው ይሆናል። እንባዎችንም ከዓይኖቻቸው ያብሳል፣ ሞትም ከእንግዲህ ወዲህ አይሆንም፣ ኀዘንም ቢሆን ወይም ጩኸት ወይም ሥቃይ ከእንግዲህ ወዲህ አይሆንም፣ የቀደመው ሥርዓት አልፎአልና።”

      መጽሐፍ ቅዱስ አምላክ ስለሚፈጥረው የተሻለ ዓለም በተደጋጋሚ ይገልጻል:- “ጽድቅ የሚኖርባትን አዲስ ሰማይና አዲስ ምድር እንደተስፋ ቃሉ እንጠብቃለን።”—2 ጴጥሮስ 3:13፤ መዝሙር 37:9–11, 29፤ ኢሳይያስ 11:6–9፤ 35:5, 6

      ኢየሱስ ደቀ መዛሙርቱን “መንግሥትህ ትምጣ፤ ፈቃድህ በሰማይ እንደሆነች እንዲሁ በምድር ትሁን” ብለው እንዲጸልዩ ባስተማራቸው ጊዜ እንዳመለከተው የይሖዋ ምሥክሮች የሰው ልጆች ችግሮች ብቸኛ መፍትሔ የዚህ ተስፋ ፍጻሜ እንደሆነ ያምናሉ። (ማቴዎስ 6:10) የአምላክ መንግሥት እውነተኛ መስተዳድር እንደሆነች እናምናለን። (ኢሳይያስ 9:6, 7) የሰውን ልጆች የሚያስጨንቁትን ሁኔታዎች በሙሉ ከምድር ላይ አጥፍታ ዘላቂ ሰላም ለማምጣት የምትችል ብቸኛ መንግሥት ነች።

      የአምላክ መንግሥት መምጣት በአሁኑ ጊዜ ባሉት መንግሥታት ላይ ምን ውጤት እንደሚያስከትል በሌላ የመጽሐፍ ቅዱስ ትንቢት ላይ ተገልጿል:- “የሰማይ አምላክ ለዘላለም የማይፈርስ መንግሥት ያስነሣል. . . እነዚያንም መንግሥታት ሁሉ ትፈጫቸዋለች። ታጠፋቸውማለች። ለዘላለምም ትቆማለች።”—ዳንኤል 2:44

      ይህ ለውጥ በጣም እንደቀረበ ስለምናምን ወጣቶቻችን የአምላክ መንግሥት እውነተኛ መስተዳድር ስለመሆኗ ካለን እምነት ጋር ለሚስማማ የዕድሜ ልክ ሥራ መዘጋጀት ተገቢ መሆኑን ያምናሉ። ዋነኛ ዓላማችን በፊታችን ስላለው ብሩህ ተስፋ ለሰዎች መናገር ነው። በአሁኑ ጊዜ ያሉትን ኀዘኖችና ችግሮች አልፈን አምላክ ለሚያገለግሉት ያዘጋጃቸውን በረከቶች የምናገኝበትን ጊዜ በታላቅ ጉጉት እንጠብቃለን። እርግጠኛ የሆነው የአምላክ ተስፋ “ዓለሙም ምኞቱም ያልፋሉ። የእግዚአብሔርን ፈቃድ የሚያደርግ ግን ለዘላለም ይኖራል” ይላል። 1 ዮሐንስ 2:17

      ከዓለም መለየት

      የይሖዋ ምሥክሮች ስለ መጪው ጊዜ ያላቸው ይህ አመለካከት በመጀመሪያዎቹ ክርስቲያኖች ላይም ትልቅ ውጤት አስከትሎ እንደነበረ መገመት አያስቸግርም። ከዓለም የተለዩ ሰዎች እንዲሆኑ አድርጓቸዋል። ታሪክ ጸሐፊው ኢ ጂ ሃርዲ ክርስቲያኒቲ ኤንድ ዘ ሮማን ገቨርንመንት በተሰኘው መጽሐፋቸው ላይ እንደገለጹት “ክርስቲያኖቹ በዙሪያቸው በነበረው ዓለም እንግዶችና መጻተኞች ነበሩ። ዜግነታቸው በሰማይ ነበር። የሚጠብቋት መንግሥት የዚህ ዓለም አልነበረችም። ስለዚህ ከመጀመሪያ ጀምሮ በሕዝባዊ ጉዳዮች ውስጥ ለመግባት አለመፈለግ የክርስትና ግልጽ ገጽታ ሆነ።”

      ኢየሱስ ደቀ መዛሙርቱ ተለይተው ከሚታወቁባቸው ዋነኛ ባሕርያት አንዱ ከዓለም መለየታቸው እንደሆነ ገልጿል። “ከዓለም አይደሉም” ብሏል። (ዮሐንስ 17:16፤ 15:19) የይሖዋ ምሥክሮችም ከዚህ መሠረታዊ ሥርዓት ጋር በመስማማት “የዓለም ክፍል” ላለመሆን ይጥራሉ። እርግጥ ነው፣ እንዲህ ሲባል ራሳችንን ከዓለም ሰውረን ባህታውያን እንሆናለን ማለት አይደለም። በምንኖርበት ማኅበረሰብና በትምህርት ቤት ስላሉት ሰዎች ደህንነት ከልብ እናስባለን። ወጣቶቻችንም ለትምህርት ቤት እንቅስቃሴዎች ጠቃሚ አስተዋጽኦ ለማበርከት ይፈልጋሉ።

      ይሁን እንጂ ከዚህ ጋር አብረን “ዓለምም በሞላው በክፉው እንደተያዘ” መጽሐፍ ቅዱስ በግልጽ እንደሚናገር እናምናለን። (1 ዮሐንስ 5:19፤ ዮሐንስ 12:31፤ 2 ቆሮንቶስ 4:4) በመሆኑም የዓለም ተጽዕኖ በልጆቻችን ላይ ስለሚኖረው ጐጂ ውጤት እናስባለን። ብዙውን ጊዜ እኛ ከጥሩ ሥነ ምግባር ውጭ እንደሆነ የምናምነውን አኗኗር ዓለም አስውቦ ያቀርበዋል። ትምህርት ቤቶችም በዚህ ይነካሉ። ስለዚህ የይሖዋ ምሥክሮች በተቻለ መጠን ልጆቻቸው እነዚህን ከመሰሉት ጐጂ ተጽዕኖዎች እንዲርቁ ይፈልጋሉ።

አማርኛ ጽሑፎች (1991-2025)
ውጣ
ግባ
  • አማርኛ
  • አጋራ
  • የግል ምርጫዎች
  • Copyright © 2025 Watch Tower Bible and Tract Society of Pennsylvania
  • የአጠቃቀም ውል
  • ሚስጥር የመጠበቅ ፖሊሲ
  • ሚስጥር የመጠበቅ ማስተካከያ
  • JW.ORG
  • ግባ
አጋራ