የመጠበቂያ ግንብ የኢንተርኔት ቤተ መጻሕፍት
መጠበቂያ ግንብ
የኢንተርኔት ቤተ መጻሕፍት
አማርኛ
፦
  • ፡
  • መጽሐፍ ቅዱስ
  • የሕትመት ውጤቶች
  • ስብሰባዎች
  • be ጥናት 21 ገጽ 150-ገጽ 152 አን. 5
  • ጥቅስ ስታነብብ ተፈላጊውን ነጥብ ማጉላት

በዚህ ክፍል ውስጥ ምንም ቪዲዮ አይገኝም።

ይቅርታ፣ ቪዲዮውን ማጫወት አልተቻለም።

  • ጥቅስ ስታነብብ ተፈላጊውን ነጥብ ማጉላት
  • በቲኦክራሲያዊ የአገልግሎት ትምህርት ቤት ከሚሰጠው ሥልጠና ተጠቀም
  • ተመሳሳይ ሐሳብ ያለው ርዕስ
  • ጥቅሶችን ማንበብና ከጉዳዩ ጋር ማገናዘብ
    ቲኦክራሲያዊ የአገልግሎት ትምህርት ቤት መመሪያ መጽሐፍ
  • ቁልፍ ቃላትን በተገቢው ሁኔታ ማጥበቅ
    በቲኦክራሲያዊ የአገልግሎት ትምህርት ቤት ከሚሰጠው ሥልጠና ተጠቀም
  • ‘ለሕዝብ ለማንበብ መትጋት’
    ቲኦክራሲያዊ የአገልግሎት ትምህርት ቤት መመሪያ መጽሐፍ
  • ጥቅሶችን ከነጥቡ ጋር ማገናዘብ
    በቲኦክራሲያዊ የአገልግሎት ትምህርት ቤት ከሚሰጠው ሥልጠና ተጠቀም
ለተጨማሪ መረጃ
በቲኦክራሲያዊ የአገልግሎት ትምህርት ቤት ከሚሰጠው ሥልጠና ተጠቀም
be ጥናት 21 ገጽ 150-ገጽ 152 አን. 5

ጥናት 21

ጥቅስ ስታነብብ ተፈላጊውን ነጥብ ማጉላት

ምን ማድረግ ይኖርብሃል?

ለምታብራራው ነጥብ አጽንዖት ለመስጠት የሚረዱ ቃላትን አጉላ። ተገቢውን ስሜት በሚያንጸባርቅ መንገድ አንብብ።

አስፈላጊ የሆነው ለምንድን ነው?

ጥቅስ ስታነብብ ነጥቡን በተገቢው መንገድ ሳታጎላ ከቀረህ የጥቅሱ ኃይል ይዳከማል።

ከሰዎች ጋር ስትወያይም ይሁን ንግግር ስትሰጥ ስለ አምላክ ዓላማ የምትጠቅሰው ሐሳብ በአምላክ ቃል ላይ የተመሠረተ መሆን ይኖርበታል። ይህ ደግሞ ብዙውን ጊዜ የመጽሐፍ ቅዱስ ጥቅስ ማንበብ የሚጠይቅ ሲሆን ጥቅሶቹ በሚገባ መነበብ ይኖርባቸዋል።

ተገቢውን ስሜት በሚያንጸባርቅ መንገድ ማንበብ። ጥቅሶችን የምታነብበት መንገድ ድርቅ ያለ መሆን የለበትም። ጥቂት ምሳሌዎች ተመልከት። መዝሙር 37:​11⁠ን በምታነብበት ጊዜ ድምፅህ በጥቅሱ ላይ የተገለጸውን የሰላም ተስፋ እንደምትናፍቅ የሚያንጸባርቅ ሊሆን ይገባል። ስቃይና ሞት እንደሚያከትም የሚናገረውን ራእይ 21:​4⁠ን ስታነብብ የሰው ልጅ ስለሚያገኘው ታላቅ እፎይታ ያለህ ጥልቅ አድናቆት በድምፅህ ቃና መንጸባረቅ ይኖርበታል። ኃጢአቷ እስከ ሰማይ ከደረሰው ‘ከታላቂቱ ባቢሎን’ እንድንወጣ ጥሪ የሚያቀርበው ራእይ 18:​2, 4, 5 የመልእክቱን አጣዳፊነት በሚያሳይ መንገድ ሊነበብ ይገባል። ይህ ሲባል ግን በንባብህ የምታንጸባርቀው ስሜት ከውስጥህ የሚመነጭ እንጂ የተጋነነ መሆን የለበትም። የምታነብበትን ስሜት ለመመጠን የሚረዳህ ጥቅሱና የተጠቀሰበት ምክንያት ነው።

ትክክለኛዎቹን ቃላት ማጉላት:- በአንድ ጥቅስ ላይ የምትሰጠው ማብራሪያ በተወሰነው ክፍል ላይ ብቻ ያተኮረ ከሆነ በምታነብበት ጊዜ ያንን የጥቅሱን ክፍል ማጉላት ይኖርብሃል። ለምሳሌ ያህል ‘አስቀድሞ የእግዚአብሔርን መንግሥት ስለ መፈለግ’ እያብራራህ ከሆነ ማቴዎስ 6:​33⁠ን ስታነብብ “ጽድቁንም” ወይም “ይህም ሁሉ” የሚሉትን መግለጫዎች ማጉላት አይኖርብህም።

በአገልግሎት ስብሰባ ላይ ንግግር ስታቀርብ ማቴዎስ 28:​19⁠ን ለማንበብ ትፈልግ ይሆናል። ታዲያ ማጉላት የሚኖርብህ የትኞቹን ቃላት ነው? የመጽሐፍ ቅዱስ ጥናት በማስጀመር ረገድ ተጨማሪ ጥረት እንዲያደርጉ ማበረታታት ከፈለግህ “ደቀ መዛሙርት አድርጓቸው” የሚለውን ማጉላት ይኖርብሃል። በሌላ በኩል ደግሞ ከሌላ አገር ለመጡ ሰዎች የመጽሐፍ ቅዱስን እውነት የመንገር ክርስቲያናዊ ኃላፊነታችንን በተመለከተ ስትናገር ወይም አንዳንድ አስፋፊዎች እርዳታ ወደሚያስፈልግበት አካባቢ ሄደው እንዲያገለግሉ ስታበረታታ “አሕዛብን ሁሉ” የሚለውን የጥቅሱን ክፍል ማጉላት ትችላለህ።

ብዙውን ጊዜ ጥቅስ የሚጠቀሰው ለአንድ ጥያቄ መልስ ለመስጠት ወይም አንድን ሐሳብ ለመደገፍ ነው። በጥቅሱ ውስጥ ያለውን ሁሉንም ሐሳብ ካጎላህ አድማጮች ጥቅሱ ከጉዳዩ ጋር ያለውን ዝምድና ማስተዋል ሊቸገሩ ይችላሉ። ነጥቡ ለአንተ ግልጽ ሆኖልሃል ማለት ለእነርሱም ግልጽ ይሆንላቸዋል ማለት አይደለም።

ለምሳሌ ያህል የያዝኸው መጽሐፍ ቅዱስ በመዝሙር 83:​18 ላይ መለኮታዊውን ስም የሚጠቀም ከሆነ “ልዑል” የሚለውን ቃል ብቻ ብታጎላ የምታነጋግረው ሰው አምላክ የግል መጠሪያ አለው የሚለውን ለአንተ ግልጽ የሆነ እውነት ሳያስተውል ሊቀር ይችላል። ጠበቅ አድርገህ መግለጽ ያለብህ “ይሖዋ” የሚለውን ስም ነው። ይሁን እንጂ ስለ ይሖዋ ሉዓላዊነት ለማስረዳት በማሰብ ይህንኑ ጥቅስ ስታነብብ ማጉላት ያለብህ “ልዑል” የሚለውን ቃል ነው። በተመሳሳይም እምነት በሥራ መገለጽ እንዳለበት ለማስረዳት አስበህ ያዕቆብ 2:​24⁠ን ስታነብብ “በሥራ” የሚለውን ቃል ትተህ “እንዲጸድቅ” የሚለውን ቃል ብታጎላ አንዳንድ አድማጮችህ የተፈለገውን ነጥብ ላይረዱት ይችላሉ።

ሮሜ 15:​7-13⁠ም ግሩም ምሳሌ ይሆናል። ይህ ጥቅስ ሐዋርያው ጳውሎስ ከአሕዛብ ወገን የሆኑና በትውልድ አይሁዳዊ የሆኑ ክርስቲያኖችን ላቀፈ አንድ ጉባኤ በጻፈው መልእክት ውስጥ የሚገኝ ነው። ጳውሎስ የክርስቶስ አገልግሎት የተገረዙ አይሁዳውያንን ብቻ ሳይሆን ከአሕዛብ የመጡትን ጭምር የሚጠቅም እንደሆነ እያብራራ ነው። ይህም ‘አሕዛብ ስለ ምሕረቱ እግዚአብሔርን ያከብሩ ዘንድ’ ምክንያት እንደሚሆን ጠቅሷል። ጳውሎስ አሕዛብ ያገኙትን ይህንን አጋጣሚ የሚያረጋግጡ አራት ጥቅሶች ተጠቅሟል። እያብራራ ያለውን ሐሳብ ለማጉላት ከፈለግህ እነዚህን ጥቅሶች እንዴት ልታነባቸው ይገባል? ለማጉላት በፈለግኸው ቃል ላይ ምልክት የምታደርግ ከሆነ ከቁጥር 8 እና 9 “አሕዛብ፣” ከቁጥር 11 “እናንተ አሕዛብ ሁላችሁ” እና “ሕዝቦቹም ሁሉ” እንዲሁም ከቁጥር 12 “አሕዛብ” የሚሉትን ቃላት ትመርጥ ይሆናል። እነዚህን ቃላት እያጎላህ ሮሜ 15:​7-13⁠ን ለማንበብ ሞክር። እንዲህ ካደረግህ ጳውሎስ እያብራራው ያለው ነጥብ ይበልጥ ግልጽና ለመረዳትም ቀላል ይሆናል።

ለማጉላት የሚረዱ ዘዴዎች። ለየት ብለው እንዲታዩ የምትፈልጋቸውን መልእክት አዘል ቃላት በተለያየ መንገድ ማጉላት ትችል ይሆናል። ይሁንና የምትጠቀምበት ዘዴ ከጥቅሱ ይዘትና ከንግግሩ ነጥቦች ጋር የሚጣጣም መሆን ይኖርበታል። ከዚህ ቀጥሎ ለማጉላት የሚረዱ አንዳንድ ዘዴዎችን እንመለከታለን።

ድምፅን መለዋወጥ። ይህም መልእክት አዘል የሆኑት ቃላት ከቀረው ዓረፍተ ነገር ለየት ብለው እንዲታዩ የሚያደርግን ማንኛውንም የድምፅ ለውጥ ያመለክታል። በአንዳንድ ቋንቋዎች የድምፅን መጠን በመጨመር ወይም በመቀነስ ማጉላት ይቻል ይሆናል። በሌሎች ቋንቋዎች ግን እንዲህ ማድረግ ጭራሽ ትርጉሙን ሊቀይረው ይችላል። ቁልፍ የሆነው ቃል ላይ ስትደርስ ዝግ ካልክ ለዚያ ቃል ትኩረት እንዲሰጠው ታደርጋለህ። ቋንቋህ ድምፅን በመለዋወጥ ቃላትን ማጉላት የማይፈቅድ ከሆነ ይህንን ለማድረግ በቋንቋው የተለመደውን ማንኛውንም ዘዴ መጠቀም ያስፈልግ ይሆናል።

ቆም ማለት። ልታጎላው ከፈለግኸው የጥቅሱ ክፍል በፊት ወይም በኋላ ወይም በሁለቱም ቦታ ቆም ማለት ይቻላል። ዋናው ነጥብ ላይ ስትደርስ ቆም ማለት አድማጮች ቀጥሎ የሚነበበውን በጉጉት እንዲጠባበቁ የሚያደርግ ሲሆን ከተነበበ በኋላ ቆም ማለት ደግሞ ጉዳዩን ይበልጥ እንዲያስቡበት ያደርጋል። ሆኖም አሁንም አሁንም ቆም የምትል ከሆነ ጎላ ብሎ የሚታይ ነጥብ አይኖርም።

መደጋገም። ወደኋላ መለስ ብለህ ቃሉን ወይም ሐረጉን ደግመህ በማንበብ አንድን ነጥብ ማጉላት ትችላለህ። ብዙውን ጊዜ የተሻለ የሚሆነው ጥቅሱን አንብበህ ከጨረስህ በኋላ ማጉላት የምትፈልገውን ሐሳብ መድገሙ ነው።

አካላዊ መግለጫ። ፊታችን ላይ የሚነበበውን ስሜት ጨምሮ ማንኛውም አካላዊ መግለጫ ቃሉን ይበልጥ ያጠናክረዋል።

የድምፅ ቃና። በአንዳንድ ቋንቋዎች ቃላቱ የሚነበቡበት ቃና ትርጉማቸውን ሊለውጥ እንዲሁም ለየት ብለው እንዲታዩ ሊያደርግ ይችላል። በዚህም ረገድ በተለይ ደግሞ አነጋገሩ የምጸት በሚሆንበት ጊዜ ጥንቃቄ ማድረግ ያስፈልጋል።

ጥቅሱን ሌሎች በሚያነቡበት ጊዜ። የምታነጋግረው ሰው ጥቅሱን ሲያነብብ የማይፈለገውን ቃል ሊያጎላ ወይም ደግሞ ምንም ቃል ሳያጎላ ሊቀር ይችላል። በዚህ ጊዜ ምን ማድረግ ትችላለህ? ብዙውን ጊዜ የጥቅሱን መልእክት ማብራራቱ የተሻለ ይሆናል። ከዚያ በኋላ ያንን ሐሳብ የሚያስተላልፉት የጥቅሱ ቃላት ጎላ ብለው እንዲታዩ ማድረግ ትችል ይሆናል።

ይህን ችሎታ ማዳበር የሚቻለው እንዴት ነው?

  • ልታነብበው ያሰብከውን ማንኛውንም ጥቅስ በተመለከተ እንዲህ እያልክ ጠይቅ:- ‘እነዚህ ቃላት የሚያስተላልፉት ስሜት ምንድን ነው? ሳነብብስ ይህንን ስሜት ማንጸባረቅ የምችለው እንዴት ነው?’

  • ልታነብበው ያሰብከውን እያንዳንዱን ጥቅስ በተመለከተ ‘ይህንን ጥቅስ የማነብበት ዓላማ ምንድን ነው? ይህንን ዓላማ ለማሳካትስ ማጉላት ያለብኝ የትኞቹን ቃላት ነው?’ እያልክ ራስህን ጠይቅ።

መልመጃ፦ (1) በመስክ አገልግሎት ልትጠቀምበት ያሰብከውን አንድ ጥቅስ መርጠህ ተገቢውን ስሜት በሚያንጸባርቅ መንገድ ማንበብ ተለማመድ። ጥቅሱን የምታነብበትን ዓላማ በማሰብ ትክክለኛውን ቃል (ቃላት) እያጎላህ ድምፅህን ከፍ አድርገህ አንብብ። (2) በዚህ ሳምንት ከሚጠና ጽሑፍ ላይ ከመጽሐፍ ቅዱስ በቀጥታ የተወሰደ ጥቅስ የሚገኝበት አንድ አንቀጽ ምረጥ። የጥቅሶቹን አገባብ ልብ በል። መልእክት አዘል በሆኑት ቃላት ላይ ምልክት አድርግ። ከዚያም ተፈላጊ የሆነውን የጥቅሶቹን ነጥብ በተገቢው መንገድ እያጎላህ መላውን አንቀጽ ድምፅህን ከፍ አድርገህ አንብብ።

    አማርኛ ጽሑፎች (1991-2025)
    ውጣ
    ግባ
    • አማርኛ
    • አጋራ
    • የግል ምርጫዎች
    • Copyright © 2025 Watch Tower Bible and Tract Society of Pennsylvania
    • የአጠቃቀም ውል
    • ሚስጥር የመጠበቅ ፖሊሲ
    • ሚስጥር የመጠበቅ ማስተካከያ
    • JW.ORG
    • ግባ
    አጋራ