-
“ተዘጋጅታችሁ ኑሩ”የመንግሥት አገልግሎት—2003 | ኅዳር
-
-
“ተዘጋጅታችሁ ኑሩ”
1 ኢየሱስ የዚህን ሥርዓት መደምደሚያ አስመልክቶ በተናገረው ትንቢት ላይ በዕለት ተዕለት የሕይወት ሩጫ ከልክ በላይ መጠላለፍን በሚመለከት አስጠንቅቆ ነበር። (ማቴ. 24:36-39፤ ሉቃስ 21:34, 35) ታላቁ መከራ በማንኛውም ጊዜ ሊጀምር ስለሚችል “ተዘጋጅታችሁ ኑሩ፣ የሰው ልጅ በማታስቡበት ሰዓት ይመጣልና” የሚለውን የኢየሱስ ምክር ተግባራዊ ማድረጋችን በጣም አስፈላጊ ነው። (ማቴ. 24:44) በዚህ ረገድ ምን ሊረዳን ይችላል?
2 የኑሮ ጭንቀቶችንና ጊዜን የሚያባክኑ ነገሮችን ማሸነፍ:- ልንጠነቀቅበት የሚገባን አንዱ መንፈሳዊ ወጥመድ ‘ስለ ኑሮ መጨነቅ’ ነው። (ሉቃስ 21:34 አ.መ.ት) በአንዳንድ አገሮች ድህነት፣ ሥራ ማጣትና የኑሮ ውድነት ለሕይወት የሚያስፈልጉ መሠረታዊ ነገሮችን ማግኘት አስቸጋሪ እንዲሆን አድርገውታል። በሌሎች አገሮች ደግሞ ቁሳዊ ንብረቶችን ማፍራት ከባድ አይደለም። ሆኖም ስለ ቁሳዊ ነገሮች ከልክ በላይ መጨነቅ ከጀመርን ትኩረታችንን መንግሥቱን በሚመለከቱ ተጨባጭ እውነታዎች ላይ ማድረግ ያቅተናል። (ማቴ. 6:19-24, 31-33) ክርስቲያናዊ ስብሰባዎች ትኩረታችንን በመንግሥቱ ላይ እንድናደርግ ይረዱናል። በሁሉም ስብሰባዎች ላይ የመገኘት ግብ አለህ?—ዕብ. 10:24, 25
3 ዛሬ ያለው ዓለም ውድ ጊዜያችንን ሊሻሙብን የሚችሉ በርካታ ነገሮች ያቀርብልናል። አንድ ሰው ኢንተርኔት በመቃኘት፣ ኢ-ሜይል በመጻጻፍ ወይም የኮምፒውተር ጨዋታዎች በመጫወት ከልክ በላይ ጊዜ የሚያጠፋ ከሆነ ኮምፒውተር ወጥመድ ሊሆንበት ይችላል። ቴሌቪዥን ወይም የቪዲዮ ፊልሞችን በመመልከት፣ ዓለማዊ ጽሑፎችን በማንበብ ወይም በስፖርትና በሌሎች የትርፍ ጊዜ ማሳለፊያዎች በርካታ ሰዓታት ማባከን ለመንፈሳዊ ጉዳዮች ልናውለው የምንችለውን ጊዜና ጉልበት ሊያሟጥጥብን ይችላል። መዝናኛ ጊዜያዊ እርካታ ሊያስገኝልን ቢችልም መጽሐፍ ቅዱስን በግልና በቤተሰብ ማጥናት ግን ዘላቂ ጥቅሞች አሉት። (1 ጢሞ. 4:7, 8) በየዕለቱ በአምላክ ቃል ላይ ለማሰላሰል ጊዜ ትመድባለህ?—ኤፌ. 5:15-17
4 የይሖዋ ድርጅት “ሊመጣ ካለው ከዚህ ሁሉ ለማምለጥ፣ በሰው ልጅም ፊት ለመቆም” እንድንችል መንፈሳዊ ትምህርት የምናገኝበትን ፕሮግራም ስላዘጋጀልን ምንኛ አመስጋኞች መሆን ይኖርብናል! (ሉቃስ 21:36) በእነዚህ መንፈሳዊ ዝግጅቶች በሚገባ በመጠቀምና ‘ተዘጋጅተን በመኖር’ “ኢየሱስ ክርስቶስ ሲገለጥ፣ ለምስጋናና ለክብር ለውዳሴም” የሚሆን እምነት ይኑረን።—1 ጴጥ. 1:6, 7
-
-
ምስጋና መንፈስ ያድሳልየመንግሥት አገልግሎት—2003 | ኅዳር
-
-
ምስጋና መንፈስ ያድሳል
1 ትንሿ ልጅ አልጋዋ ውስጥ ገብታ እያለቀሰች “ዛሬ ጨዋ ልጅ ሆኜ አልዋልኩም?” በማለት እናቷን ትጠይቃታለች። የልጅቷ ጥያቄ እናትየዋን ሳያስገርማት አልቀረም። የዚያን ዕለት ትንሿ ልጅ ጨዋ ሆና መዋሏን ብታስተውልም አንድም ጊዜ አላመሰገነቻትም። የዚህች ትንሽ ልጅ እንባ ሕፃን አዋቂ ሳይባል ሁላችንም ምስጋና እንደሚያስፈልገን ያስገነዝበናል። እኛስ ሰዎች ላደረጉት መልካም ነገር አድናቆታችንን በመግለጽ ሌሎችን እናበረታታለን?—ምሳሌ 25:11
2 ክርስቲያን ባልንጀሮቻችን እንድናመሰግናቸው የሚያደርጉ ብዙ ጥሩ ነገሮች አሏቸው። ሽማግሌዎች፣ የጉባኤ አገልጋዮችና አቅኚዎች ኃላፊነቶቻቸውን ለመወጣት ጠንክረው ይሠራሉ። (1 ጢሞ. 4:10፤ 5:17) ፈሪሃ አምላክ ያላቸው ወላጆች ልጆቻቸውን በይሖዋ መንገድ ለማሳደግ አቅማቸው የፈቀደውን ሁሉ ያደርጋሉ። (ኤፌ. 6:4) ክርስቲያን ወጣቶች ‘የዓለም መንፈስ” እንዳያሸንፋቸው ብርቱ ትግል ያደርጋሉ። (1 ቆሮ. 2:12፤ ኤፌ. 2:1-3) ሌሎች ደግሞ የዕድሜ መግፋት፣ የጤና ችግር ወይም ሌሎች ፈተናዎች እያሉባቸውም ይሖዋን በታማኝነት ያገለግላሉ። (2 ቆሮ. 12:7) እነዚህ ሁሉ ምስጋና ይገባቸዋል። ታዲያ መልካም ጥረታቸውን ጠቅሰን እናመሰግናቸዋለን?
3 ለይታችሁ በመጥቀስ በግለሰብ ደረጃ አመስግኑ:- ሁላችንም መላው ጉባኤ ከመድረክ ሲመሰገን ስንሰማ በእጅጉ እንደሰታለን። ይሁን እንጂ ምስጋና ይበልጥ መንፈስን የሚያድሰው በግለሰብ ደረጃ ሲሰጥ ነው። ለምሳሌ ያህል ጳውሎስ በሮም ለሚኖሩ ክርስቲያኖች በጻፈው ደብዳቤ ምዕራፍ 16 ላይ ፌቤን፣ ጵርስቅላና አቂላ፣ ፕሮፊሞና እና ጢሮፊሞሳ፣ ጠርሲዳ እንዲሁም ሌሎች ያደረጉትን በቀጥታ በመጥቀስ አመስግኗቸዋል። (ሮሜ 16:1-4, 12) እነዚህ ታማኝ ክርስቲያኖች በጳውሎስ ቃላት ምን ያህል ተበረታተው ይሆን! እንዲህ ያለው ምስጋና ወንድሞቻችንና እህቶቻችን እንደሚፈለጉ እንዲሰማቸው የሚያደርግ ከመሆኑም በላይ እርስ በርስ ይበልጥ ያቀራርበናል። አንተስ የሚያስመሰግኑ ነገሮችን በቀጥታ በመጥቀስ በቅርቡ በግል ያመሰገንከው ሰው አለ?—ኤፌ. 4:29
4 ከልብ የመነጨ ይሁን:- ምስጋና መንፈስን የሚያድስ እንዲሆን ከተፈለገ ከልብ የመነጨ መሆን ይኖርበታል። ሰዎች የምንናገረው ነገር ከልብ ይሁን ወይም እንዲያው ‘ሽንገላ’ መለየት አያቅታቸውም። (ምሳሌ 28:23 አ.መ.ት) የሰዎችን መልካም ጎን ለመመልከት ጥረት ባደረግን መጠን ልባችን እነርሱን ለማመስገን ይገፋፋል። እንግዲያው ‘በጊዜው የተነገረ ቃል መልካም’ መሆኑን ተገንዝበን ከልባችን በማመስገን ረገድ ለጋሶች እንሁን።—ምሳሌ 15:23
-