-
ጽናት ይክሳልየመንግሥት አገልግሎት—2004 | ነሐሴ
-
-
ጽናት ይክሳል
1 “ጸንታችሁም በመቆም ነፍሳችሁን ታተርፋላችሁ።” (ሉቃስ 21:19) ኢየሱስ ስለ ‘ሥርዓቱ መጨረሻ’ የተናገረው ትንቢት ክፍል የሆኑት እነዚህ ቃላት ታማኝነታችንን ከመጠበቅ ጋር በተያያዘ በርካታ ፈተናዎች ሊደርሱብን እንደሚችሉ መጠበቅ እንዳለብን በግልጽ ያሳያሉ። ይሁን እንጂ ከይሖዋ በምናገኘው ብርታት ሁላችንም ‘እስከ መጨረሻው መጽናትና መዳን’ እንችላለን።—ማቴ. 24:3, 13፤ ፊልጵ. 4:13
2 ስደት፣ የጤና እክል፣ የኢኮኖሚ ችግርና የመንፈስ ጭንቀት እያንዳንዱን ቀን ፈታኝ ሊያደርግብን ይችላል። ይሁን እንጂ ሰይጣን ለይሖዋ ያለንን ታማኝነት እንድናጓድል ለማድረግ እየጣረ መሆኑን መዘንጋት አይኖርብንም። በሰማይ ለሚኖረው አባታችን ያለንን ታማኝነት ጠብቀን በምናሳልፈው በእያንዳንዱ ቀን ይሖዋን ለሚሰድበው ለሰይጣን መልስ እየሰጠን ነው። መከራ ሲያጋጥመን የምናፈሰው ‘እንባ’ ተረስቶ እንደማይቀር ማወቃችን ምንኛ ያስደስታል! ያፈሰስነው እንባ በይሖዋ ፊት ውድ ከመሆኑም በላይ በታማኝነት መጽናታችን ልቡን ደስ ያሰኘዋል።—መዝ. 56:8፤ ምሳሌ 27:11
3 በመከራ የተፈተኑ ባሕርያት፦ መከራ እምነታችን ደካማ መሆኑን እንዲሁም እንደ ኩራት ወይም ትዕግሥት ማጣት ያለ ድክመት እንዳለብን ሊጠቁም ይችላል። ቅዱስ ጽሑፋዊ ያልሆኑ መንገዶችን ተጠቅሞ ፈተናን ለማስቀረት ወይም ለማምለጥ ከመሞከር ይልቅ “ትዕግሥት ሥራውን ይፈጽም” ዘንድ አጋጣሚ እንድንሰጠው የሚናገረውን የመጽሐፍ ቅዱስ ምክር መከተል አለብን። ለምን? ምክንያቱም ፈተናዎችን በጽናት ማለፋችን “ፍጹማንና ምሉአን” እንድንሆን ይረዳናል። (ያዕ. 1:2-4) ጽናት እንደ ምክንያታዊነት፣ ርኅሩኅነትና መሐሪነት ያሉ በዋጋ ሊተመኑ የማይችሉ ባሕርያትን እንድናዳብር ሊረዳን ይችላል።—ሮሜ 12:15
4 በፈተና የጠራ እምነት፦ ፈተናዎችን በጽናት ስንወጣ በአምላክ ዘንድ ትልቅ ዋጋ ያለውን በመከራ ተፈትኖ የጠራ እምነት እናዳብራለን። (1 ጴጥ. 1:6, 7) እንዲህ ያለው እምነት ወደፊት የሚያጋጥሙንን ፈተናዎች በታማኝነት ለማለፍ ያስችለናል። ከዚህም በላይ የአምላክን ሞገስ እንዳገኘን የሚሰማን ሲሆን ይህም ይበልጥ ሕያውና ጠንካራ የሆነ ተስፋ እንዲኖረን ያደርጋል።—ሮሜ 5:3-5
5 ጽናት የሚያስገኝልን ከሁሉ የላቀ ሽልማት በያዕቆብ 1:12 ላይ እንዲህ ተብሎ ተገልጿል:- “በፈተና የሚጸና ሰው የተባረከ ነው፤ ምክንያቱም ፈተናን ሲቋቋም . . .የሕይወትን አክሊል ያገኛል።” እንግዲያው ይሖዋ “ለሚወዱት” የተትረፈረፈ በረከት እንደሚሰጥ ሙሉ በሙሉ በመተማመን ታማኞች ሆነን እንቀጥል።
-
-
ክፍል 2—የመጽሐፍ ቅዱስ ጥናቶቻችን እድገት እንዲያደርጉ መርዳትየመንግሥት አገልግሎት—2004 | ነሐሴ
-
-
ክፍል 2—የመጽሐፍ ቅዱስ ጥናቶቻችን እድገት እንዲያደርጉ መርዳት
ጥናቱን ለመምራት መዘጋጀት
1 መጽሐፍ ቅዱስ በምናስጠናበት ወቅት ውጤታማ በሆነ መንገድ ማስተማር የሚጠናውን ጽሑፍ ከማብራራትና ምዕራፍና ቁጥራቸው ብቻ የተጠቀሱትን ጥቅሶች ከማንበብ የበለጠ ነገርን ይጨምራል። ትምህርቱን የተማሪውን ልብ በሚነካ መንገድ ማቅረብ ይኖርብናል። ይህ ደግሞ የተማሪውን ሁኔታ በአእምሮ ይዞ በሚገባ መዘጋጀትን ይጠይቃል።—ምሳሌ 15:28
2 መዘጋጀት ያለብህ እንዴት ነው? ስለ ተማሪውና ስለሚያስፈልጉት ነገሮች ለይሖዋ በመጸለይ ዝግጅትህን ጀምር። የተማሪውን ልብ መንካት እንድትችል የይሖዋን እርዳታ ጠይቅ። (ቆላ. 1:9, 10) የምዕራፉን ወይም የትምህርቱን ጭብጥ በሚገባ ለመረዳት እንድትችል ጊዜ ወስደህ በርዕሱ፣ በንዑስ ርዕሶቹና በሥዕሎቹ ላይ አሰላስልባቸው። ‘የምዕራፉ ፍሬ ነገር ምንድን ነው?’ ብለህ ራስህን ጠይቅ። ይህ በጥናቱ ወቅት በዋና ዋና ነጥቦች ላይ እንድታተኩር ይረዳሃል።
3 የምታጠኑትን ጽሑፍ አንቀጽ በአንቀጽ በጥንቃቄ ተዘጋጅ። የጥያቄዎቹን መልሶች ፈልገህ ካገኘህ በኋላ ቁልፍ በሆኑት ቃላትና ሐረጎች ላይ ብቻ ምልክት አድርግ። ምዕራፍና ቁጥራቸው ብቻ የተሰጡት ጥቅሶች ከአንቀጹ ሐሳብ ጋር ያላቸውን ግንኙነት ተመልከት። እንዲሁም በጥናቱ ወቅት የምታነቧቸውን ጥቅሶች ምረጥ። በጽሑፉ ኅዳግ ላይ ጥቅሶቹን በሚመለከት አጠር ያሉ ማስታወሻዎችን መጻፍ ትችላለህ። ተማሪው እየተማረ ያለው ከአምላክ ቃል መሆኑ ግልጽ ሊሆንለት ይገባል።—1 ተሰ. 2:13
4 ትምህርቱን ለተማሪህ እንደሚስማማ አድርገህ አቅርበው፦ ከዚህ በመቀጠል ተማሪህን በአእምሮህ ይዘህ ትምህርቱን በድጋሚ ከልሰው። ጥያቄ ሊያነሳባቸው የሚችላቸውን ነጥቦችና ለመረዳት ወይም ለመቀበል ሊከብዱት የሚችሉ ሐሳቦችን አስቀድመህ ለመገመት ሞክር። ‘መንፈሳዊ እድገት ለማድረግ እንዲችል ሊያስተውለው የሚገባው ነጥብ ወይም ማሻሻል ያለበት ጉዳይ ምንድን ነው? ልቡን መንካት የምችለው እንዴት ነው?’ በማለት ራስህን ጠይቅ። ከዚያም በዚህ መሠረት ትምህርቱን እንደሚስማማ አድርገህ አቅርበው። አንዳንድ ጊዜ ተማሪህ አንድን ነጥብ ወይም ጥቅስ በሚገባ ለማስተዋል እንዲችል ለመርዳት ምሳሌ፣ ማብራሪያ ወይም የተለያዩ ጥያቄዎችን ማዘጋጀት ያስፈልግህ ይሆናል። (ነህ. 8:8) ይሁን እንጂ ከጭብጡ ጋር ብዙም ተዛምዶ የሌለውን ተጨማሪ ሐሳብ ከመጨመር ተቆጠብ። በጥናቱ መጨረሻ ላይ አጭር ክለሳ ማድረግ ተማሪው ዋና ዋና ነጥቦችን ለማስታወስ ይረዳዋል።
5 አዳዲሶች ይሖዋን የሚያስከብር የጽድቅ ፍሬ ሲያፈሩ ስንመለከት በእጅጉ እንደሰታለን! (ፊልጵ. 1:11) ተማሪዎችህ እዚህ ደረጃ ላይ እንዲደርሱ ለመርዳት ምንጊዜም ጥናት ከመምራትህ በፊት በሚገባ ተዘጋጅ።
-