የመጠበቂያ ግንብ የኢንተርኔት ቤተ መጻሕፍት
መጠበቂያ ግንብ
የኢንተርኔት ቤተ መጻሕፍት
አማርኛ
፦
  • ፡
  • መጽሐፍ ቅዱስ
  • የሕትመት ውጤቶች
  • ስብሰባዎች
  • ቤተሰብህ ደስተኛ መሆን የሚችለው እንዴት ነው?
    ከአምላክ የተላከ ምሥራች!
    • ትምህርት 9

      ቤተሰብህ ደስተኛ መሆን የሚችለው እንዴት ነው?

      1. በሕጋዊ መንገድ መጋባት ለቤተሰብ ደስታ ወሳኝ የሆነው ለምንድን ነው?

      አንድ ወንድና አንዲት ሴት ጋብቻቸውን ሕጋዊ ሲያደርጉ

      ምሥራቹ የተላከው ደስተኛ አምላክ ከሆነው ከይሖዋ ሲሆን እሱም ቤተሰቦች ደስተኛ እንዲሆኑ ይፈልጋል። (1 ጢሞቴዎስ 1:11) ጋብቻን ያቋቋመው እሱ ነው። በሕጋዊ መንገድ መጋባት ልጆችን ማሳደግ የሚቻልበት አስተማማኝና ምቹ ሁኔታ ስለሚፈጥር ለቤተሰብ ደስታ ወሳኝ ነው። ክርስቲያኖች ጋብቻን ሕጋዊ ከማድረግ ጋር በተያያዘ በአካባቢያቸው ያለውን ሕግ ሊያከብሩ ይገባል።​—ሉቃስ 2:1, 4, 5ን አንብብ።

      አምላክ ለጋብቻ ምን አመለካከት አለው? ጋብቻ በአንድ ወንድና በአንዲት ሴት መካከል የሚመሠረት ዘላቂ ጥምረት እንዲሆን ይፈልጋል። ይሖዋ፣ ባልና ሚስት አንዳቸው ለሌላው ታማኞች እንዲሆኑ ይፈልጋል። (ዕብራውያን 13:4) ይሖዋ ፍቺን ይጠላል። (ሚልክያስ 2:16) ሆኖም አንደኛው የትዳር ጓደኛ ምንዝር ከፈጸመ ክርስቲያኖች መፋታትና በድጋሚ ማግባት እንደሚችሉ የአምላክ ቃል ይገልጻል።​—ማቴዎስ 19:3-6, 9ን አንብብ።

      2. ባልና ሚስት አንዳቸው ሌላውን እንዴት መያዝ ይኖርባቸዋል?

      ደስተኛ የሆኑ ባልና ሚስት

      ይሖዋ ወንዶችንና ሴቶችን የፈጠረው በጋብቻ ውስጥ አንዳቸው የሌላውን ጉድለት እንዲያሟሉ አድርጎ ነው። (ዘፍጥረት 2:18) አንድ ባል የቤተሰብ ራስ እንደመሆኑ መጠን ለቤተሰቡ የሚያስፈልገውን ቁሳዊ ነገር ለማቅረብም ሆነ እነሱን ስለ አምላክ ለማስተማር ግንባር ቀደም መሆን አለበት። ለሚስቱ ከራስ ወዳድነት ነፃ የሆነ ፍቅር ማሳየት ይኖርበታል። የትዳር ጓደኛሞች እርስ በርስ መዋደድና መከባበር አለባቸው። ሁሉም ባልና ሚስት ፍጽምና ስለሚጎድላቸው ይቅር ባይ መሆናቸው ደስተኛ የቤተሰብ ሕይወት እንዲኖራቸው ከፍተኛ አስተዋጽኦ ያደርጋል።​—ኤፌሶን 4:31, 32ን፤ 5:22-25, 33ን እና 1 ጴጥሮስ 3:7ን አንብብ።

      3. በትዳራችሁ ደስተኛ ካልሆናችሁ መለያየት ይኖርባችኋል?

      በትዳራችሁ ውስጥ ችግሮች ከተፈጠሩ አንዳችሁ ሌላውን በፍቅር ለመያዝ ጥረት አድርጉ። (1 ቆሮንቶስ 13:4, 5) የአምላክ ቃል በትዳር ውስጥ ለሚፈጠሩ ችግሮች መፍትሔው መለያየት እንደሆነ አይናገርም።​—1 ቆሮንቶስ 7:10-13ን አንብብ።

      4. ልጆች፣ አምላክ ምን እንድታገኙ ይፈልጋል?

      ወላጆች በቤት ውስጥ ልጆቻቸውን ሲረዱ

      ይሖዋ ደስተኛ እንድትሆኑ ይፈልጋል። የወጣትነት ዕድሜያችሁን በደስታ ለማሳለፍ እንድትችሉ የሚረዳ ከሁሉ የተሻለ ምክር ይሰጣችኋል። ወላጆቻችሁ ካካበቱት ጥበብና ካሳለፉት የሕይወት ተሞክሮ ጥቅም እንድታገኙ ይፈልጋል። (ቆላስይስ 3:20) ይሖዋ፣ የፈጣሪያችሁንና የልጁን ፈቃድ በማድረግ እንድትደሰቱም ይፈልጋል።​—መክብብ 11:9 እስከ 12:1ን፣ ማቴዎስ 19:13-15ን እና 21:15, 16ን አንብብ።

      5. ወላጆች፣ ልጆቻችሁ ደስተኞች እንዲሆኑ ማድረግ የምትችሉት እንዴት ነው?

      አንድ አባት ከልጁ ጋር ሲነጋገር

      ለልጆቻችሁ ምግብ፣ መጠለያና ልብስ ለማቅረብ በትጋት መሥራት ይኖርባችኋል። (1 ጢሞቴዎስ 5:8) ሆኖም ልጆቻችሁ ደስተኞች እንዲሆኑ አምላክን እንዲወዱና እሱ የሚላቸውን ነገር እንዲሰሙ ማስተማርም ያስፈልጋችኋል። (ኤፌሶን 6:4) ለአምላክ ፍቅር እንዳላችሁ በተግባር የምታሳዩ ከሆነ ይህ ምሳሌነታችሁ የልጆቻችሁን ልብ በጥልቅ ሊነካ ይችላል። በአምላክ ቃል ላይ ተመሥርታችሁ የምትሰጧቸው መመሪያዎች የልጆቻችሁን አስተሳሰብ በጥሩ መንገድ ሊቀርጹት ይችላሉ።​—ዘዳግም 6:4-7ን እና ምሳሌ 22:6ን አንብብ።

      ልጆቻችሁ የእናንተን ምስጋና እና ማበረታቻ ማግኘታቸው ይጠቅማቸዋል። በሌላ በኩል ደግሞ እርማትና ተግሣጽም ያስፈልጋቸዋል። እንዲህ ዓይነቱ ሥልጠና ደስታቸውን እንዲያጡ ከሚያደርግ አካሄድ እንዲርቁ ይረዳቸዋል። (ምሳሌ 22:15) ያም ቢሆን ልጆችን በኃይል ወይም በጭካኔ መቅጣት ተገቢ አይደለም።​—ቆላስይስ 3:21ን አንብብ።

      የይሖዋ ምሥክሮች ወላጆችንም ሆነ ልጆችን ለመርዳት ታስበው የተዘጋጁ በርካታ መጻሕፍት አሳትመዋል። እነዚህ መጻሕፍት በመጽሐፍ ቅዱስ ላይ ተመሥርተው የተዘጋጁ ናቸው።​—መዝሙር 19:7, 11ን አንብብ።

      ተጨማሪ ማብራሪያ ለማግኘት መጽሐፍ ቅዱስ ምን ያስተምረናል? የተባለውን መጽሐፍ ምዕራፍ 14 ተመልከት።

  • የመጽሐፍ ቅዱስ መሠረታዊ ሥርዓቶች የሚጠቅሙን እንዴት ነው?
    ከአምላክ የተላከ ምሥራች!
    • ትምህርት 11

      የመጽሐፍ ቅዱስ መሠረታዊ ሥርዓቶች የሚጠቅሙን እንዴት ነው?

      1. የሰው ልጆች መመሪያ የሚያስፈልገን ለምንድን ነው?

      የመጽሐፍ ቅዱስ መሠረታዊ ሥረዓቶች ተግባራዊ ሲሆኑ፦ እናት ለልጆች የተዘጋጀ የደህንነት ቀበቶ ተጠቅማለች፤ አባት እና ወንድ ልጁ ብስክሌት ሲነዱ የራስ ቁር አድርገዋል፤ ተገቢውን ጥንቃቄ የሚያደርጉ አንዲት እርጉዝ ሴትና ሠራተኛ

      የመጽሐፍ ቅዱስ መሠረታዊ ሥርዓቶች ሕይወትን አደጋ ላይ የሚጥል ነገር ላለማድረግ እንድንጠነቀቅ የሚረዱን እንዴት ነው?—መዝሙር 36:9

      ፈጣሪያችን ከእኛ ይበልጥ ጥበበኛ ነው። አፍቃሪ አባት በመሆኑ ስለ እኛ ያስባል። ከዚህም ሌላ ከእሱ አመራር ውጪ ራሳችንን እንድንመራ አድርጎ አልፈጠረንም። (ኤርምያስ 10:23) በመሆኑም አንድ ትንሽ ልጅ የወላጆቹን መመሪያ ማግኘት እንደሚያስፈልገው ሁሉ የሰው ልጆች በሙሉ ከአምላክ መመሪያ ማግኘት ያስፈልገናል። (ኢሳይያስ 48:17, 18) የመጽሐፍ ቅዱስ መሠረታዊ ሥርዓቶች፣ የሚያስፈልገንን መመሪያ ይሰጡናል፤ በመሆኑም አምላክ ለእኛ እንደላከልን ስጦታ ናቸው።​—2 ጢሞቴዎስ 3:16ን አንብብ።

      የይሖዋ አምላክ ሕግጋትና መሠረታዊ ሥርዓቶች በአሁኑ ጊዜ ከሁሉ የሚሻለው የሕይወት መንገድ የቱ እንደሆነ የሚያስተምሩን ከመሆኑም በላይ ወደፊት ዘላለማዊ በረከቶችን ማጨድ የምንችልበትን መንገድ ያሳዩናል። የፈጠረን አምላክ በመሆኑ ለሚሰጠን መመሪያዎች አመስጋኝ መሆናችንና በእነሱ መመራታችን ተገቢ እንደሆነ ጥያቄ የለውም።​—መዝሙር 19:7, 11ን እና ራእይ 4:11ን አንብብ።

      2. የመጽሐፍ ቅዱስ መሠረታዊ ሥርዓቶች ምንድን ናቸው?

      የመጽሐፍ ቅዱስ መሠረታዊ ሥርዓቶች፣ አጠቃላይ ወይም መሠረታዊ የሆኑ እውነቶች ናቸው። በሌላ በኩል ግን ሕግ ዝርዝር የሆኑ ጉዳዮችን የሚመለከት ነው። (ዘዳግም 22:8) አንድ መሠረታዊ ሥርዓት ከአንድ ሁኔታ ጋር በተያያዘ እንዴት እንደሚሠራ ለመረዳት እንድንችል የመለየት ወይም የማመዛዘን ችሎታችንን መጠቀም ያስፈልገናል። (ምሳሌ 2:10-12) ለምሳሌ፣ ሕይወት ከአምላክ የተገኘ ስጦታ እንደሆነ መጽሐፍ ቅዱስ ያስተምራል። ይህ መሠረታዊ ሥርዓት በሥራ ቦታችን፣ በቤታችንና በጉዞ ላይ በምንሆንበት ጊዜ መመሪያ ሊሆነን ይችላል። የራሳችንንም ሆነ የሌሎችን ሕይወት አደጋ ላይ የሚጥል ነገር ላለማድረግ እንድንጠነቀቅ ይረዳናል።​—የሐዋርያት ሥራ 17:28ን አንብብ።

      3. ዋነኞቹ መሠረታዊ ሥርዓቶች የትኞቹ ናቸው?

      ኢየሱስ ትልቅ ቦታ ስለሚሰጣቸው ሁለት መሠረታዊ ሥርዓቶች ተናግሯል። የመጀመሪያው መሠረታዊ ሥርዓት ሰዎች የተፈጠሩበትን ዓላማ የሚገልጽ ሲሆን ይህም አምላክን ማወቅ፣ መውደድና እሱን በታማኝነት ማገልገል ነው። ማንኛውንም ውሳኔ ስናደርግ የመጀመሪያውን መሠረታዊ ሥርዓት ከግምት ማስገባት ይኖርብናል። (ምሳሌ 3:6) በዚህ መሠረታዊ ሥርዓት የሚመሩ ሰዎች ከአምላክ ጋር ወዳጅነት መመሥረት የሚችሉ ከመሆኑም ሌላ እውነተኛ ደስታና የዘላለም ሕይወት ያገኛሉ።​—ማቴዎስ 22:36-38ን አንብብ።

      ሁለተኛው መሠረታዊ ሥርዓት ደግሞ ከሌሎች ጋር ሰላማዊ ግንኙነት እንዲኖረን ይረዳናል። (1 ቆሮንቶስ 13:4-7) ሰዎችን አምላክ በሚይዝበት መንገድ በመያዝ ሁለተኛውን መሠረታዊ ሥርዓት ተግባራዊ ማድረግ እንችላለን።​—ማቴዎስ 7:12ን እና 22:39, 40ን አንብብ።

      4. የመጽሐፍ ቅዱስ መሠረታዊ ሥርዓቶች የሚጠቅሙን እንዴት ነው?

      ደስተኛ ቤተሰብ

      የመጽሐፍ ቅዱስ መሠረታዊ ሥርዓቶች ቤተሰቦች ፍቅርና አንድነት እንዲኖራቸው ይረዷቸዋል። (ቆላስይስ 3:12-14) የአምላክ ቃል ቤተሰቦች ሊመሩበት የሚገባ ሌላ መሠረታዊ ሥርዓትም ይዟል፤ ጋብቻ ዘላቂ ጥምረት መሆን እንዳለበት የሚያስተምር ሲሆን ይህም የቤተሰቡ ደኅንነት እንዲጠበቅ ያደርጋል።​—ዘፍጥረት 2:24ን አንብብ።

      የመጽሐፍ ቅዱስን ትምህርቶች ተግባራዊ ማድረጋችን በቁሳዊ ነገሮች ረገድ የሚጠቅመን ከመሆኑም ሌላ ውስጣዊ ሰላምና አዎንታዊ አመለካከት እንዲኖረን ይረዳናል። ለምሳሌ ያህል፣ ቀጣሪዎች ብዙውን ጊዜ የሚፈልጉት እንደ ሐቀኝነትና ታታሪነት ባሉት የመጽሐፍ ቅዱስ መሠረታዊ ሥርዓቶች የሚመሩ ሠራተኞችን ነው። (ምሳሌ 10:4, 26፤ ዕብራውያን 13:18) በተጨማሪም የአምላክ ቃል በሚያስፈልጉን ነገሮች ረክተን እንድንኖርና ከቁሳዊ ነገሮች ይልቅ ከአምላክ ጋር ላለን ወዳጅነት ትልቅ ቦታ እንድንሰጥ ያስተምረናል።​—ማቴዎስ 6:24, 25, 33ን እና 1 ጢሞቴዎስ 6:8-10ን አንብብ።

      የመጽሐፍ ቅዱስን መሠረታዊ ሥርዓቶች ተግባራዊ ማድረግ ጤንነታችንን መጠበቅ እንድንችልም ይረዳናል። (ምሳሌ 14:30፤ 22:24, 25) ለምሳሌ፣ ከስካር እንድንርቅ የሚያዝዘውን የአምላክ ሕግ ማክበራችን ከአደጋና ለሞት ከሚዳርጉ በሽታዎች ይጠብቀናል። (ምሳሌ 23:20) ይሖዋ የአልኮል መጠጥ እንድንጠጣ የፈቀደልን ቢሆንም ይህን በልክ እንድናደርግ ይጠብቅብናል። (መዝሙር 104:15፤ 1 ቆሮንቶስ 6:10) አምላክ ያወጣቸው መሠረታዊ ሥርዓቶች ከመጥፎ ድርጊቶች ብቻ ሳይሆን ከመጥፎ ሐሳቦችም እንድንርቅ ስለሚያስተምሩን ጠቃሚ ናቸው። (መዝሙር 119:97-100) ይሁንና እውነተኛ ክርስቲያኖች አምላክ ያወጣቸውን መሥፈርቶች የሚጠብቁት ጥቅም ስለሚያስገኙላቸው ብቻ አይደለም። ይህን የሚያደርጉት ይሖዋን ማክበር ስለሚፈልጉ ነው።​—ማቴዎስ 5:14-16ን አንብብ።

      ተጨማሪ ማብራሪያ ለማግኘት መጽሐፍ ቅዱስ ምን ያስተምረናል? የተባለውን መጽሐፍ ምዕራፍ 12 እና 13 ተመልከት።

አማርኛ ጽሑፎች (1991-2025)
ውጣ
ግባ
  • አማርኛ
  • አጋራ
  • የግል ምርጫዎች
  • Copyright © 2025 Watch Tower Bible and Tract Society of Pennsylvania
  • የአጠቃቀም ውል
  • ሚስጥር የመጠበቅ ፖሊሲ
  • ሚስጥር የመጠበቅ ማስተካከያ
  • JW.ORG
  • ግባ
አጋራ