-
ሳንሄድሪን ፊት ቀረበ፤ ከዚያም ወደ ጲላጦስ ተወሰደኢየሱስ—መንገድ፣ እውነት፣ ሕይወት
-
-
ምዕራፍ 127
ሳንሄድሪን ፊት ቀረበ፤ ከዚያም ወደ ጲላጦስ ተወሰደ
ማቴዎስ 27:1-11 ማርቆስ 15:1 ሉቃስ 22:66–23:3 ዮሐንስ 18:28-35
ማለዳ ላይ የሳንሄድሪን ሸንጎ ያካሄደው ችሎት
የአስቆሮቱ ይሁዳ ራሱን ለመስቀል ሞከረ
ኢየሱስ፣ ጲላጦስ እንዲፈርድበት ወደ እሱ ተላከ
ጴጥሮስ ኢየሱስን ለሦስተኛ ጊዜ የካደው ሌሊቱ ሊነጋ ሲል ነው። የሳንሄድሪን ሸንጎ አባላት፣ ለይምሰል ያካሄዱትን ችሎት አጠናቀው ተበትነዋል። ዓርብ ጎህ ሲቀድ ሸንጎው እንደገና ተሰበሰበ፤ አሁን የተገናኙት ሌሊት ያካሄዱት ሕገ ወጥ ችሎት ሕጋዊ መልክ እንዲኖረው ለማድረግ ይመስላል። በመሆኑም ኢየሱስ ሸንጎው ፊት ቀረበ።
በዚህ ጊዜ የሸንጎው አባላት “አንተ ክርስቶስ ከሆንክ ንገረን” በማለት በድጋሚ ጠየቁት። ኢየሱስ “ብነግራችሁም እንኳ ፈጽሞ አታምኑም። ብጠይቃችሁም አትመልሱም” አለ። ያም ቢሆን ኢየሱስ በዳንኤል 7:13 ላይ ትንቢት የተነገረው ስለ እሱ መሆኑን በድፍረት ገለጸ። “ከአሁን ጀምሮ የሰው ልጅ በኃያሉ አምላክ ቀኝ ይቀመጣል” አላቸው።—ሉቃስ 22:67-69፤ ማቴዎስ 26:63
እነሱም “ስለዚህ የአምላክ ልጅ ነህ ማለት ነው?” በማለት አጥብቀው ጠየቁት። እሱም “የአምላክ ልጅ መሆኔን እናንተው ራሳችሁ እየተናገራችሁ ነው” አላቸው። ይህን በማለቱ ‘አምላክን ተሳድቧል’ በሚል ክስ ሊገደል እንደሚገባ ወሰኑ። “ከዚህ በላይ ምን ማስረጃ ያስፈልገናል?” አሉ። (ሉቃስ 22:70, 71፤ ማርቆስ 14:64) ስለዚህ ኢየሱስን አስረው ወደ ሮማዊው አገረ ገዢ ጳንጥዮስ ጲላጦስ ወሰዱት።
የአስቆሮቱ ይሁዳ፣ ኢየሱስ ወደ ጲላጦስ ሲወሰድ አይቶ ሊሆን ይችላል። ይሁዳ ኢየሱስ እንደተፈረደበት ባወቀ ጊዜ የጸጸትና የተስፋ መቁረጥ ስሜት አደረበት። ይሁንና እውነተኛ ንስሐ ገብቶ አምላክን ይቅርታ ከመጠየቅ ይልቅ 30ዎቹን የብር ሳንቲሞች ለመመለስ ሄደ። ይሁዳ ለካህናት አለቆቹ “ንጹሕ ሰው አሳልፌ በመስጠቴ በድያለሁ” አላቸው። እነሱ ግን በጭካኔ “ታዲያ እኛ ምን አገባን? የራስህ ጉዳይ ነው!” አሉት።—ማቴዎስ 27:4
ይሁዳ 30ዎቹን የብር ሳንቲሞች ቤተ መቅደሱ ውስጥ በትኖ ወጣ፤ ከዚያም ራሱን ለመግደል በመሞከር ሌላ ኃጢአት ፈጸመ። ይሁዳ ታንቆ ለመሞት ቢሞክርም ገመዱን ያሰረበት ቅርንጫፍ የተሰበረ ይመስላል። በመሆኑም ከታች ያለው ዓለት ላይ ሲወድቅ ሰውነቱ ፈነዳ።—የሐዋርያት ሥራ 1:17, 18
ኢየሱስ ወደ ጳንጥዮስ ጲላጦስ ቤተ መንግሥት የተወሰደው ገና በማለዳ ነው። ሆኖም ኢየሱስን ወደዚያ የወሰዱት አይሁዶች ወደ ቤተ መንግሥቱ ለመግባት ፈቃደኞች አልሆኑም። አይሁዶች ከአሕዛብ ጋር እንዲህ ያለ ግንኙነት ማድረግ እንደሚያረክሳቸው ያምናሉ። በዚህ መንገድ ከረከሱ ደግሞ ኒሳን 15 ላይ ከሚቀርበው ማዕድ መብላት አይችሉም፤ ይህ ዕለት የቂጣ በዓል የመጀመሪያ ቀን ሲሆን ከፋሲካ ጋር የተያያዘ በዓል እንደሆነ ይቆጠራል።
ጲላጦስ ወደ ውጭ ወጣና “በዚህ ሰው ላይ የምታቀርቡት ክስ ምንድን ነው?” አላቸው። እነሱም መልሰው “ይህ ሰው ጥፋተኛ ባይሆን ኖሮ ለአንተ አሳልፈን አንሰጠውም ነበር” አሉት። ጲላጦስ ጫና ሊያሳድሩበት እየሞከሩ እንደሆነ ስለተሰማው ሳይሆን አይቀርም “እናንተ ራሳችሁ ወስዳችሁ በሕጋችሁ መሠረት ፍረዱበት” አላቸው። አይሁዳውያኑም “እኛ ማንንም ሰው ለመግደል ሕግ አይፈቅድልንም” በማለት ዓላማቸው ኢየሱስን መግደል እንደሆነ ጠቆሙ።—ዮሐንስ 18:29-31
ኢየሱስን በፋሲካ በዓል ላይ ከገደሉት ሕዝባዊ ዓመፅ ሊቀሰቀስ ይችላል። ሆኖም ከሳሾቹ፣ በፖለቲካዊ ክስ ተጠቅመው ሮማውያን ኢየሱስን እንዲገድሉት ማድረግ ከቻሉ በሕዝቡ ዘንድ ከተጠያቂነት ነፃ ይሆናሉ፤ ምክንያቱም ሮማውያን እንዲህ ዓይነት ክስ የቀረበባቸውን ሰዎች የመግደል ሥልጣን አላቸው።
የሃይማኖት መሪዎቹ፣ ኢየሱስ ላይ የፈረዱበት ‘አምላክን ሰድቦአል’ በሚል ክስ እንደሆነ ለጲላጦስ አልነገሩትም። አሁን የሚከተሉትን የሐሰት ክሶች አቀረቡ፦ “ይህ ሰው [1] ሕዝባችንን ሲያሳምፅ፣ [2] ለቄሳር ግብር እንዳይከፈል ሲከለክልና [3] ‘እኔ ክርስቶስ ንጉሥ ነኝ’ ሲል አግኝተነዋል።”—ሉቃስ 23:2
ጲላጦስ የሮም ተወካይ እንደመሆኑ መጠን ‘ኢየሱስ ንጉሥ እንደሆነ ተናግሯል’ በሚል የተመሠረተው ክስ ቢያሳስበው የሚያስገርም አይደለም። ስለዚህ ጲላጦስ እንደገና ወደ ቤተ መንግሥቱ ገብቶ ኢየሱስን አስጠራውና “አንተ የአይሁዳውያን ንጉሥ ነህ?” ብሎ ጠየቀው። በሌላ አነጋገር፣ ‘ቄሳርን ተቃውመህ ንጉሥ እንደሆንክ በመግለጽ የሮምን ሕግ ተላልፈሃል?’ ማለቱ ነው። ኢየሱስም “ይህ የራስህ ጥያቄ ነው ወይስ ሌሎች ስለ እኔ ነግረውህ ነው?” አለው፤ ምናልባትም ይህን ያለው ጲላጦስ ስለ እሱ ምን ያህል እንደሰማ ማወቅ ፈልጎ ሊሆን ይችላል።—ዮሐንስ 18:33, 34
ጲላጦስ ስለ ኢየሱስ የሚያውቀው ነገር እንደሌለና እውነታውን ማወቅ እንደሚፈልግ ሲገልጽ “እኔ አይሁዳዊ ነኝ እንዴ?” አለ። አክሎም “ለእኔ አሳልፈው የሰጡህ የራስህ ሕዝብና የካህናት አለቆች ናቸው። ያደረግከው ምንድን ነው?” ሲል ጠየቀው።—ዮሐንስ 18:35
ኢየሱስ ንግሥናን በተመለከተ የተነሳውን ጉዳይ እንዲሁ አድበስብሶ ለማለፍ አልሞከረም። ኢየሱስ የሰጠው መልስ አገረ ገዢውን ጲላጦስን በጣም ሳያስገርመው አልቀረም።
-
-
ጲላጦስም ሆነ ሄሮድስ ምንም ጥፋት አላገኙበትምኢየሱስ—መንገድ፣ እውነት፣ ሕይወት
-
-
ምዕራፍ 128
ጲላጦስም ሆነ ሄሮድስ ምንም ጥፋት አላገኙበትም
ማቴዎስ 27:12-14, 18, 19 ማርቆስ 15:2-5 ሉቃስ 23:4-16 ዮሐንስ 18:36-38
ጲላጦስና ሄሮድስ ኢየሱስን መረመሩት
ኢየሱስ፣ ንጉሥ መሆኑን ከጲላጦስ ለመደበቅ አልሞከረም። ያም ቢሆን መንግሥቱ በሮም መንግሥት ላይ የሚፈጥረው ስጋት የለም። እንዲህ አለ፦ “መንግሥቴ የዚህ ዓለም ክፍል አይደለም። መንግሥቴ የዚህ ዓለም ክፍል ቢሆን ኖሮ በአይሁዳውያን እጅ እንዳልወድቅ አገልጋዮቼ ይዋጉልኝ ነበር። አሁን ግን መንግሥቴ ከዚህ አይደለም።” (ዮሐንስ 18:36) አዎን፣ ኢየሱስ መንግሥት አለው፤ ይሁንና መንግሥቱ ከዚህ ዓለም አይደለም።
ሆኖም ጲላጦስ ጉዳዩን በዚህ አልተወውም። “እንግዲያው አንተ ንጉሥ ነህ?” ብሎ ጠየቀው። ኢየሱስም እንደሚከተለው ብሎ በመመለስ ጲላጦስ ትክክለኛው መደምደሚያ ላይ እንደደረሰ ገለጸ፦ “እኔ ንጉሥ እንደሆንኩ አንተ ራስህ እየተናገርክ ነው። እኔ የተወለድኩትና ወደ ዓለም የመጣሁት ስለ እውነት ለመመሥከር ነው። ከእውነት ጎን የቆመ ሁሉ ቃሌን ይሰማል።”—ዮሐንስ 18:37
ኢየሱስ ከዚህ ቀደም ለቶማስ “እኔ መንገድ፣ እውነትና ሕይወት ነኝ” ብሎታል። አሁን ደግሞ፣ ወደ ምድር የመጣው “ስለ እውነት” በተለይም ስለ መንግሥቱ የሚገልጸውን እውነት ለመመሥከር መሆኑን ለጲላጦስ እንኳ ነገረው። ኢየሱስ፣ ሕይወቱን የሚያሳጣው ቢሆንም ለዚህ እውነት ታማኝ ለመሆን ዝግጁ ነው። ጲላጦስ “እውነት ምንድን ነው?” ብሎ ጠየቀው፤ ሆኖም መልስ እንዲሰጠው አልጠበቀም። በዚህ ሰው ላይ ለመፍረድ የሚያስችል በቂ መረጃ እንዳገኘ ተሰምቶታል።—ዮሐንስ 14:6፤ 18:38
ጲላጦስ ከቤተ መንግሥቱ ውጭ ሆኖ ወደሚጠባበቀው ሕዝብ ተመለሰ። የካህናት አለቆቹንና አብረዋቸው ያሉትን ሰዎች “በዚህ ሰው ላይ ምንም ወንጀል አላገኘሁበትም” አላቸው፤ ይህን ያለው ኢየሱስን ከጎኑ አቁሞ ሳይሆን አይቀርም። የተሰበሰቡት ሰዎች በዚህ ውሳኔ ተበሳጭተው “በመላው ይሁዳ፣ ከገሊላ አንስቶ እስከዚህ ድረስ እያስተማረ ሕዝቡን ይቀሰቅሳል” በማለት አጥብቀው ተናገሩ።—ሉቃስ 23:4, 5
የአይሁዳውያኑ ጭፍንና ግትር የሆነ አቋም ጲላጦስን ሳያስገርመው አይቀርም። የካህናት አለቆቹና የሕዝቡ ሽማግሌዎች መጮኻቸውን ሲቀጥሉ ጲላጦስ ወደ ኢየሱስ ዞር አለና “በስንት ነገር እየመሠከሩብህ እንዳሉ አትሰማም?” ሲል ጠየቀው። (ማቴዎስ 27:13) ኢየሱስ ምንም መልስ አልሰጠም። ኢየሱስ፣ ቁጣ የተሞላበት ይህ ሁሉ ክስ እየተሰነዘረበት መረጋጋቱ ጲላጦስን አስደነቀው።
አይሁዳውያን ኢየሱስ ‘ከገሊላ እንደተነሳ’ ገልጸዋል። ጲላጦስ ስለዚህ ጉዳይ ሲያጣራ ኢየሱስ በእርግጥም የገሊላ ሰው መሆኑን ተረዳ። ይህን ሲያውቅ በኢየሱስ ላይ ከመፍረድ ራሱን ነፃ ማውጣት የሚችልበት መንገድ እንዳለ ተሰማው። የገሊላ ገዢ ሄሮድስ አንቲጳስ (የታላቁ ሄሮድስ ልጅ) ሲሆን እሱ ደግሞ በፋሲካ በዓል ወቅት ኢየሩሳሌም መጥቷል። በመሆኑም ጲላጦስ ኢየሱስን ወደ ሄሮድስ ላከው። የመጥምቁ ዮሐንስን ራስ ያስቆረጠው ሄሮድስ አንቲጳስ ነው። ከጊዜ በኋላ ሄሮድስ፣ ኢየሱስ ተአምራት እየፈጸመ እንዳለ ሲሰማ ዮሐንስ ከሞት እንደተነሳና ኢየሱስ የተባለው እሱ እንደሆነ ስለተሰማው ጉዳዩ አሳስቦት ነበር።—ሉቃስ 9:7-9
አሁን ሄሮድስ ኢየሱስን የሚያይበት አጋጣሚ በማግኘቱ ተደሰተ። ሄሮድስ የተደሰተው ኢየሱስን ሊረዳው አስቦ አሊያም ደግሞ በእሱ ላይ የተሰነዘሩት ክሶች እውነተኛ መሆናቸውን በሚገባ ለማጣራት ፈልጎ አይደለም። ከዚህ ይልቅ የማወቅ ፍላጎት ስላደረበትና ኢየሱስ “አንዳንድ ተአምራት ሲፈጽም ለማየት” ተስፋ ስላደረገ ነው። (ሉቃስ 23:8) ይሁን እንጂ ኢየሱስ፣ ሄሮድስ የጓጓለትን ነገር ለመፈጸም ፈቃደኛ አልሆነም። እንዲያውም ሄሮድስ ሲጠይቀው ኢየሱስ አንድም ቃል አልተነፈሰም። ሄሮድስ፣ የጠበቀውን ነገር ኢየሱስ ስላላደረገ በመበሳጨቱ ከወታደሮቹ ጋር ሆኖ “አቃለለው።” (ሉቃስ 23:11) ያማረ ልብስ አልብሰው አፌዙበት። ከዚያም ሄሮድስ፣ ኢየሱስን መልሶ ወደ ጲላጦስ ላከው። ቀደም ሲል ጠላቶች የነበሩት ሄሮድስና ጲላጦስ አሁን ጥሩ ወዳጆች ሆኑ።
ኢየሱስ ተመልሶ ሲመጣ ጲላጦስ የካህናት አለቆችን፣ የአይሁድ መሪዎችንና ሕዝቡን አንድ ላይ ጠርቶ እንዲህ አላቸው፦ “ይህን ሰው . . . በፊታችሁ መረመርኩት፤ ሆኖም በእሱ ላይ ያቀረባችሁትን ክስ የሚደግፍ ምንም ነገር አላገኘሁም። ሄሮድስም ቢሆን ምንም ጥፋት ስላላገኘበት ወደ እኛ መልሶ ልኮታል፤ በመሆኑም ለሞት የሚያበቃ ምንም ነገር አልፈጸመም። ስለዚህ ቀጥቼ እፈታዋለሁ።”—ሉቃስ 23:14-16
ካህናቱ ኢየሱስን አሳልፈው የሰጡት በቅናት ተነሳስተው እንደሆነ ጲላጦስ ስለተገነዘበ ኢየሱስን ሊፈታው ፈልጓል። ጲላጦስ ኢየሱስን ለመፍታት እየሞከረ እያለ ይህንን ጥረቱን ይበልጥ እንዲገፋበት የሚያነሳሳ ሌላ ነገር አጋጠመው። ፍርድ ወንበር ላይ ተቀምጦ ሳለ ሚስቱ “በእሱ ምክንያት ዛሬ በሕልም [ምንጩ መለኮታዊ ሳይሆን አይቀርም] ብዙ ስለተሠቃየሁ በዚያ ጻድቅ ሰው ላይ ምንም ነገር እንዳታደርግ” የሚል መልእክት ላከችበት።—ማቴዎስ 27:19
ጲላጦስ ይህን ንጹሕ ሰው መፍታት እንዳለበት ግልጽ ነው፤ ታዲያ እንዴት ሊፈታው ይችላል?
-
-
ጲላጦስ “እነሆ፣ ሰውየው!” አለኢየሱስ—መንገድ፣ እውነት፣ ሕይወት
-
-
ምዕራፍ 129
ጲላጦስ “እነሆ፣ ሰውየው!” አለ
ማቴዎስ 27:15-17, 20-30 ማርቆስ 15:6-19 ሉቃስ 23:18-25 ዮሐንስ 18:39–19:5
ጲላጦስ ኢየሱስን ለመፍታት ሞከረ
አይሁዳውያን በርባን እንዲፈታላቸው ጠየቁ
ኢየሱስን አሾፉበት እንዲሁም አንገላቱት
ጲላጦስ፣ ኢየሱስ እንዲገደል ለሚፈልገው ሕዝብ “በእሱ ላይ ያቀረባችሁትን ክስ የሚደግፍ ምንም ነገር አላገኘሁም” አላቸው። አክሎም ‘ሄሮድስም ቢሆን ምንም ጥፋት አላገኘበትም’ አለ። (ሉቃስ 23:14, 15) ከዚያም ጲላጦስ ኢየሱስን ለማዳን ሌላ ዘዴ ለመጠቀም ሞከረ፤ ሕዝቡን እንዲህ አላቸው፦ “በልማዳችሁ መሠረት በፋሲካ አንድ ሰው ለእናንተ መፍታቴ አይቀርም። ስለዚህ የአይሁዳውያንን ንጉሥ እንድፈታላችሁ ትፈልጋላችሁ?”—ዮሐንስ 18:39
ጲላጦስ በዝርፊያ፣ ዓመፅ በማነሳሳትና በነፍስ ግድያ የሚታወቅ በርባን የተባለ እስረኛ እንዳለ ያውቃል። ስለዚህ ጲላጦስ “ማንን እንድፈታላችሁ ትፈልጋላችሁ? በርባንን ወይስ ክርስቶስ የሚባለውን ኢየሱስን?” ሲል ጠየቃቸው። ሕዝቡም የካህናት አለቆች ስላግባቧቸው ኢየሱስ ሳይሆን በርባን እንዲፈታ ጠየቁ። ጲላጦስም “ከሁለቱ ማንን እንድፈታላችሁ ትፈልጋላችሁ?” በማለት በድጋሚ ጠየቀ። ሕዝቡ “በርባንን” ብለው ጮኹ!—ማቴዎስ 27:17, 21
ጉዳዩ ያስጨነቀው ጲላጦስ “እንግዲያው ክርስቶስ የሚባለውን ኢየሱስን ምን ባደርገው ይሻላል?” አላቸው። ሕዝቡም “ይሰቀል!” ብለው ጮኹ። (ማቴዎስ 27:22) ንጹሕ ሰው እንዲሞት እየጠየቁ መሆናቸው በጣም ያሳፍራል። ጲላጦስ “ለምን? ይህ ሰው ምን ያጠፋው ነገር አለ? ለሞት የሚያበቃ ምንም ነገር አላገኘሁበትም፤ ስለዚህ ቀጥቼ እፈታዋለሁ” አላቸው።—ሉቃስ 23:22
ጲላጦስ በተደጋጋሚ ሙከራ ቢያደርግም ክፉኛ የተቆጣው ሕዝብ “ይሰቀል!” እያለ በአንድነት መጮኹን ቀጠለ። (ማቴዎስ 27:23) የሃይማኖት መሪዎቹ የተሰበሰቡትን ሰዎች በማነሳሳት ስሜታዊ እንዲሆኑ ስላደረጓቸው ደም ለማፍሰስ ቆርጠዋል! ማስገደል የፈለጉት ደግሞ አንድን ወንጀለኛ ወይም ነፍሰ ገዳይ አይደለም። ከአምስት ቀናት በፊት እንደ ንጉሥ ሆኖ ወደ ኢየሩሳሌም ሲገባ ጥሩ አቀባበል የተደረገለትን ንጹሕ ሰው ነው። የኢየሱስ ደቀ መዛሙርት በቦታው ተገኝተው ከሆነ ማንነታቸው እንዳይታወቅ ድምፃቸውን አጥፍተዋል።
ጲላጦስ ሕዝቡን ለማግባባት ያደረገው ጥረት እንዳልተሳካ ተገነዘበ። ሁከት እየተነሳ መሆኑን ስላስተዋለ ውኃ አምጥቶ በሕዝቡ ፊት እጁን ታጠበ። ከዚያም “ከዚህ ሰው ደም ንጹሕ ነኝ። ከዚህ በኋላ ተጠያቂ የምትሆኑት እናንተ ናችሁ” አላቸው። ሕዝቡ ይህን ሲሰሙ እንኳ አመለካከታቸውን አልቀየሩም። እንዲያውም “ደሙ በእኛና በልጆቻችን ላይ ይሁን” አሉ።—ማቴዎስ 27:24, 25
አገረ ገዢው ትክክል እንደሆነ የሚያውቀውን ነገር ከማድረግ ይልቅ የሕዝቡን ፍላጎት ማሟላትን መረጠ። በመሆኑም ጲላጦስ በርባንን በመፍታት እንደ ፍላጎታቸው አደረገላቸው። ኢየሱስንም ልብሱን አስወልቆ አስገረፈው።
ኢየሱስ በጣም በሚያሠቃይ ሁኔታ ከተገረፈ በኋላ ወታደሮቹ ወደ አገረ ገዢው ቤተ መንግሥት ወሰዱት። በዚያም የሠራዊቱ አባላት ሁሉ ተሰብስበው ይበልጥ አዋረዱት። የእሾህ አክሊል ጎንጉነው በራሱ ላይ ደፉበት። በተጨማሪም ወታደሮቹ በቀኝ እጁ የመቃ ዘንግ አስያዙት፤ እንዲሁም ነገሥታት የሚለብሱት ዓይነት ቀይ መጎናጸፊያ አለበሱት። ከዚያም “የአይሁዳውያን ንጉሥ ሆይ፣ ሰላም ለአንተ ይሁን!” እያሉ አሾፉበት። (ማቴዎስ 27:28, 29) ይባስ ብለውም ምራቃቸውን ተፉበት፤ በጥፊም መቱት። እንዲሁም ጠንካራውን መቃ ከእጁ ወስደው ጭንቅላቱን ይመቱት ጀመር፤ እሱን ለማዋረድ ብለው ራሱ ላይ በደፉት “አክሊል” ላይ ያሉት ሹል እሾኾች በዚህ ጊዜ ጭንቅላቱ ላይ ይበልጥ ተሰኩ።
ኢየሱስ፣ ይህን ሁሉ ቁም ስቅል ክብሩን ጠብቆ መቋቋሙና ጥንካሬው ጲላጦስን በጣም ስላስደነቀው ራሱን ከኃላፊነት ነፃ ለማውጣት ሌላ ሙከራ አደረገ። ሕዝቡን “ምንም ጥፋት እንዳላገኘሁበት ታውቁ ዘንድ እነሆ ወደ ውጭ አወጣላችኋለሁ” አላቸው። ጲላጦስ፣ ሕዝቡ የኢየሱስ ሰውነት በልዞና ደም በደም ሆኖ መመልከታቸው ልባቸውን እንደሚያራራው አስቦ ይሆን? ኢየሱስ ጨካኝ በሆነው ሕዝብ ፊት ቆሞ እያለ ጲላጦስ “እነሆ፣ ሰውየው!” አላቸው።—ዮሐንስ 19:4, 5
ኢየሱስ የተደበደበና የቆሳሰለ ቢሆንም የመንፈስ ጥንካሬና መረጋጋት ይነበብበታል። ጲላጦስም እንኳ ይህን እንዳስተዋለ አክብሮትና ሐዘን ከተቀላቀለበት ንግግሩ መረዳት ይቻላል።
-
-
ኢየሱስ አልፎ ተሰጠ፤ ከዚያም ሊገደል ተወሰደኢየሱስ—መንገድ፣ እውነት፣ ሕይወት
-
-
ምዕራፍ 130
ኢየሱስ አልፎ ተሰጠ፤ ከዚያም ሊገደል ተወሰደ
ማቴዎስ 27:31, 32 ማርቆስ 15:20, 21 ሉቃስ 23:24-31 ዮሐንስ 19:6-17
ጲላጦስ ኢየሱስን ሊፈታው ሞከረ
ኢየሱስ ተፈረደበት፤ ወደሚገደልበት ቦታም ተወሰደ
ኢየሱስ ጭካኔ በተሞላበት ሁኔታ የተንገላታና የተዘበተበት ቢሆንም ጲላጦስ እሱን ለመልቀቅ ያደረገው ሙከራ የካህናት አለቆቹና ተባባሪዎቻቸው እንዲራሩለት አላደረጋቸውም። ኢየሱስን ከመግደል ምንም ነገር እንዳያግዳቸው ቆርጠዋል። “ይሰቀል! ይሰቀል!” እያሉ መጮኻቸውን ቀጠሉ። ጲላጦስም “እኔ ምንም ጥፋት ስላላገኘሁበት ራሳችሁ ወስዳችሁ ግደሉት” አላቸው።—ዮሐንስ 19:6
አይሁዳውያን ኢየሱስ ላይ ያቀረቡት ፖለቲካዊ ክስ ለሞት የሚያበቃ እንደሆነ ጲላጦስን ማሳመን አልቻሉም፤ ይሁንና ከሃይማኖት ጋር የተያያዘ ክስ ቢያቀርቡስ? ኢየሱስ በሳንሄድሪን ሸንጎ ፊት ቀርቦ በነበረበት ጊዜ የሰነዘሩትን ‘አምላክን ተሳድቧል’ የሚል ክስ እንደገና አነሱ። አይሁዳውያኑ “እኛ ሕግ አለን፤ ይህ ሰው ደግሞ ራሱን የአምላክ ልጅ ስላደረገ በሕጉ መሠረት መሞት አለበት” አሉ። (ዮሐንስ 19:7) ይህ ለጲላጦስ አዲስ ክስ ነው።
ጲላጦስ ወደ ቤተ መንግሥቱ ተመለሰ፤ ከዚያም የደረሰበትን ከባድ ሥቃይ በጽናት የተቋቋመውንና ሚስቱ በሕልሟ ያየችውን ኢየሱስን መፍታት የሚችልበትን መንገድ መፈለግ ጀመረ። (ማቴዎስ 27:19) አይሁዳውያን፣ እስረኛው “የአምላክ ልጅ” እንደሆነ መናገሩን አስመልክቶ የሰነዘሩት አዲስ ክስስ? ጲላጦስ፣ ኢየሱስ የገሊላ ሰው መሆኑን ያውቃል። (ሉቃስ 23:5-7) ይሁንና “ለመሆኑ ከየት ነው የመጣኸው?” ብሎ ጠየቀው። (ዮሐንስ 19:9) ጲላጦስ፣ ኢየሱስ ከዚያ በፊት በሕይወት ይኖር እንደነበረና ምናልባትም ከአማልክት ዘንድ የመጣ እንደሆነ አስቦ ይሆን?
ኢየሱስ ንጉሥ እንደሆነ፣ ሆኖም መንግሥቱ ከዚህ ዓለም እንዳልሆነ በቀጥታ ለጲላጦስ ነግሮታል። ኢየሱስ ተጨማሪ ማብራሪያ መስጠት አስፈላጊ እንዳልሆነ ስለተሰማው ለጲላጦስ ጥያቄ መልስ አልሰጠም። ኢየሱስ ጸጥ ሲለው ጲላጦስ ክብሩ እንደተነካ ስለተሰማው ድንገት ግንፍል ብሎ “መልስ አትሰጠኝም? ልፈታህም ሆነ ልገድልህ ሥልጣን እንዳለኝ አታውቅም?” አለው።—ዮሐንስ 19:10
ኢየሱስም እንዲህ ሲል መለሰ፦ “ከላይ ባይሰጥህ ኖሮ በእኔ ላይ ምንም ሥልጣን አይኖርህም ነበር። ለአንተ አሳልፎ የሰጠኝ ሰው የባሰ ኃጢአት ያለበት ለዚህ ነው።” (ዮሐንስ 19:11) ኢየሱስ ይህን ያለው አንድ ሰው በአእምሮው ይዞ ላይሆን ይችላል። ከዚህ ይልቅ ቀያፋና ግብረ አበሮቹ እንዲሁም የአስቆሮቱ ይሁዳ ከጲላጦስ የበለጠ ተጠያቂነት እንዳለባቸው መግለጹ ነው።
ጲላጦስ በኢየሱስ ንግግርም ሆነ ምግባር ከመደነቁም በላይ ከአማልክት ዘንድ የመጣ ሊሆን እንደሚችል በማሰብ ይበልጥ ስለፈራ እሱን ለመፍታት በድጋሚ ጥረት አደረገ። ይሁንና አይሁዳውያን ጲላጦስን ሊያስፈራው የሚችል ሌላ ነጥብ አነሱ። “ይህን ሰው ከፈታኸው አንተ የቄሳር ወዳጅ አይደለህም። ራሱን ንጉሥ የሚያደርግ ሰው ሁሉ የቄሳር ተቃዋሚ ነው” ሲሉ አስፈራሩት።—ዮሐንስ 19:12
አገረ ገዢው ኢየሱስን ዳግመኛ ወደ ውጭ በማውጣት በፍርድ ወንበር ላይ ተቀምጦ ሕዝቡን “እነሆ፣ ንጉሣችሁ!” አላቸው። አይሁዳውያኑ ግን ሐሳባቸውን አልቀየሩም። “አስወግደው! አስወግደው! ስቀለው!” እያሉ ጮኹ። ጲላጦስም “ንጉሣችሁን ልግደለው?” ሲል ጠየቃቸው። አይሁዳውያን የሮማውያን አገዛዝ ያስመረራቸው ቢሆንም የካህናት አለቆቹ አፍ አውጥተው “ከቄሳር በቀር ሌላ ንጉሥ የለንም” ሲሉ መለሱ።—ዮሐንስ 19:14, 15
ጲላጦስ፣ የአይሁዳውያኑን ውትወታ ላለመቀበል ድፍረት ስላጣ በመጨረሻ ለጥያቄያቸው ተንበረከከ፤ በመሆኑም ኢየሱስን እንዲገድሉት አሳልፎ ሰጣቸው። ወታደሮቹ ቀዩን ልብስ ገፈው የራሱን መደረቢያዎች አለበሱት። ኢየሱስን ሲወስዱት የራሱን የመከራ እንጨት እንዲሸከም አደረጉት።
አሁን ዓርብ፣ ኒሳን 14 እኩለ ቀን እየተቃረበ ነው። ኢየሱስ ከሐሙስ ማለዳ ጀምሮ አልተኛም፤ በዚያ ላይ ደግሞ መከራና ሥቃይ ሲፈራረቅበት ቆይቷል። ስለዚህ እንጨቱን ተሸክሞ ሲሄድ ኃይሉ ተሟጠጠ። በመሆኑም ወታደሮቹ፣ አፍሪካ ውስጥ ከምትገኘው ከቀሬና የመጣውን ስምዖን የተባለ መንገደኛ እንጨቱን ተሸክሞ ኢየሱስ ወደሚገደልበት ቦታ እንዲወስድ አስገደዱት። ብዙ ሕዝብ እየተከተለው ነው፤ ከእነሱ መካከል አንዳንዶቹ በሐዘን ደረታቸውን እየደቁ ያለቅሳሉ።
ኢየሱስ የሚያለቅሱትን ሴቶች እንዲህ አላቸው፦ “እናንተ የኢየሩሳሌም ልጆች፣ ለእኔ አታልቅሱ። ይልቁንስ ለራሳችሁና ለልጆቻችሁ አልቅሱ፤ ሰዎች ‘መሃን የሆኑ ሴቶች፣ ያልወለዱ ማህፀኖችና ያላጠቡ ጡቶች ደስተኞች ናቸው!’ የሚሉበት ቀን ይመጣልና። በዚያን ጊዜ ተራሮችን ‘በላያችን ውደቁ!’ ኮረብቶችንም ‘ሸሽጉን!’ ይላሉ። ዛፉ እርጥብ ሆኖ ሳለ እንዲህ ካደረጉ በደረቀ ጊዜማ ምን ይከሰት ይሆን?”—ሉቃስ 23:28-31
ኢየሱስ እየተናገረ ያለው ስለ አይሁድ ብሔር ነው። ብሔሩ፣ እየደረቀ ቢሆንም ትንሽ እርጥበት እንደቀረው ዛፍ ነው፤ ምክንያቱም ኢየሱስና በእሱ የሚያምኑ አንዳንድ አይሁዳውያን አሉ። አምላክ እነዚህን ሰዎች ከብሔሩ እንዲወጡ ሲያደርጋቸው ግን የሚቀረው ልክ እንደደረቀ ዛፍ በመንፈሳዊ ሁኔታ የሞተ ብሔር ነው። የሮም ሠራዊት የአምላክ ፍርድ አስፈጻሚ ሆኖ የአይሁድን ሕዝብ በሚያጠፋበት ጊዜ ታላቅ ለቅሶ ይሆናል!
-
-
ምንም ጥፋት የሌለበት ንጉሥ በእንጨት ላይ ተሰቀለኢየሱስ—መንገድ፣ እውነት፣ ሕይወት
-
-
ምዕራፍ 131
ምንም ጥፋት የሌለበት ንጉሥ በእንጨት ላይ ተሰቀለ
ማቴዎስ 27:33-44 ማርቆስ 15:22-32 ሉቃስ 23:32-43 ዮሐንስ 19:17-24
ኢየሱስ በመከራ እንጨት ላይ ተቸነከረ
ከራሱ በላይ በተሰቀለው ምልክት የተነሳ አፌዙበት
ኢየሱስ ገነት በምትሆነው ምድር ላይ የመኖር ተስፋ ሰጠ
ኢየሱስ ከከተማዋ ብዙም ወደማይርቅ ቦታ ተወሰደ፤ በዚያም እሱና ሁለት ዘራፊዎች ይሰቀላሉ። ጎልጎታ የሚባለው ይህ ስፍራ የራስ ቅል ቦታ የሚል ትርጉም አለው፤ ቦታው ‘ከሩቅ ይታያል።’—ማርቆስ 15:40
ሞት የተፈረደባቸው ሦስቱ ሰዎች ልብሳቸውን እንዲያወልቁ ተደረገ። ከዚያም ከርቤና ሐሞት የተቀላቀለበት የወይን ጠጅ ሰጧቸው። መጠጡን ያዘጋጁት የኢየሩሳሌም ሴቶች ሳይሆኑ አይቀሩም፤ ሮማውያንም ሞት የተፈረደባቸው ሰዎች ሥቃዩ እንዳይሰማቸው የሚያደርገው ይህ መጠጥ እንዳይሰጣቸው አይከለክሉም። ኢየሱስ ግን ከቀመሰው በኋላ ሊጠጣው ፈቃደኛ አልሆነም። ለምን? በዚህ ታላቅ የፈተና ወቅት አእምሮው እንዲደነዝዝ አልፈለገም፤ ንቁ ሆኖ እስከ ሞት ድረስ ታማኝነቱን ለመጠበቅ ቆርጧል።
ኢየሱስ እጆቹን ዘርግቶ በእንጨቱ ላይ ተጋደመ። (ማርቆስ 15:25) ከዚያም ወታደሮቹ በእጆቹና በእግሮቹ ላይ ምስማር ቸነከሩ፤ ምስማሮቹ ሥጋውንና ጅማቶቹን በስተው ሲገቡ ከፍተኛ ሥቃይ ያስከትላሉ። እንጨቱ ቀጥ ብሎ እንዲቆም ሲደረግ ደግሞ የሰውነቱ ክብደት ምስማሮቹ በገቡባቸው ቦታዎች ላይ ስለሚያርፍ ሥቃዩ በጣም ይበረታል። ያም ቢሆን ኢየሱስ ወታደሮቹን አልተቆጣቸውም። ከዚህ ይልቅ “አባት ሆይ፣ የሚያደርጉትን ስለማያውቁ ይቅር በላቸው” ሲል ጸለየ።—ሉቃስ 23:34
ሮማውያን ሞት የተፈረደበት ወንጀለኛ የሠራውን ጥፋት የሚገልጽ ምልክት የማንጠልጠል ልማድ አላቸው። ጲላጦስ “የአይሁዳውያን ንጉሥ፣ የናዝሬቱ ኢየሱስ” የሚል ጽሑፍ በመከራው እንጨት ላይ አንጠለጠለ። ምልክቱ የተጻፈው በዕብራይስጥ፣ በላቲንና በግሪክኛ በመሆኑ አብዛኛው ሰው ሊያነበው ይችላል። ጲላጦስ ይህን ማድረጉ ኢየሱስን ላስገደሉት አይሁዳውያን ያለውን ንቀት ያሳያል። በዚህ የተበሳጩት የካህናት አለቆች ጲላጦስን “እሱ ‘የአይሁዳውያን ንጉሥ ነኝ’ እንዳለ ጻፍ እንጂ ‘የአይሁዳውያን ንጉሥ’ ብለህ አትጻፍ” በማለት ተቃውሟቸውን ገለጹ። ጲላጦስ ግን በድጋሚ የእነሱ መሣሪያ መሆን ስላልፈለገ “እንግዲህ የጻፍኩትን ጽፌአለሁ” ሲል መለሰ።—ዮሐንስ 19:19-22
በንዴት የበገኑት ካህናት፣ ቀደም ሲል በሳንሄድሪን ሸንጎ ፊት ያቀረቡትን የሐሰት ክስ እንደገና አነሱ። በመሆኑም በዚያ የሚያልፉ ሰዎች ራሳቸውን እየነቀነቁ “ቤተ መቅደሱን አፍርሼ በሦስት ቀን እሠራዋለሁ ባይ! እስቲ ከተሰቀልክበት እንጨት ላይ ወርደህ ራስህን አድን” እያሉ ማፌዛቸውና መሳደባቸው የሚያስገርም አይደለም። በተመሳሳይም የካህናት አለቆችና ጸሐፍት እርስ በርሳቸው “አይተን እናምን ዘንድ የእስራኤል ንጉሥ ክርስቶስ እስቲ አሁን ከተሰቀለበት እንጨት ይውረድ” ተባባሉ። (ማርቆስ 15:29-32) ከተሰቀሉት መካከል ምንም ጥፋት የሌለበት ኢየሱስ ብቻ ቢሆንም በቀኙና በግራው የተሰቀሉት ዘራፊዎች እንኳ ሳይቀር ነቀፉት።
አራቱ ሮማውያን ወታደሮችም በኢየሱስ ላይ መቀለድ ጀመሩ። ወታደሮቹ የኮመጠጠ የወይን ጠጅ ሲጠጡ ቆይተው ሊሆን ይችላል፤ አሁን በኢየሱስ ላይ ለማፌዝ የወይን ጠጁን ወደ እሱ አቀረቡት፤ ኢየሱስ ወይኑን ተቀብሏቸው ሊጠጣ እንደማይችል ግልጽ ነው። ሮማውያኑ በኢየሱስ አናት ላይ የተንጠለጠለውን ምልክት እየጠቆሙ “አንተ የአይሁዳውያን ንጉሥ ከሆንክ ራስህን አድን” በማለት ዘበቱበት። (ሉቃስ 23:36, 37) እስቲ አስበው! መንገድ፣ እውነትና ሕይወት መሆኑን ያስመሠከረው ሰው ግፍ እየተፈጸመበትና እየተፌዘበት ነው። ያም ቢሆን እያዩት ያሉትን አይሁዳውያን፣ የሚያፌዙበትን ሮማውያን ወታደሮች እንዲሁም እንጨት ላይ ከጎኑ የተሰቀሉትን ሁለት ወንጀለኞች ሳይነቅፍ የደረሰበትን መከራ በጽናት ተቋቋመ!
አራቱ ወታደሮች መደረቢያዎቹን ወስደው አራት ቦታ ቆራረጧቸው። ከዚያም የትኛውን እንደሚወስዱ ለመወሰን ዕጣ ተጣጣሉ። ኢየሱስ ከውስጥ የለበሰው ግን “ከላይ እስከ ታች አንድ ወጥ ሆኖ ያለ ስፌት የተሠራ” ከፍተኛ ጥራት ያለው ልብስ ነው። ወታደሮቹ “ከምንቀደው ዕጣ ተጣጥለን ለማን እንደሚደርስ እንወስን” ተባባሉ። ይህን ሲያደርጉ “መደረቢያዎቼን እርስ በርሳቸው ተከፋፈሉ፤ በልብሴም ላይ ዕጣ ተጣጣሉ” የሚለውን የቅዱስ መጽሐፉን ቃል ፈጽመዋል።—ዮሐንስ 19:23, 24፤ መዝሙር 22:18
ከተወሰነ ጊዜ በኋላ ከዘራፊዎቹ አንዱ ኢየሱስ በእርግጥም ንጉሥ መሆን እንዳለበት አስተዋለ። በመሆኑም ጓደኛውን እንዲህ ሲል ገሠጸው፦ “አንተ ራስህ ተመሳሳይ ፍርድ ተቀብለህ እያለ ትንሽ እንኳ አምላክን አትፈራም? እኛስ ላደረግነው ነገር የሚገባንን ቅጣት በሙሉ እየተቀበልን ስለሆነ በእኛ ላይ የተፈጸመው ፍርድ ተገቢ ነው፤ ይህ ሰው ግን ምንም የሠራው ጥፋት የለም።” ቀጥሎም ኢየሱስን “ወደ መንግሥትህ ስትመጣ አስበኝ” በማለት ተማጸነው።—ሉቃስ 23:40-42
ኢየሱስም “እውነት እልሃለሁ ዛሬ፣ ከእኔ ጋር በገነት ትሆናለህ” በማለት መለሰለት፤ ኢየሱስ ‘ከእኔ ጋር በመንግሥቴ ትሆናለህ’ አላለውም። (ሉቃስ 23:43) ኢየሱስ ለወንጀለኛው የሰጠው ተስፋ ለሐዋርያቱ ከገባው ቃል ይኸውም በመንግሥቱ ከእሱ ጋር በዙፋን እንደሚቀመጡ ከሰጣቸው ተስፋ የተለየ ነው። (ማቴዎስ 19:28፤ ሉቃስ 22:29, 30) ይሁንና ይህ አይሁዳዊ ወንጀለኛ፣ ይሖዋ መጀመሪያ ላይ አዳምና ሔዋን እንዲሁም ዘሮቻቸው እንዲኖሩበት በምድር ላይ ስላዘጋጀው ገነት ሰምቶ ሊሆን ይችላል። ዘራፊው የሞተው እንዲህ ያለ ተስፋ እንደተዘጋጀለት አውቆ ነው።
-
-
“ይህ በእርግጥ የአምላክ ልጅ ነበር”ኢየሱስ—መንገድ፣ እውነት፣ ሕይወት
-
-
ምዕራፍ 132
“ይህ በእርግጥ የአምላክ ልጅ ነበር”
ማቴዎስ 27:45-56 ማርቆስ 15:33-41 ሉቃስ 23:44-49 ዮሐንስ 19:25-30
ኢየሱስ በእንጨት ላይ ተሰቅሎ ሞተ
ኢየሱስ ሲሞት የተፈጸሙ እንግዳ ክንውኖች
አሁን ከቀኑ “ስድስት ሰዓት” ሆኗል። “አገሩ በሙሉ እስከ ዘጠኝ ሰዓት ድረስ በጨለማ ተሸፈነ።” (ማርቆስ 15:33) እንግዳ የሆነውና ጭንቅ የሚለው ይህ ጨለማ የተከሰተው በፀሐይ ግርዶሽ ሳቢያ አይደለም። ምክንያቱም የፀሐይ ግርዶሽ የሚፈጠረው አዲስ ጨረቃ በምትኖርበት ጊዜ ነው፤ አሁን የፋሲካ ወቅት ሲሆን በዚህ ጊዜ ደግሞ ጨረቃ ሙሉ ነች። ከዚህም ሌላ ለጥቂት ደቂቃዎች ብቻ ከሚቆየው የፀሐይ ግርዶሽ በተለየ ይህ ጨለማ የቆየው ረዘም ላለ ጊዜ ነው። ስለዚህ ምድሪቱ በጨለማ እንድትሸፈን ያደረገው አምላክ ነው!
በኢየሱስ ላይ ሲያላግጡ የቆዩት ሰዎች በዚህ ወቅት ምን እንደሚሰማቸው አስበው። አካባቢው በጨለማ በተሸፈነበት ሰዓት አራት ሴቶች ወደ መከራ እንጨቱ ቀረቡ። እነሱም የኢየሱስ እናት፣ ሰሎሜ፣ መግደላዊቷ ማርያምና የትንሹ ያዕቆብ እናት የሆነችው ማርያም ናቸው።
ሐዋርያው ዮሐንስ በሐዘን ከተደቆሰችው የኢየሱስ እናት ጋር ሆኖ ‘በመከራው እንጨት አጠገብ’ ቆሟል። ማርያም ወልዳና ተንከባክባ ያሳደገችው ልጇ ተሰቅሎ ሲሠቃይ እየተመለከተች ነው። በዚህ ወቅት “ትልቅ ሰይፍ” በውስጧ ያለፈ ያህል ተሰምቷት መሆን አለበት። (ዮሐንስ 19:25፤ ሉቃስ 2:35) ኢየሱስ በከፍተኛ ሥቃይ ላይ ቢሆንም የእናቱ ነገር አሳስቦታል። እንደምንም ተጣጥሮ በጭንቅላቱ ወደ ዮሐንስ በማመልከት እናቱን “ልጅሽ ይኸውልሽ!” አላት። ከዚያም ወደ ማርያም በመጠቆም ዮሐንስን “እናትህ ይህችውልህ!” አለው።—ዮሐንስ 19:26, 27
በዚህ መንገድ ኢየሱስ፣ እናቱን እንዲንከባከባት ይበልጥ ለሚወደው ሐዋርያ በአደራ ሰጠው፤ በዚህ ወቅት ማርያም መበለት ሳትሆን አትቀርም። ኢየሱስ፣ ወንድሞቹ ይኸውም የማርያም ሌሎች ልጆች በእሱ ገና እንዳላመኑ ያውቃል። በመሆኑም የእናቱ ቁሳዊ ብቻ ሳይሆን መንፈሳዊ ፍላጎትም እንዲሟላ ዝግጅት እያደረገ ነው። ይህ እንዴት ያለ ጥሩ ምሳሌ ነው!
ጨለማው ሊገፈፍ አካባቢ ኢየሱስ “ተጠማሁ” አለ። ይህን ሲል የቅዱስ መጽሐፉ ቃል እንዲፈጸም እያደረገ ነው። (ዮሐንስ 19:28፤ መዝሙር 22:15) ኢየሱስ፣ ንጹሕ አቋሙ እስከ መጨረሻ ድረስ እንዲፈተን አባቱ ጥበቃውን ከእሱ ላይ እንዳነሳ ሆኖ ተሰምቶታል። ክርስቶስ “ኤሊ፣ ኤሊ፣ ላማ ሳባቅታኒ?” ብሎ ጮኸ፤ ትርጉሙም “አምላኬ፣ አምላኬ ለምን ተውከኝ?” ማለት ነው። ኢየሱስ የተናገረው በገሊላ በሚነገር የአረማይክ ቋንቋ ሊሆን ይችላል። በአቅራቢያው የቆሙት ሰዎች ምን ማለቱ እንደሆነ ግልጽ ስላልሆነላቸው “አያችሁ! ኤልያስን እየተጣራ ነው” አሉ። ከመካከላቸው አንዱ ሮጦ በመሄድ የኮመጠጠ የወይን ጠጅ ውስጥ ሰፍነግ ከነከረ በኋላ በመቃ ላይ አድርጎ እንዲጠጣ ለኢየሱስ ሰጠው። ሌሎች ግን “ተዉት! እስቲ ኤልያስ መጥቶ ያወርደው እንደሆነ እንይ” አሉ።—ማርቆስ 15:34-36
ከዚያም ኢየሱስ “ተፈጸመ!” ብሎ ጮኸ። (ዮሐንስ 19:30) አዎን፣ አባቱ ወደ ምድር ሲልከው እንዲያከናውነው የሰጠውን ሥራ ሁሉ ፈጽሟል። በመጨረሻም ኢየሱስ “አባት ሆይ፣ መንፈሴን በእጅህ አደራ እሰጣለሁ” አለ። (ሉቃስ 23:46) በዚህ መንገድ ኢየሱስ የሕይወቱን ኃይል ለይሖዋ ሰጠ፤ ይህን ያደረገው አምላክ እንደገና መልሶ እንደሚሰጠው እርግጠኛ ሆኖ ነው። ከዚያም ክርስቶስ በአምላክ ሙሉ በሙሉ በመተማመን ራሱን ዘንበል አድርጎ ሞተ።
በዚህ ጊዜ ኃይለኛ የምድር መናወጥ ተከሰተ፤ ዓለቶችም ተሰነጣጠቁ። የምድር መናወጡ በጣም ከባድ ከመሆኑ የተነሳ ከኢየሩሳሌም ውጭ ያሉ መቃብሮች ተከፈቱ፤ አስከሬኖችም ከመቃብሩ ውስጥ ተስፈንጥረው ወጡ። በዚያ የሚያልፉ ሰዎች አስከሬኖቹን ሲያዩ ወደ “ቅድስቲቱ ከተማ” ገብተው የተመለከቱትን ነገር አወሩ።—ማቴዎስ 12:11፤ 27:51-53
ኢየሱስ ሲሞት፣ በአምላክ ቤተ መቅደስ ውስጥ ቅድስቱን ከቅድስተ ቅዱሳኑ የሚለየው ትልቅና ወፍራም መጋረጃ ከላይ እስከ ታች ለሁለት ተቀደደ። ይህ አስደናቂ ክንውን አምላክ፣ ልጁን በገደሉት ሰዎች ላይ የተሰማውን ቁጣ ይገልጻል፤ ከዚህም ሌላ ወደ ቅድስተ ቅዱሳኑ ማለትም ወደ ሰማይ የሚያስገባው መንገድ እንደተከፈተ ያመለክታል።—ዕብራውያን 9:2, 3፤ 10:19, 20
ሰዎቹ ታላቅ ፍርሃት ያደረባቸው መሆኑ የሚያስገርም አይደለም። ግድያውን እንዲያስፈጽም ኃላፊነት የተሰጠው መኮንን “ይህ ሰው በእርግጥ የአምላክ ልጅ ነበር” አለ። (ማርቆስ 15:39) ይህ መኮንን፣ በጲላጦስ ፊት በተካሄደው ችሎት ላይ ኢየሱስ የአምላክ ልጅ ስለ መሆኑ በተጠየቀበት ወቅት በቦታው ኖሮ ሊሆን ይችላል። አሁን ኢየሱስ ጻድቅ እንደሆነ አልፎ ተርፎም የአምላክ ልጅ እንደሆነ አመነ።
በእነዚህ ያልተለመዱ ክንውኖች ስሜታቸው የተጎዳ ሌሎች ሰዎች የተሰማቸውን ጥልቅ ሐዘንና ኀፍረት ለመግለጽ “ደረታቸውን እየደቁ ወደ ቤታቸው ተመለሱ።” (ሉቃስ 23:48) በርቀት ሆነው ከሚመለከቱት መካከል አንዳንድ ጊዜ ከኢየሱስ ጋር ይጓዙ የነበሩ በርካታ ሴት ደቀ መዛሙርት ይገኙበታል። እነሱም በእነዚህ አስገራሚ ክንውኖች ስሜታቸው በጥልቅ ተነክቷል።
-
-
የኢየሱስ አስከሬን ተዘጋጅቶ ተቀበረኢየሱስ—መንገድ፣ እውነት፣ ሕይወት
-
-
ምዕራፍ 133
የኢየሱስ አስከሬን ተዘጋጅቶ ተቀበረ
ማቴዎስ 27:57–28:2 ማርቆስ 15:42–16:4 ሉቃስ 23:50–24:3 ዮሐንስ 19:31–20:1
የኢየሱስን አስከሬን ከእንጨቱ ላይ አወረዱት
አስከሬኑ ለቀብር ተዘጋጀ
ሴቶቹ መቃብሩን ባዶ ሆኖ አገኙት
ዓርብ፣ ኒሳን 14 ምሽት እየተቃረበ ነው። ኒሳን 15 ላይ የሚውለው ሰንበት ፀሐይ ስትጠልቅ ይጀምራል። ኢየሱስ ሞቷል፤ ከጎኑ የተሰቀሉት ሁለቱ ዘራፊዎች ግን አሁንም በሕይወት አሉ። ሕጉ፣ በድን ‘በእንጨቱ ላይ ማደር’ እንደሌለበት ከዚህ ይልቅ “በዚያው ዕለት” መቀበር እንዳለበት ይናገራል።—ዘዳግም 21:22, 23
ዓርብ ከሰዓት በኋላ የዝግጅት ቀን ተብሎ ይጠራል፤ ምክንያቱም ሰዎች ምግብ የሚያዘጋጁትና ሰንበት እስኪያልፍ ድረስ ሊቆዩ የማይችሉትን ሌሎች አጣዳፊ ሥራዎች የሚያጠናቅቁት በዚህ ቀን ነው። ፀሐይ ስትጠልቅ ድርብ ወይም “ታላቅ” ሰንበት ይጀምራል። (ዮሐንስ 19:31) ለሰባት ቀን የሚከበረው የቂጣ በዓል የመጀመሪያ ቀን ኒሳን 15 ነው፤ የዚህ በዓል የመጀመሪያ ቀን ደግሞ ምንጊዜም ሰንበት ነው። (ዘሌዋውያን 23:5, 6) በዚህ ዓመት የበዓሉ የመጀመሪያ ቀን ከሳምንታዊው ሰንበት ይኸውም ከሰባተኛው ቀን ጋር ተገጣጥሟል።
አይሁዳውያን ጲላጦስ ፊት ቀርበው የኢየሱስና አጠገቡ ያሉት የሁለቱ ዘራፊዎች ሞት እንዲፋጠን ያደርግ ዘንድ ጠየቁት። ይህ የሚደረገው እንዴት ነው? እግሮቻቸውን በመስበር ነው። ይህም በእግሮቻቸው ተጠቅመው ሰውነታቸውን ወደ ላይ በመግፋት አየር መሳብ በጣም ከባድ እንዲሆንባቸው ያደርጋል። ስለዚህ ወታደሮቹ መጥተው የሁለቱን ዘራፊዎች እግር ሰበሩ። ኢየሱስ ግን መሞቱን ስላዩ እግሮቹን አልሰበሩም። ይህም “አጥንቶቹን ሁሉ ይጠብቃል፤ አንዳቸውም ቢሆኑ አልተሰበሩም” የሚለው የመዝሙር 34:20 ጥቅስ ፍጻሜውን እንዲያገኝ አደረገ።
ከወታደሮቹ አንዱ ኢየሱስ እንደሞተ ሙሉ በሙሉ እርግጠኛ ለመሆን ጎኑን በጦር ወጋው፤ ጦሩም ልቡ አካባቢ በስቶ ስለገባ ወዲያው “ደምና ውኃ ፈሰሰ።” (ዮሐንስ 19:34) ይህ ደግሞ “እነሱም የወጉትን ያዩታል” የሚለው ሌላ ትንቢት እንዲፈጸም ያደርጋል።—ዘካርያስ 12:10
አርማትያስ ከተባለች ከተማ የመጣ ዮሴፍ የሚባል “ሀብታም” እና የተከበረ የሳንሄድሪን አባል ኢየሱስ ሲገደል በቦታው ተገኝቷል። (ማቴዎስ 27:57) ዮሴፍ “ጥሩና ጻድቅ ሰው” እንደሆነ እንዲሁም ‘የአምላክን መንግሥት እንደሚጠባበቅ’ ተገልጿል። “ዮሴፍ የኢየሱስ ደቀ መዝሙር” ቢሆንም ‘አይሁዳውያንን ስለፈራ ይህን ለማንም አልተናገረም።’ ያም ቢሆን ሸንጎው በኢየሱስ ላይ ያስተላለፈውን ፍርድ አልደገፈም። (ሉቃስ 23:50፤ ማርቆስ 15:43፤ ዮሐንስ 19:38) ዮሴፍ ራሱን አደፋፍሮ ወደ ጲላጦስ ገባና የኢየሱስ አስከሬን እንዲሰጠው ጠየቀ። ጲላጦስም ኢየሱስ ሞቶ እንደሆነ ለማወቅ የመቶ አለቃውን ጠርቶ ጠየቀው። መሞቱን ከመቶ አለቃው ካረጋገጠ በኋላም አስከሬኑን እንዲወስድ ለዮሴፍ ፈቀደለት።
ዮሴፍ ንጹሕ የሆነ ጥሩ በፍታ ከገዛ በኋላ የኢየሱስን አስከሬን ከእንጨቱ ላይ አወረደው። ከዚያም አስከሬኑን ለቀብር ለማዘጋጀት በበፍታው ገነዘው። “ቀደም ሲል በማታ ወደ ኢየሱስ መጥቶ የነበረው ኒቆዲሞስም” አስከሬኑን በማዘጋጀቱ ሥራ አገዘ። (ዮሐንስ 19:39) ኒቆዲሞስ 30 ኪሎ ግራም ገደማ የሚሆን ውድ የሆነ የከርቤና የእሬት ድብልቅ ይዞ መጣ። ከዚያም ጥሩ መዓዛ ባላቸው በእነዚህ ቅመሞች ተጠቅመው የኢየሱስን አስከሬን በአይሁዳውያን የአገናነዝ ልማድ መሠረት ገነዙት።
ዮሴፍ ማንም ሰው ተቀብሮበት የማያውቅ ከዓለት ተፈልፍሎ የተሠራ አዲስ የመቃብር ስፍራ በአቅራቢያው አለው፤ የኢየሱስን አስከሬን እዚያ አሳረፉት። ከዚያም ትልቅ ድንጋይ አንከባለው መቃብሩን ዘጉት። አስከሬኑን ሰንበት ከመጀመሩ በፊት ለመቅበር ሲባል ዝግጅቱ የተከናወነው በጥድፊያ ነው። መግደላዊቷ ማርያምና የትንሹ ያዕቆብ እናት የሆነችው ማርያም የኢየሱስን አስከሬን ለቀብር በማዘጋጀቱ ሥራ አስተዋጽኦ አበርክተው ሊሆን ይችላል። እነዚህ ሴቶች ከሰንበት በኋላ የኢየሱስን አስከሬን ለመቀባት የሚጠቀሙባቸውን “ጥሩ መዓዛ ያላቸው ቅመሞችና ዘይቶች ለማዘጋጀት” በፍጥነት ወደ ቤታቸው ሄዱ።—ሉቃስ 23:56
በማግስቱ ማለትም በሰንበት ቀን የካህናት አለቆቹና ፈሪሳውያን ወደ ጲላጦስ ሄዱና እንዲህ አሉት፦ “ያ አስመሳይ በሕይወት ሳለ ‘ከሦስት ቀን በኋላ እነሳለሁ’ ብሎ የተናገረው ትዝ አለን። ስለዚህ ደቀ መዛሙርቱ መጥተው እንዳይሰርቁትና ለሕዝቡ ‘ከሞት ተነስቷል!’ እንዳይሉ እስከ ሦስተኛው ቀን ድረስ መቃብሩ እንዲጠበቅ ትእዛዝ ስጥልን። አለዚያ ይህ የኋለኛው ማታለያ ከፊተኛው የከፋ ይሆናል።” ጲላጦስም “ጠባቂዎች መውሰድ ትችላላችሁ። ሄዳችሁ በምታውቁት መንገድ አስጠብቁ” አላቸው።—ማቴዎስ 27:63-65
እሁድ ጠዋት ማለዳ ላይ መግደላዊቷ ማርያም፣ የያዕቆብ እናት ማርያምና ሌሎች ሴቶች የኢየሱስን አስከሬን ለመቀባት ጥሩ መዓዛ ያላቸው ቅመሞች ይዘው ወደ መቃብሩ ሄዱ። እርስ በርሳቸውም “በመቃብሩ ደጃፍ ላይ ያለውን ድንጋይ ማን ያንከባልልልናል?” ተባባሉ። (ማርቆስ 16:3) ሆኖም ታላቅ የምድር መናወጥ ተከስቷል። ከዚህም ሌላ የአምላክ መልአክ ድንጋዩን አንከባሎታል፤ ጠባቂዎቹ ሄደዋል፣ መቃብሩም ባዶ ነው!
-