የአንባቢያን ጥያቄዎች
ምሥራቹን የመስበኩ ሥራ የሚያበቃው መቼ ነው?
ኢየሱስ “ይህ የመንግሥቱ ምሥራች ለብሔራት ሁሉ ምሥክር እንዲሆን በመላው ምድር ይሰበካል፤ ከዚያም መጨረሻው ይመጣል” ብሏል። (ማቴ. 24:14) በዚህ ጥቅስ እንዲሁም በቁጥር 6 እና 13 ላይ “መጨረሻ” ተብሎ የተተረጎመው የግሪክኛ ቃል ቴሎስ ነው። ይህ ቃል የሰይጣን ዓለም በአርማጌዶን የሚጠፋበትን ጊዜ ያመለክታል። (ራእይ 16:14, 16) ስለዚህ አርማጌዶን ሊጀምር ጥቂት እስኪቀረው ድረስ ምሥራቹን መስበካችንን እንቀጥላለን። ይህ ቀደም ሲል በነበረን ግንዛቤ ላይ የተደረገ ማስተካከያ ነው።
ቀደም ሲል፣ ምሥራቹን መስበክ የምናቆመው ታላቁ መከራ በታላቂቱ ባቢሎን ጥፋት በሚጀምርበት ጊዜ እንደሆነ እናስብ ነበር። (ራእይ 17:3, 5, 15, 16) ይህ ክንውን “ይሖዋ በጎ ፈቃድ [የሚያሳይበት] ዓመት” ማብቃቱን እንደሚያሳይ እናምን ነበር። (ኢሳ. 61:2) በተጨማሪም ከታላቁ መከራ የሚተርፉ ሰዎች ይህ ክንውን ከመጀመሩ በፊት ለይሖዋ ያላቸውን ታማኝነት ማስመሥከር እንደሚጠበቅባቸው ይሰማን ነበር። እነዚህ ሰዎች በ607 ዓ.ዓ. ከኢየሩሳሌም ጥፋት ከተረፉት አይሁዳውያን ጋር እንደሚመሳሰሉ እናስብ ነበር። እነዚያ አይሁዳውያን ይሖዋን በማምለካቸውና ክፋትን በመጥላታቸው ከጥፋቱ እንዲተርፉ አስቀድሞ ምልክት ተደርጎባቸው ነበር። (ሕዝ. 5:11፤ 9:4) ሆኖም ይህ ንጽጽር ኢየሱስ በማቴዎስ 24:14 ላይ ከተናገረው ሐሳብ ጋር ይጋጫል፤ ይህ ጥቅስ ሰዎች መጨረሻው ሊመጣ ማለትም አርማጌዶን ሊጀምር ጥቂት እስኪቀረው ድረስ ለምሥራቹ ምላሽ የመስጠት አጋጣሚ ሊኖራቸው እንደሚችል ይጠቁማል።
ማቴዎስ 24:14ን በምንረዳበት መንገድ ላይ ማስተካከያ በማድረጋችን በበረዶ ድንጋይ ስለተመሰለ መልእክት የሚናገረውን ራእይ 16:21ን በምንረዳበት መንገድ ላይ ማስተካከያ ማድረግ ያስፈልገናል። በዚህ ጉዳይ ላይ ያደረግነው ተጨማሪ ምርምር ሁለቱ ጥቅሶች ተመጋጋቢ እንደሆኑ አስገንዝቦናል። እንዴት? ለውጥ የሚያመጣው ሰዎች ለመንግሥቱ መልእክት የሚሰጡት ምላሽ ነው። ሐዋርያው ጳውሎስ መልእክቱ “ወደ መዳን በሚወስደው ጎዳና ላይ ላሉት” ምሥራች ወይም “የሕይወት መዓዛ” እንደሆነ ገልጿል። ለአምላክ ጠላቶች ግን መጥፎ ዜና ማለትም “የሞት ሽታ” ነው። (2 ቆሮ. 2:15, 16) እነዚህ ሰዎች፣ የሚወዱት ዓለም ክፉ እንደሆነ፣ በሰይጣን ቁጥጥር ሥር እንዳለና በቅርቡ እንደሚጠፋ ስለሚያጋልጥ የመንግሥቱን መልእክት ይጠሉታል።—ዮሐ. 7:7፤ 1 ዮሐ. 2:17፤ 5:19
ከዚህም ሌላ ምሳሌያዊው የበረዶ ድንጋይ “እጅግ ታላቅ” እንደሚሆን ልብ ማለት ያስፈልጋል። ይህም በታላቁ መከራ ወቅት የስብከቱ ሥራ ይበልጥ ኃይለኛ እንደሚሆን ማለትም የይሖዋ ስም ከዚህ በፊት ሆኖ በማያውቅ መጠን በስፋት እንደሚታወቅ የሚጠቁም ሊሆን ይችላል። (ሕዝ. 39:7) በዚያ ያለቀ ሰዓት ማለትም ታላቂቱ ባቢሎን ከጠፋች በኋላ አንዳንዶች መልእክቱን እንደ ሕይወት መዓዛ መቁጠር ይጀምሩ ይሆን? ሊሆን ይችላል። ምናልባትም የይሖዋ ምሥክሮች የሐሰት ሃይማኖት እንደሚጠፋ ለበርካታ ዓመታት ሲናገሩ እንደቆዩ ይገነዘቡ ወይም ያስታውሱ ይሆናል።
ሁኔታውን በጥንቷ ግብፅ ከአሥሩ መቅሰፍቶች በኋላ ከተፈጠረው ነገር ጋር ማወዳደር ይቻላል። ይሖዋ ‘በግብፅ አማልክት ሁሉ ላይ የፍርድ እርምጃ ከወሰደ’ በኋላ እስራኤላውያን ያልሆኑ ሰዎችን ያቀፈ “እጅግ ብዙ ድብልቅ ሕዝብ” ከአምላክ ሕዝብ ጋር አብሮ ወጥቷል። (ዘፀ. 12:12, 37, 38) እነዚህ የባዕድ አገር ሰዎች ሙሴ አሥሩን መቅሰፍቶች አስመልክቶ የተናገረው ማስጠንቀቂያ ሲፈጸም ካዩ በኋላ ከይሖዋ ሕዝቦች ጋር ለመቀላቀል ወስነው ሊሆን ይችላል።
ከታላቂቱ ባቢሎን ጥፋት በኋላ ወደ ይሖዋ ዘወር የሚሉ ሰዎች በወቅቱ በምድር ላይ ለሚቀሩት የክርስቶስ ወንድሞች መልካም ነገር የማድረግ አጋጣሚ ያገኛሉ። (ማቴ. 25:34-36, 40) እርግጥ ነው፣ ከቅቡዓኑ መካከል የመጨረሻዎቹ ከአርማጌዶን ጥቂት ቀደም ብሎ ሰማያዊ ሽልማታቸውን ሲያገኙ ሰዎች እንደ በግ መቆጠር የሚችሉበት አጋጣሚ ያበቃል።
ይህ አዲስ ግንዛቤ የይሖዋን ታላቅ ፍቅርና ምሕረት ጎላ አድርጎ ያሳያል። በእርግጥም እሱ “ሁሉ ለንስሐ እንዲበቃ እንጂ ማንም እንዲጠፋ” አይፈልግም!—2 ጴጥ. 3:9